Site icon ETHIO12.COM

“ሕወሓት ለሰላም ተነሳሽነትን ከማሳየት ይልቅ ለወረራ ዝግጅት እያደረገ ነው” አማራ ክልል

በአማራ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች ላይ ብሄርን ከብሄር፣ እምነትን ከእምነት ለማጋጨት የሚንቀሳቀሱ ሃይሎች ከድርጊታቸው ሊቆጠቡ ይገባል ሲሉ የክልሉ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ግዛቸው ሙሉነህ አሳሰቡ፡፡ሕወሓትለሰላምተነሳሽነትንከማሳየትይልቅለወረራዝግጅትእያደረገነው

አቶ ግዛቸው ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ ጸረ ሰላም ሃይሎች ብሄርና እምነትን መሰረት ያደረገ ግጭት እንዲቀሰቀስ ሙሉ ሃይላቸውን ተጠቅመው እየሰሩ ይገኛሉ። ስርዓት ለማስያዝና ሕግ ለማስከበር የጸጥታ ሃይሉ ስምሪት አድርጓል፡፡ 

አንዳንድ አካባቢዎች ምልክቶች ይታያሉ፣ የተፈጠሩ ግጭቶችም አሉ፡፡ ጸረ ሰላም ሃይሎች ወትሮም ይሰሩ ነበር አሁን ደግሞ ሙሉ ሃይላቸውን ተጠቅመው እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ 

ችግሩን በሽምግልና እና በተለያዩ የሰላም አማራጮች እያደራደሩ ለማረጋጋት፣ ወደከፋ ግጭት እንዳያድግ እየተሰራ ቢሆንም ሰላምን የማይሹ ሃይሎቹ አሁንም ሊያርፉ አልቻሉም፡፡ በአጎራባች ክልልችም ተመሳሳይ እንቅስቃሴዎች መስተዋላቸውን አንስተዋል፡፡ 

በማዕከላዊ ጎንደር አካባቢ የቅማንት ጽንፈኛ ቡድን በተደጋጋሚ ትንኮሳ እያደረገ ይገኛል፣ በጃዊ አካባቢም ያለው ዝንባሌ ትክክል አይደለም፣ በተለይ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ መተከል ዞን አዋሳኝ አካባቢዎች ላይ የብሄር ግጭት ለማስነሳት እንቅስቃሴዎች መኖራቸውንና የሰው ሕይወትም እንደጠፋ አስታውሰዋል፡፡ 

እንደርሳቸው ማብራሪያ፤ ኦሮሞ ብሄረሰብ ላይ ሰሜን ሸዋ፣ ምንጃር አካባቢም በተመሳሳይ እነዚህ የጥፋት ሃይሎች ግጭት ለማስነሳት እንቅስቃሴ እያደረጉ ናቸው። ይህ ሕብረተሰብን አይወክልም፡፡ ከሁሉም ብሄሮች ያሉ ሕዝብን ከሕዝብ የማጋጨት፣ የመላላክ ስራና ወደ ሌላ ጽንፍ ለመውሰድ የሚሰሩ አካላት አደብ ሊገዙ ይገባል ብለዋል፡፡ 

ሰሞኑንም ሰላምን የማወክ ዝንባሌ ይታያል፡፡ በክልሉ ሰላምና ደህንነት ላይ ጠባሳ የሚጥሉ እንቅስቃሴዎችን መፍታት ያስፈልጋል፡፡ ችግሮችም ካሉ መፈታት የሚቻለው በውይይት ብቻ ነው፡፡ 

ወደ ጦርነት የተገባው የህልውና ስጋት በመኖሩ ነው ያሉት አቶ ግዛቸው፤ አሁንም ሕወሓት በወረራ በያዛቸው አካባቢዎች ላይ የህልውና ስጋት የሆነባቸው አካባቢዎችን መልቀቅ አለበት፡፡ አላማጣ እና ኮረም፣ ዋግ ኽምራ አካባቢም ሶስት ወረዳ ላይ፣ ማይጠብሪ አዲአርቃይ አካባቢዎች ላይም የሽብር ቡድኑ ወረራ ፈጽሟል ብለዋል፡፡ 

ጠላት በእነዚህ አካባቢዎች ረዘም ያለ ጊዜ እየተንቀሳቀሰ በመሆኑ ዜጎችንም ለእንግልት እየዳረገ ነው፡፡ መንግሥት ባለበት ቆሞ የያዘውን አስጠብቆ ሕዝቡ እፎይታ እንዲያገኝ በሚል እነዚህ አካባቢ ያሉ ሰዎች ዋጋ እየከፈሉ ይገኛሉ፡፡ 

መንግሥት የሰላም አማራጭን ቢከተልም ሕወሓት ለእዚህ ዝግጁ የሆነ አይመስልም፡፡ አሸባሪ ሃይሉ ለሰላም ተነሳሽነትን ከማሳየት ይልቅ ለወረራ ዝግጅት እያደረገ ነው፡፡

ድርጊቱ ቡድኑ ለሕዝብ ደንታ ቢስ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ ሂደት የሚቀጥል ከሆነ ምን ይሆናል የሚለውን የሚወስነው የፌዴራል መንግሥት ነው፡፡ የፌዴራል መንግሥት በሚሰጠው አቅጣጫ መሰረት እንደክልል የድርሻችንን የምንወጣ ይሆናል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ 

ለዘላቂ ሰላም ትርጉም ከሰጠ በሚል ሕዝብ አላስፈላጊ ዋጋ እየከፈለና እየተንገላታ ይገኛል፡፡ ፌዴራል መንግስትም ሰላም እንዲሰፍን ማድረግ የሚችለውን ሁሉ እያደረገ ነው፡፡ ይህ የማይሆን ከሆነ ሕዝብ እየተጎዳ ዝም ማለት ስለማይቻል አንድ ውሳኔ ላይ እንደሚደረስ እንጠብቃለን ብለዋል፡፡ 

ከጦርነት ይልቅ ጉዳዩ በሰላም እንዲፈታ እንጠብቃለን፡፡ ከዚህም ከዛኛውም ወገን የሚጎዳው ሕዝብ ነው፡፡ ያኛውም የእኛ ሕዝብ እንደመሆኑ እንዲጎዳ አንፈልግም፡፡

መንግስት የሚመራው ፓርቲ ከጉባኤ በኋላ ከህዝብ ጋር ባካሄደው ውይይት የሰላም ጉዳይ አሳሳቢ መሆኑ ተነስቷል፡፡ ሰላም ለማስፈን መፍትሄዎችና አቅጣጫዎችም ተቀምጠዋል። ሕዝቡን የሰላሙ ባለቤት የማድረግ ጉዳይም የመፍትሄዎቹ አካል መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡

ዘላለም ግዛው 

አዲስ ዘመን መጋቢት 25 ቀን 2014 ዓ.ም

Exit mobile version