Site icon ETHIO12.COM

የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ “ፖለቲካዊ ይዘት አለው” ባለው በሃይማኖት ስም የሚፈጸም የመሬት ወረራ ላይ እርምጃ እየወሰደ መሆኑንን አስታወቀ

ጽንፈኞች በሃይማኖትና በፖለቲካ ፖርቲዎች ብቻ ሳይሆን በመንግስት መዋቅር ዉስጥም እንደሚገኙ የተናገሩት ኃላፊ የብልጽግና ፖርቲ ባስቀመጠዉ አቅጣጫ ፖለቲካዊ መፍትሄና ፖለቲካዊ እርምጃ እየተወሰደ ነዉ። መንግስት የሕግ የበላይነትን የማስከበር ግዳጅ ስላለበት በተለያዩ ወንጀሎች የተጠረጠሩ ግለሰቦች በሕግ ቁጥጥር ስር መዋላቸዉንና ጉዳያቸዉም በሕግ አግባብ እየታየ ነው።

ሕዝቡ የሚያነሳቸዉን የጸጥታ ችግሮች በየጊዜዉ ተከታትለን እንቀርፋለን ያሉት ኃላፊዉ ፊንፊኔ የበርካታ ብሔር ብሔረሰቦች: የተለያዩ ሃይማኖቶችና የፖለቲካ ፖርቲዎች መገኛ እንደመሆኗ መጠን የሃይማኖት: የብሔርና የፖለቲካ ጽንፈኝነትና አክራሪነት በምንም አይነት መመዘኛ የጸጥታ ስጋት ሊሆን አይገባም።

በፊንፊኔ ከተማና በኦሮሚያ ክልል ድንበር አካባቢዎች በሃይማኖት ስም የሚፈጸመዉ የመሬት ወረራ ፖለቲካዊ ይዘት ስላለዉ ፖለቲካዊና ሕጋዊ እርምጃ እየተወሰደ ነዉ ሲል የፊንፊኔ ከተማ የሠላምና ጸጥታ አስተዳደር ቢሮ ገለጸ።

የፊንፊኔ ከተማ የሠላምና ጸጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ቀነአ ያደታ በፊንፊኔ ከተማ ሲካሄዱ በነበሩ ህዝባዊ የዉይይት መድረኮች ላይ ሲነሱ በነበሩ የጸጥታ ጥያቄዎችና እየተወሰዱ ባሉ እርምጃዎች ዙሪያ ለOBN ማብራሪያ ሰጥተዋል።

የፊንፊኔ ከተማ የፊንፊኔ ከተማ አስተዳደር: የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት: የፌደራል መንግስትና የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ ነች። በርካታ አህጉር አቀፍና አለም አቀፍ ድርጅቶችና ዲፕሎማቶች መቀመጫቸዉ እዚሁ በፊንፊኔ ከተማ ነዉ።

የበርካታ ብሄር ብሄረሰቦች: ሃይማኖቶች: የፖለቲካ ፖርቲዎች: የንግድ ማዕከላት: አንጋፋ የግልና የመንግስት ተቋማት መገኛ የሆነችዉ ፊንፊኔ በርካቶች በመግባባት: በመቻቻልና መከባበር የሚኖሩባት ከተማ ነች።

ፊንፊኔ ይህንን የመሠለ ሃገር አቀፍና አለም አቀፍ ገጽታ ቢኖራትም አንዳንድ ጽንፈኞች ግን ሃይማኖትን: ብሔርንና ፖለቲካን መሠረት ያደረገ አጀንዳ በማንሳት የከተማዋን ጸጥታ ለማደፍረስ ሲሯሯጡ ይስተዋላል።

የፊንፊኔ ከተማ የሠላምና ጸጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊዉ ዶ/ር ቀነአ ያደታ ባለፉት ሳምንታት በከተማዋ ሲካሄዱ በነበሩ ህዝባዊ የዉይይት መድረኮች ላይ አራት መሠረታዊ ጥያቄዎች ትኩረት አግኝተዉ መለየታቸዉ ይናገራሉ።

ከነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎች መካከል የብሔር: የሃይማኖትና የፖለቲካ ጽንፈኝነት ጉዳይ ዋንኛዉ እንደነበር ያስረዳሉ። ስርቆትና ሕገ ወጥ ግንባታን ጨምሮ በከተማዋ የሚታዩ ደረቅ ወንጀሎች: ህገ ወጥ የጦር መሳሪያና የገንዘብ ዝዉዉሮች ሕጋዊ መፍትሄ እንዲያገኙ ህዝቡ ጠይቋል ብለዋል። ሕብረተሰብ አቀፍ የፖሊስ አገልግሎት በየአካባቢዉ ተደራሽ እንዲሆን ሕዝቡ መጠየቁንም ኃላፊዉ አስታዉሰዋል።

በዉይይት መድረኮቹ ላይ ከተነሱ መሠረታዊ የሕዝብ ጥያቄዎች መካከል በሃይማኖት ስም የሚፈጸመዉ የመሬት ወረራ ሌላኛዉ መሆኑንም ኃላፊዉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

የተለያዩ ቡድኖችና ግለሰቦች በሃይማኖት ስም በፊንፊኔ ከተማና በኦሮሚያ ክልል ድንበር አካባቢዎች ከፍተኛ የመሬት ወረራ እያካሄዱ ነዉ። መንግስት የሕግ የበላይነትን ያስከብርልን ሲል ሕዝቡ ጠይቋል ብለዋል የከተማዉ የሠላምና ጸጥታ አስተዳደር ኃላፊዉ ዶ/ር ቀነአ ያደታ።

በሃይማኖት ስም በፊንፊኔ ከተማና በኦሮሚያ ክልል ድንበር አካባቢዎች የሚፈጸመዉ የመሬት ወረራም ፖለቲካዊ ይዘት እንዳለዉ ኃላፊዉ ተናግረዋል።

በተለያዩ መንግስታዊና በሕዝባዊ በአላት ላይ ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸዉ አጀንዳዎችን ይዘዉ በመምጣት ተገቢ ያልሆነ ድርጊት ለመፈጸም የሚነሳሱ ቡድኖች መታየታቸዉንም ተናግረዋል።

እነዚህ ጽንፈኛ ሃይማኖተኞች: ፖለቲከኞችና ብሔርተኞች በአድዋና በካራማራ የድል በአላት ላይም የሃገሪቱን ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ስም ጠርተዉ ሲሳደቡ ነበር ብለዋል። የብሔርን ስም ጠርተዉ ለማሳነስ የሚሞክሩ ጽንፈኞችም ነበሩ ብለዋል።

መንግስት የሕግ የበላይነትን የማስከበር ግዳጅ ስላለበት በተለያዩ ወንጀሎች የተጠረጠሩ ግለሰቦች በሕግ ቁጥጥር ስር መዋላቸዉንና ጉዳያቸዉም በሕግ አግባብ እየታየ መሆኑን ተናግረዋል።

ሕዝቡ የሚያነሳቸዉን የጸጥታ ችግሮች በየጊዜዉ ተከታትለን እንቀርፋለን ያሉት ኃላፊዉ ፊንፊኔ የበርካታ ብሔር ብሔረሰቦች: የተለያዩ ሃይማኖቶችና የፖለቲካ ፖርቲዎች መገኛ እንደመሆኗ መጠን የሃይማኖት: የብሔርና የፖለቲካ ጽንፈኝነትና አክራሪነት በምንም አይነት መመዘኛ የጸጥታ ስጋት ሊሆን አይገባም ብለዋል።

ጽንፈኞች በሃይማኖትና በፖለቲካ ፖርቲዎች ብቻ ሳይሆን በመንግስት መዋቅር ዉስጥም እንደሚገኙ የተናገሩት ኃላፊ የብልጽግና ፖርቲ ባስቀመጠዉ አቅጣጫ ፖለቲካዊ መፍትሄና ፖለቲካዊ እርምጃ እየተወሰደ ነዉ ብለዋል።

የጽንፈኝነት ችግር በጥቂት ቡድኖች የሚገለጽ እንጂ የከተማዋን ህዝብ አይወክልም ያሉት ኃላፊ የፊንፊኔ ከተማ የጸጥታ ሁኔታ ካለፉት አመታት አንጻር ከፍተኛ መሻሻል ማሳየቱን አንስተዋል።

የፊንፊኔን ከተማ ጸጥታና ደህንነት ይበልጥ አስተማማኝ ለማድረግ ከከተማዋ የጸጥታ አካላት: ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግስትና ከክልሉ የጸጥታ መዋቅር ጋር በትብብር እየሠራን ነዉ ብለዋል።

ወንድማገኝ አሰፋ – OBN

Exit mobile version