Site icon ETHIO12.COM

አማራ ክልል ትህነግ ዳግም ጦርነት ስላወጀ የ”ዝግጁነትን” አዋጅ አወጣ

Members of Amhara Special Forces stand guard along a street in Humera town, Ethiopia July 1, 2021. Photo: Reuters.

ከአማራ ክልል መንግስት የፀጥታ ምክርቤት ከተሰጠ መግለጫ የተወሰዱ ቁልፍ መልዕክቶችን

ከአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የፀጥታ ምክር ቤት የተሰጠ መግለጫ

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የፀጥታው ምክር ቤት ባደረገው ስብሰባ የክልሉን ሰላምና ፀጥታ ሁኔታ በዝርዝር ገምግሟል፡፡ የወያኔ ወራሪ ቡድን በየቀኑ የጦርነት ነጋሪት እየጎሰመ የትግራይን ህዝብ ለጦርነት እያነሳሳ በአማራ ክልል ላይ ዳግም ጦርነት አውጇል፡፡

ይህን አደገኛ ቅዠቱን ለመመከትና ለመቀልበስ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የክልሉ መንግስት የፀጥታ ምክርቤት በአንክሮ ተወያይቶበታል፡፡ ጸጥታ ምክርቤቱ በየደረጃው ያለው የፀጥታ መዋቅር ዝግጁ መሆን እንዳለበት አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡

በሌላ በኩል በየደረጃው በተደረጉ ህዝባዊ ውይይቶች ላይ ጎልተው ከወጡ ወሳኝ ጉዳዮች መካከል አንዱ የህግ ማስከበር ስራ መላላት ተጠቃሽ መሆኑን ጸጥታ ምክር ቤቱ በጥልቀት አንስቷል፡፡

በቅርብ ጊዜ ደግሞ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የአማራን የውስጥ አንድነት ለማዳከም፣ ህዝብ ከህዝብ በማጋጨትና በማጋደል ላይ ተሰማርተው ለጠላት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር እየሰሩ ያሉ የተደራጁና ያልተደራጁ ኃይሎች እየተበራከቱ መምጣታቸው ተጨባጭ የፀጥታ ስጋት እየፈጠሩ መሆኑን በዝርዝር ተወያይቶበታል፡፡

እነዚህ ኃይሎች በእምነት፣ በፖለቲካ፣ በብሔር ህዝባችን እየከፋፈሉ የአማራን የውስጥ አንድነት በማዳከም ለጥቃት ተጋላጭ እንዲሆን የሚያደርጉት ሙከራ በአጭር ካልተቀጨ በህዝባችንና በክልላችን ሰላምና ደህንነት ላይ ዘላቂ ጉዳት ሊያስከትል እንደሚችል ድምዳሜ ላይ ደርሶአል፡፡

የህገ-ወጥ ንግድን በማስፋፋት ካለው ሀገራዊ የምርት እጥረት በተጨማሪ ሰው ሰራሽ የምርት እጥረት በመፍጠር የኑሮ ውድነት የሚያባብሱ፣ ምርትን ለጠላት በኮንትሮባንድ አሳልፈው የሚልኩ፣ የህዝብን ሃብት የሚዘርፉ፣ የዜጐችን ነጻ እንቅስቃሴ የሚገድቡ ድርጊቶች በየአካባቢው ያቆጠቆጡ መጥተው ለክልሉ የፀጥታ ስጋት መሆናቸውን ጸጥታ ምክርቤቱ ለይቷል፡፡

ከዚህም በላይ በተለያዩ የክልሉ አካባቢወች እየተስፋፋ የመጣው ህገ-ወጥ የጦር መሣሪያ ዝውውር የክልሉን ሰላምና ደህንነት ስጋት ውስጥ እየጣለ ይገኛል፡፡

በተጨማሪም መሳሪያን ለመሞከር በሚል በሃዘንና በደስታ ላይ በግዴለሽነት በሚተኮስ ጥይት የንጹሀን ህይወት እየቀጨ እና የህዝባችን የፀጥታ ስጋትና የሃዘን ምንጭ እየሆነ መምጣቱን ጸጥታ ምክርቤቱ በአንክሮ ተመልክቷል፡፡

ህገ-ወጥነትና ስርዓት አልበኝነት ስር እየሰደደ በመምጣቱ ህገ-ወጥ ታጣቂዎች በሚያደርጉት ያልተገባ እንቅስቃሴ የክልሉን ልማቶች እያዳከመ፤ የዜጎችን ነጻ እንቅስቃሴ እየገደበ ፤ የኢንቨስትመንት እድሎችን እየዘጋ፣ የተፈጠረውን የስራ ዕድል እያጠፋ፣ ለቀጣይ ልማትም እንቅፋት በመሆንና በአጠቃላይ የአማራን ክልል ልማት በአደገኛ ሁኔታ እየተፈታተነ እንደሚገኝ አጽንኦት ሰጥቶ ተመልክቷል፡፡

እነዚህ ህገ-ወጥ ተግባራት በከተማም ሆነ በገጠር በአጭር ጊዜ ማረም ካልተቻለ የአማራ ክልል ልማት የሚያስቀጥል ሳይሆን የነበረውንም የሚያመክን የህገ-ወጥነትና የስርዓት አልበኝነት መናኸሪያ የሚያደርግ መሆኑን በመረዳት ለህዝብ ሰላምና ደህንነት ሲባል መልክ መያዝ እንዳለባቸው ታምኖበታል፡፡ በጦርነቱ ምክንያት ተፈናቀለው የሚገኙ ወገኖቻችንም በአግባቡ ምግብ እንዲያገኙ አድርጎ ወደ ቀያቸው ጊዜ መመለስ ካልተቻለ የፀጥታና ሰብአዊ ቀውስ እንደሚያስከትል ፀጥታ ምክርቤቱ ተወያይቶበታል፡፡

ከዚህ አንጻር መንግስት በየደረጃው ህግ የማስከበር ስራውን በጥብቅ በመፈፀም የህዝቡን ሰላምና ደህንነት ማስከበር አለበት በማለት ህዝቡ በተለያዩ መድረኮች ያነሳቸውን ጥያቄዎች መርምሮ ትክክለኛ ጥያቄ መሆኑን አስምሮበታል፡፡

ስለሆነም የክልሉ ጸጥታ ምክር ቤት የአማራ ክልል ያለበትን የፀጥታ ሁኔታ በጥልቀት በመገምገም የወያኔን ዳግም ወረራ ለመቀልበስና ለመከላከል የውስጥ አንድነትን ማጠናከር፣ ሰላምና ደህንነትን መጠበቅ ቁልፍ ጉዳይ ነው ብሎ ያምናል። ህዝባችን ዳግሞ ለወያኔ ወረራ ለጥቃት እንዳይዳረግ እቅድሚያ ሰጥቶ እንደወትሮው ሁሉ የፀጥታ መዋቅሩ፣ ደጀኑ ህዝብ የራሱን ኃላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መሆን እንዳለበት አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡

በመሆኑም በአንድ በኩል ከፌደራል የጸጥታ መዋቅር ጋር በመቀናጀት ከወያኔ የሚሰነዘርብንን ጥቃት ለመከላከል በተጠንቀቅና በዝግጁነት መቆም፤ በሌላ በኩል ደግሞ በውስጣችን ለወያኔ ሴራ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥሩትን ህገ-ወጦችንና ስርዓት አልበኞችን በመቆጣጠር የክልላችን ሰላምና ደህንነት ማስጠበቅ ግንባር ቀደም የትኩረት አቅጣጫ እንዲሆኑ ወስኗል፡፡

ስለሆነም የክልሉ የጸጥታ ምክር ቤት በየደረጃው የጸጥታ ግብረ ሀይል አቋቁሞ ህገ-ወጥነትን ለመቆጣጠርና ህግን ለማስከበር ተገቢ ነው ያላቸውን ህጋዊ ርምጃ እንዲወስድ አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡

በመሆኑም የክልላችን ህዝብ፣ ወጣቶች ፣ የገጠርና የከተማ ኗሪዎች ሰላምና ደህንነታችን ለመጠበቅ እና የውስጥ አንድነታችን ለማጠናከር የፀጥታ መዋቅሩ በሚወስደው እርምጃ ሁሉ ተባባሪ እንድትሆኑ ጥሪያችን እናስተላልፋለን፡፡

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የፀጥታ ምክር ቤት ግንቦት 5/2014 ዓ.ም ባህርዳር

Exit mobile version