Site icon ETHIO12.COM

የአማራ፣የትግራይና የኤርትራ “ቀይ መስመሮች” የሰላም የዜሮ ድምርና መንግስትና ዓለም ወዴት?

መንግስት ትህነግ እንዳይቀጠቅጠው ፈርቶ እርዳታ እንዲገባ የፈቀደ በመሆኑ ወደ ውጊያ መግባቱ ብዙም ጥቅም አለው ብለው እንደማያስቡ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ለዚህ አባባል ቃል በቃል መልስ ባይሰጥም ” ዛሬ ላይ ምንም ሃይል ኢትዮጵያን መተንኮስ እማያስበበት፣ ካሰበም ምነው ባላደረኩት እሰከ ሚልበት ደረጃ የሚዘልቅ ምላሽ ይሰጠዋል” ሲል በጥቅሉ አስታውቋል። ይህን ያስታወቁት የኮሙኒኬሽን ሃላፊው ሲያጠቃልሉ ” የኢትዮጵያ ሕዝብ አሳብ አይግባህ” ነበር ያሉት። ትህነግ ሰራዊት አጠናክሮ በክረምት በሃይል ይገቡኛል ያላቸውን ስፋራዎች መልሶ ለመያዝ ማቀዱ በተደጋጋሚ ቢገለጽም በመንግስት በኩል ተመጣጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ቁመናና ብቃት ስለመኖሩ እየተነገረ ነው። በየአቅጣጫው ያለው ሃይልም ዝግጁ መሆኑንን እያስታወቀ ነው። ሰራዊቱም ቀደም ሲል የተፈጸመበት በደል ዛሬ ድረስ የሻረለት እንዳልሆነ በልዩ ስሜት እያስታወቀ ነው።

የአማራ ክልል መሪ ዶክተር ከፍያለ ” ወልቃይት ለአማራ ቀይ መስመር ነው። ለድርድር አይቀርብም” ሲሉ በይፋ አስታውቀዋል። ቀደም ሲል አሁን ወልቃይትን እያስተዳደረ ያለው አካልም ” በጉልበት የተወሰደ መሬት በጉልበት ተመልሷል” ሲሉ ድርድር እንደማይታሰብ በተደጋጋሚ አመልክቷል። የትግራይ ክልል መሪ ዶክተር ደብረጽዮንም ሰሞኑንን ለድርድር የማይቀርቡ ሲሉ በዝርዝር ካስቀመጧቸው ነጥቦች መካከል አንዱ “ወልቃይት ለድርድር አይቀርብም” የሚለው ሃሳብ ነው። ትህነግ ስልጣን ሲይዝ “ምዕራብ ትግራይ” ያለው ማለት ነው።

ክልሎቹ አቋማቸውን “በቀይ መስመር” ቢያስታውቁም የፌደራል መንግስቱ ከትህነግ ጋር የሚደራደረው ምን ዓይነት ሁኔታዎች ሲሟሉ እንደሆነ የሚያጠና ኮሚቴ ተቋቁሞ እያጠና እንደሆነ አመልክቷል። ይህ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የሚመራው ኮሚቴ ግፋ ቢል በሁለት ሳምንታት ውስጥ ለብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የጥናቱን ሪፖርት እንደሚያቀርብ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ለፓርላማ ሲያታውቁ ነው የተሰማው።

“ኮሚቴው ሰላሙን በሚመለከት ኢትዮጵያ ምን ምን ትፈልጋለች? ምን ሲሳካ ነው የምንደራደረው? እንዴትስ ነው የምንነጋገረው? የሚለውን ጉዳይ ሲያጠና መቆየቱን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አመልክተዋል። ይህን ያሉት በድብቅ ድርድር ስለመኖሩ ተጠይቀው ህዝብ ሳያውቅ የሚደረግ ድርድር እንደማይኖርና ሁሉም ነገር የሚሆነው እንደ አገር ኢትዮጵያን በሚጠቅም አግባብ ብቻ መሆኑን በገለጹበት ወቅት ነው።

ዶክተር ደብረጽዮን ይህንኑ አስመልክቶ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ” እስካሁን ድርድር ውስጥ አልገባንም።ወደ ድርድር የምንገባ ከሆነ ግን ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ስምምነቱን የተቀበልን ጊዜ ያሳወቅነውን አቋም አንቀይርም።በወቅቱ የያዝነው አቋም ለድርድር የሚቀርብ አይደለም” ብለዋል። አቋም ያሉትን ሲዘረዝር “የትግራይ ህዝብ ወደፊት ሪፈረንደም ማካሄድ አለበት የሚለው አቋማችን ለድርድር የሚቀርብ አይሆንም” ሲሉ ትግራይ ሪፈረንደም ለማካሄድ እንደምትፈልግ አስታውቀዋል። ቀጥለውም “የትግራይ ሉዓላዊ ግዛት ጉዳይ ቢያንስ ከጦርነቱ በፊት ወደ ነበረበት መመለስ አለበት።ያ ማለት በህገ መንግስቱ የምትታወቀዋ ትግራይ ማለቴ ነው” ሲሉ “ምዕራብ ትግራይ” በተባለው አዲስ አከላል ውስጥ የተካተቱት የወልቃይት ጠገዴ ምድር ለድርድር እንደማይቀርብ አመልክተዋል።

“ሌላው የትግራይ ሰራዊት ጉዳይ ለድርድር አይቀርብም።ሰራዊታችን ትጥቁን አይፈታም።በህግ በስርዓት የሚባል ነገር አይሰራም፤አልፎበታል።” ሲሉም ዋና ዋና ጉዳያቸውን በይፋ አመልክተዋል። አሁን ባለው ህገ መንግስት መሰረት ወልቃይትን ማካለል ለድርድር አይቀርብም ሲሉ በህገመንግስቱ የክልል የጸጥታ ሃይል መታጠቀ የማይገባውን መሳሪያና ትጥቅ አስመልክቶ ” ህግ አይሰራም” ሲሉ ሁለቱን እንዲያስታርቁ ጥያቄ አልቀረበላቸውም።

የአማራ ክልል በተደጋጋሚ እንዳስታወቀውና በወላቅይት ጠገዴ ጉዳይ ድርድር አያደርግም። ምን ነገር የመስሚያ ጆሮ የለውም። ዛሬ ላይ ፋኖናና የአካባቢ ሚሊሻ አደረጃጀትን ሳይጨምር በመቶ ሺህ የሚቆጠር ልዩ ሃይል ማደራጀቱን፣ የአገር መከላከያ ሰራዊት ሜካናይዝድ ሃይል በተጠንቀቅ በቆመበት የድንበሩ አካላይ ትህነግ “ወልቃይት ቀይ መስመሬ ናት” ሲል ላስታወቀው አቋሙ ” አይሆንም”የሚል መልስ ሲሰጠው አቶ ጌታቸው ረዳ እንዳሉት በሃይል ማስመለስ ይቻለዋል ወይ የሚለውን ጉዳይ ዛሬ ላይ አከራካሪ አይመስልም።

ትህነግ ሰራዊት አጠናክሮ በክረምት በሃይል ይገቡኛል ያላቸውን ስፋራዎች መልሶ ለመያዝ ማቀዱ በተደጋጋሚ ቢገለጽም በመንግስት በኩል ተመጣጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ቁመናና ብቃት ስለመኖሩ እየተነገረ ነው። በየአቅጣጫው ያለው ሃይልም ዝግጁ መሆኑንን እያስታወቀ ነው። ሰራዊቱም ቀደም ሲል የተፈጸመበት በደል ዛሬ ድረስ የሻረለት እንዳልሆነ በልዩ ስሜት እያስታወቀ ነው።

በዚህ ሁሉ ውስጥ የሰላም ድርድሩ እንዴት ሊሄድ እንደሚችል ለመገመት የሚቸገሩ እንደሚሉት የጎንደር ዩኒቨርስቲን ጥናት ይፋ ያደረገው፣ ከወልቃይት ጠገዴ የስደት ተመላሽ ነዋሪዎች እንደተደመጠው ከሆነ ሰፊ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ከትግራይ የተለያዩ አካባቢዎች ወደ ተጠቀሱት አካባቢዎች የሰፈሩ ሲሆን በተመሳሳይ በርካታ የአካባቢው ተወላጆች እንዲሰደዱና እንዲባረሩ ተደርገዋል። በርካቶች የደረሱበት እንደማይታወቅ ተመልክቷል። የውጭ ሚዲያዎችም አሁን ላይ አካባቢው በሰው ልጆች ላይ ወንጀል የተፈጸመበት ምድር እንደሆነ እየመሰከሩ ነው። በዚህ መነሻ አካባቢውን በሪፈረንደም አግባብ እንኳን መፍትሄ ለመስጠት ዛሬ ላይ በአማራ ክልል ዘንዳ ቀልድ ነው።

ከግጭቱ ጋር በቀጥታ አብራ የምትነሳዋ ኤርትራ በይፋ ባወጣቸው መግለጫ ትህነግ በአፍሪካ ቀንድ ቀውስ ለመፍጠር በኤርትራ ላይ ጦርነት ማወጁን አስታውቆ ኤርትራ በሁሉም ረገድ ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ እንደሆነች ከረር ባለ ቃል ማስታወቋ አይዘነጋም።

ትግራይን የሚያስተዳድረው አካል ኤርትራን አስመልክቶ ያለውን አቅም በመጠቀም ያለውን መንግስት እንደሚያስወግድ በይፋ እያስታወቀ፣ አልፎ አልፎም ግጭት መኖሩና ድል እንደተቀዳጀ እያስታወቀ ነው። ቀደም ሲል ጀምሮ እንደሚገለጸው የኤርትራን ደጋማ አካባቢዎች በመያዝ ታላቋን ትግራይ የመገንባት ዕቅድ እንዳለ ሲገለጽ ነበር።

የኢርትራን መንግስት መንቀል እንደሚችሉ ቢገልጹም ከፌደራል መንግስት ጋር ምንም ዓይነት ድርድር እየተደረገ እንዳልሆነ ዶክተር ደብረርጽዮን ሲያስታውቁ እግረመንገዳቸውን “ኤርትራ ከትግራይ ክልል የያዘቻቸውን አካባቢዎች እስካሁን አልለቀቀችም” ሲሉ ተደምጠዋል። መንግስት ይህን አስመልክቶ ምንም ያለው ነገር የለም። ቀደም ሲል ግን በኢህአዴግ ማዕከላዊ ኮሚቴ አቶ መልስ የፈረሙት የአልጀርሱ ስምምነት ተፈጻሚ እንዲሆን ከውሳኔ ላይ የተደረሰውን ስምምነት መንግስት እንደሚቀበል ማስታወቁ አይዘነጋም።

ኢህአዴግ ከመፍረሱ በፊት ህዝብ የጠየቀውን ለውጥ በግድ መቀበሉን ሲያውጅ አቶ መለስ ዜናዊ የፈረሙት ይግባኝ የሌለው የአልጀርሱ ስምምነት ወደ ተግባር እንዲለወጥ በሙሉ ቃል መወሰኑን ለሕዝብ ይፋ ማድረጉ ይታወሳል። ዶክተር ደብረጽዮን የቦታዎችን ስም ስላልዘረዘሩ የኤርትራ ወታደሮች የያዙዋቸው አካባቢዎች አወዛጋቢዎቹን ስፍራዎች ይሁን ተጨማሪ ግልጽ አይደለም።

ኤርትራ በተደጋጋሚ እንዳስታወቀችው የአልጀርሱ ስምምነት ላይ በተጠቀሰው መሰረት ወደ ተግባር መሸጋገር እንጂ ሌላ ድርድርም ሆነ አማራጭ “ቀይ መስመር ነው” ብላለች።

አማራና ትግራይ ክልል በወልቃይት ጠገዴ ጉዳይ ያሰመሩት ቀይ መስመር፣ ኤርትራና በማድመና አካባቢው ያሰመረችው ቀይ መስመር፣ እንዲሁም በአማራና በትህነግ መካከል የተፈጥረውና ምን አልባትም በቀላሉ ሊረሳ የማይችለው ቁስል አንድ ላይ ተዳምሮ የሰላሙን እሳቤ የዜሮ ድምር እያደረገው መሆኑ በስፋትና በግልጽ እየተነገረ ነው።

ይህ ሁሉ ቀይ መስመር ሲሰመር ከጦርነቱ በሁውላ በቁጥር እጅግ የበዛ ሃይል መገንባቱን፣ በጥራት፣ በቴክኖሎጂ፣ በየብስ፣ በውሃና በምድር ሃይሉን እንዳዘመነ መንግስት በይፋ በየቀኑ እያስታወቀ ነው። ቀደም ሲል ከነበረበት የመመጣጠን ችግር መላቀቁን ተረት እንዳደረገ የሚናገረው መንግስት በጦርነት ፈተና ይገጥመኛል የሚል ስጋት እንደሌለው እያስታወቀ የራሱ ቀይ መስመር አስምሯል። ይህም ቀይ መስመር ከማናቸውም አካባቢም ሆነ አካላት የሚሰነዘር ትንኮሳ ነው።

ሊስማሙ ይገባል የሚባሉት ሃይሎች በቀይ መስመር አቋማቸውን “ሕዝብ ብዥታ እንዳይፈጠርበት” በሚል ሲያስታውቁ አብሮ እየተሰማ ያለው የውጪው ጫናና ጉትጎታ መላላቱ ነው። በውጭ ሃይሎች ፍላጎትና ዝንባሌ ላይ የተንጠለጠለው የኢትዮጵያ የውስጥ ፖለቲካ ትኩሳት ዛሬ ላይ አዲስ ጥርጊያ ላይ እንዳለ ምልክት እየታየ ነው።

ፍሬን ይዞ የነበረው ዓለም ባንክ ፍሬኑንን በግማሽ ለቋል። የአውሮፓ አገራት በጋራ የያዙትን አቋም በማላዘብ ትብብር እያሳዩ ነው። ሲራገሙ የነበሩትና በሚዛን አልባነት የሚታወቁ የተባበሩት መንግስታት የተለያዩ ሃላፊዎች ምስጋና እያቀረቡ ነው። አውሮፓ ህብረት የፖለቲካና የድህንነት አምባሳደሮቹን ልኳል። ባህር አልባዋ ኢትዮጵያ በአውሮፓ ህብረት ሙሉ ወጪ በቀይ ባህር ላይ የተቋቋመውን ሀገወጥ ተግባራትና የመሳሪያ ዝውውር እንድቶጣጠር ሃላፊነት ወስዳለች። አብይ አሕመድ የባህር ሃይልን ዳግም ሲመሰርቱ “እብድ” ያሉዋቸው ነበሩ።

ዋናዋ የጠብ አጋፋሪ ስትባል የነበረችው አሜሪካ ከዩክሬንና ሩሲያ ጦርነት በሁዋላ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ አፍሪካን ላለማጣት ኢትዮጵያ ላይ ያሳየችውን መገልበጥ ተከትሎ ከላይ የተዘረዘሩት አገራትና ተቋማት ያሳዩትን ወደ ቀልብ የመመለስ ውሳኔ ተከትሎ አውሮፓ ህብረትም በይፋ የአቋም መለሳለሱን ይፋ ለማድረግ ከጫፍ መድረሱ እየተሰማ ነው። በቅርቡ የህብረቱ የፖለቲካና የደህነት አምባሳደሮችም አዲስ አበባ መግባታቸው፣ እንዲሁም የአፍሪካ ህብረት ዓለም በሙሉ የአፍሪካ ህብረት ወኪል ኦባ ሳንጆ እያከናወኑት ላለው ተግባር ሙሉ ደጋፍ እንዲሰጥ መጠየቁ … አሁን ላይ እየታዩ ያሉ አበይት ጉዳዮች ናቸው።

የአውሮፓ አገራት በተናጠል ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን ግንኙነትና ትብብር እያሻሻሉ ባለበት ወቅት፣ አውሮፓ ህብረትም አቋሙን በተቋም ደረጃ ሊያሻሽል ዳር በደረሰበት፣ መንግስት ለሰብአዊ እርዳታ ሲባል የወሰደው አቋም በሁሉም ወገኖች አሜሪካን ጨምሮ በበጎ በሚነሳበት፣ የአፍሪካ አገራት ሩሲያን መደገፋቸው አሜሪካ ( አፍሪካን አልከስርም) ስትል የያዘችውን አቋም በይፋ እንድትቀይር መገደዷ፣ መንግስት የመከላከያ አቅሙን ማዘመኑና የመሳሰሉት ጉዳዮች ተዳምረው የዲፕሎማሲ አውዱ መሻሻል ማሳየቱ በይፋ እየታየ ዶክተር ደብረጽዮን ” ጦርነት ሞክረናቸው ነበር” ሲሉ መንግስት ተንቦቅቡቆ እርዳታ እንዲገባ መፍቀዱን ተናግረዋል።

መንግስት ትህነግ እንዳይቀጠቅጠው ፈርቶ እርዳታ እንዲገባ የፈቀደ በመሆኑ ወደ ውጊያ መግባቱ ብዙም ጥቅም አለው ብለው እንደማያስቡ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ለዚህ አባባል ቃል በቃል መልስ ባይሰጥም ” ዛሬ ላይ ምንም ሃይል ኢትዮጵያን መተንኮስ እማያስበበት፣ ካሰበም ምነው ባላደረኩት እሰከ ሚልበት ደረጃ የሚዘልቅ ምላሽ ይሰጠዋል” ሲል በጥቅሉ አስታውቋል። ይህን ያስታወቁት የኮሙኒኬሽን ሃላፊው ሲያጠቃልሉ ” የኢትዮጵያ ሕዝብ አሳብ አይግባህ” ነበር ያሉት።

መንግስት ይፋ ያደረገውና ቢበዛ በሁለት ሳምንት ውስጥ ጥናቱን የሚያቀርበው ኮሚቴ ከሚያካትታቸው አንድ ዋና ጉዳይ በትግራይ ህገመንግስቱ ከሚፈቅደው ውጪ ያደራጀውን ሃይልና የታጠቀውን ትጥቅ መፍታትን አስመልክቶ የመንግስት ቀይ መስመር እንደሆነ ተሰምቷል። መንግስት፣ ክልሎችና ኤርትራ ሁሉም የራሳቸውን ቀይ መስመር ያሰመሩባት የሰሜኑ ጉዳይ እንዴት ወደ ሰላም ያምራ? ለሚለው ጥያቄ ይህ ነው የሚል የመግባቢያ አሳብ የሚያቀርብ የለም። የትግራይ ክልል በዚህ መልኩ መቀጠል ስለማይችል ጦርነቱ አይቀሬ መሆኑንን በርካቶች ያምናሉ። እንደውም ትህነግ ለምን እስካሁን ዝም አለ? በሚል የትህነግን ሃይል የድል ዜና በጉጉት የሚጠብቁ በርካታ ናቸው። ህዝብ ግን ሰላም ይፈልጋል።

Exit mobile version