ETHIO12.COM

ለትግራይ እርዳታ በጫኑ ተሽከርካሪዎች የተሸሸገ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ አፋር ኬላ ተያዘ

ዛሬ የተያዘውን ጨምሮ በመቆጣጠሪያ ጣቢያ በአንድ ሳምንት ውስጥ ከ18 ሚሊዮን ብር በላይ ጥሬ ገንዘብ ሰብአዊ እርዳታ በጫኑ መኪኖች ላይ በተደረገ ፍተሻ መያዙን አስታውቀዋል

ሰብአዊ እርዳታ በጫነ ከባድ ተሽከርካሪ በሕገወጥ መንገድ ሲዘዋወር የነበረ ከ7 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ መያዙን በአፋር ክልል በጉምሩክ ኮሚሽን የሰመራ ቅርጫፍ ሰርዶ መቆጣጠሪያ ጣቢያ አስታወቀ።

የመቆጣጠሪያ ጣቢያው አስተባባሪ ኮማንደር አህመድ ሳልህ ለኢዜአ እንደገለጹት የእርዳታ እህል ሲጭኑ የነበሩ ከባድ ተሽከርካሪዎች ከዚህ በፊት ነዳጅና ጨውን ጨምሮ የተለያዩ ህገወጥ እቃዎችን ለማሳለፍ ይሞክሩ ነበር።

ይህን ድርጊታቸው በፍተሻ ጣቢያው ሰራተኞች ጥብቅ ቁጥጥር ሲከሽፍ ፊታቸውን ወደ ህገወጥ ብርና ልዩልዩ ጌጣጌጦችን የማዘዋወር ስራ መግባታቸውን አብራርተዋል።

የመቆጣጠሪያ ጣቢያው ሰራተኞችና አመራሮች እየተለዋወጠ የመጣውን ህገወጥ ዝውውር ለመቆጣጠር በፈጠሩት መናበብ ተጨባጭ ውጤት እየታየ ለመሆኑ ሰሞኑ በጣቢያው የተያዙት ህገ ወጥ ብሮች በቂ ማሳያ ናቸው ብለዋል።

ዛሬም ከአዲስ አበበ ሰብአዊ እርዳታ ጭነው ይጓዙ የነበር ሁለት ተሽከርካሪዎች ላይ በተደረገ ፍተሻ ከ7 ሚሊዮን 900ሺ ብር በላይ በፍተሻ መያዙን ገልጸዋል።

ከዚህም ውስጥ የመጀመሪያው 2 ሚሊዮን 85ሺ 200 ብር ዛሬ ጧት ሁለት ሰአት ኮድ3-64879 ኢ/ት ተሳቢ 25350 በሆነ ከባድ መኪና ላይ በጣቢያው ፈታሾች ገንዘቡ መያዙን አብራርተዋል።

በተጨማሪም ኮድ3-12806 ኢ/ት ተሳቢ 06037 በሆን ተሽከርካሪ ከጧቱ 4 ሰአት በጣቢያው ሰራተኞች በተደረገ ፍተሻ 5ሚሊዮን 815ሺ 400 ብር መያዙን ተናግረዋል።

ዛሬ የተያዘውን ጨምሮ በመቆጣጠሪያ ጣቢያ በአንድ ሳምንት ውስጥ ከ18 ሚሊዮን ብር በላይ ጥሬ ገንዘብ ሰብአዊ እርዳታ በጫኑ መኪኖች ላይ በተደረገ ፍተሻ መያዙን አስታውቀዋል።

አሽከርካሪዎቹ በቁጥጥር ስር ውለዉ ተጨማሪ ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሚገኘም የጣቢያ አስተባባሪ ተናግረዋል። ነዳጅና መሳሪያ የጫኑ ህገወጦች በዕርዳታ ስም ሲነግዱ በተደጋጋሚ መያዝቸው ይታወሳል። ሞንጆሪኖ የሚባሉት የትህነግ አመራር እንዲህ ያለውን ተገባር እንዲበረታታ በእቅድ እንደሚሰራ በትግርኛ ቋንቋ የተናገሩትን ቪዲዮ አስፋው አብርሃ አትሞ እንደነበር ይታወሳል።

Exit mobile version