Site icon ETHIO12.COM

የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሰላም ንግግር በአስቸኳይ እንዲጀመር ድጋፉን እንዲያደርግ ተጠየቀ

የትግራይ፣ የአፋርና የአማራ ክልል አካባቢዎች ነዋሪ የሆኑ ዜጎች እየገጠማቸው ያለውን ችግር መቅረፍ እንደሚገባ፤ በተለይም የሰብዓዊ ድጋፍ አስተማማኝ እና ዘላቂ በሆነ መንገድ ለማድረስ ይቻል ዘንድ፣ እንዲሁም የመሰረተ ልማት እና የመሰረታዊ አገልግሎቶችን ዳግም ስራ ለማስጀመር አስቻይ የሆነ ሁኔታ በፍጥነት ለመፍጠር፤ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ በአጭር ጊዜ ላይ መድረስ

የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የአፍሪካ ሕብረት የጀመረው የሰላም ጥረት እንዲሳካ ድጋፉን እንዲያደርግ ተጠየቀ

ነሐሴ 11 ቀን 2014 (ኢዜአ) የኢትዮጵያ መንግስት ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የአፍሪካ ሕብረት የጀመረው የሰላም ጥረት እንዲሳካ ድጋፉን እንዲያደርግ ጠየቀ።

መንግስት በሕብረቱ ማዕቀፍ የሚካሄደው የሰላም ንግግር በአስቸኳይ እንዲጀመር ከአህጉራዊው ተቋም ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑን ገልጿል።

የኢትዮጵያን መንግስት መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ላደረጉ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት በሰሜን ኢትዮጵያ ባለው ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ዛሬ ማብራሪያ ሰጥቷል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የብሔራዊ ደህንነት አማካሪ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን እና የፍትሕ ሚኒስትር ዶክተር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ ለዲፕሎማቶቹ ገለጻ አድርገዋል።

ማብራሪያው መንግስት ሰላም ለማምጣት እያደረጋቸው ያላቸው ጥረቶች፣ የሰብአዊ ድጋፍ አቅርቦት ተደራሽነትና የመሰረታዊ አገልግሎቶችን ዳግም ማስጀመር ዙሪያ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ያተኮረ ነው።

በማብራሪያው ላይ መንግስት የሰላም አማራጭ አብይ ኮሚቴ የሰላም አማራጭን በዘላቂነት እውን ለማድረግና በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል፣ በተለይም የግጭት ሰለባ እና ተጋላጭ በሆኑ የትግራይ፣ የአፋርና የአማራ ክልል አካባቢዎች ነዋሪ የሆኑ ዜጎች እየገጠማቸው ያለውን ችግር መቅረፍ እንደሚገባ፤ በተለይም የሰብዓዊ ድጋፍ አስተማማኝ እና ዘላቂ በሆነ መንገድ ለማድረስ ይቻል ዘንድ፣ እንዲሁም የመሰረተ ልማት እና የመሰረታዊ አገልግሎቶችን ዳግም ስራ ለማስጀመር አስቻይ የሆነ ሁኔታ በፍጥነት ለመፍጠር፤ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ በአጭር ጊዜ ላይ መድረስ እንደሚገባ ኮሚቴው መወያየቱ ተገልጿል።

ሂደቱን ለማፋጠን ወደ ተኩስ አቁም ስምምነት ሊያደርስ የሚችል እና ለቀጣይ የፖለቲካ ውይይቶች መሰረት የሚጥል የሰላም ምክረ ሃሳብ ላይ ውይይት በማድረግ የምክረ ሃሳብ ሰነዱን ማጽደቁንና ኮሚቴው ይህ ምክረ ሃሳብ በተቻለ ፍጥነት ለአፍሪካ ሕብረት ከፍተኛ ወኪል እንዲቀርብ መወሰኑን አመልክቷል።

የሕብረቱ ሰላም ጥረት በሚደግፉ አካላት ትብብር በመታገዝ በአጭር ጊዜ ዘላቂ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ለመድረስ የሰላም ምክረ ሃሳቡን በተመለከተ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ማብራሪያ መስጠት አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱ ተገልጿል።

ኮሚቴው ወደ ተኩስ አቁም ስምምነት ሲገባ በሚፈጠረው አስቻይ ሁኔታ፣ መሰረታዊ አገልግሎቶችን በተቻለ ፍጥነት መልሶ ማቅረብ ይቻል ዘንድ፣ አስፈላጊ ቅደም ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑ በማብራሪያው ወቅት ተገልጿል።

የአፍሪካ ሕብረትም የሰላም ንግግሩ በአስቸኳይ ተጀምሮ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ መድረስ ይቻል ዘንድ፣ የሰላም ንግግሩ የሚካሄድበትን ቦታ እና ጊዜ በፍጠነት ወሰኖ ንግግሩ እንዲጀመር፣ ይህን ማድረግ ይቻል ዘንድ ከአፍሪካ ህብረት ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑም ተነግሯል።

ENA

Exit mobile version