Site icon ETHIO12.COM

የትግራይ ሕዝብ ይህን “ደም-የማይጠግብ የሽብር ቡድን” አሽቀንጥሮ እንዲጥል አብን ጠየቀ፤ ድጋፍ እንደሚያደርግም ገለጸ

በመሆኑም ልጆችህን ከጉያህ እየነጠቀ ፣ ጥሪትህን እያሟጠጠ እና አግቶ በመያዝ ከሌሎች ኢትዮጵያውን ጋር በአንድነት እና በሰላም እንዳትኖር ጋሬጣ የሆነብህን ደም-የማይጠግብ የሽብር ቡድን ከራስህ ላይ አሽቀንጥረህ በመጣል ራስህን ነጻ እንድታወጣ ጥሪያችንን እያስተላለፍን ፣ ከሽብር ቡድኑ እገታ ነጻ ለመውጣት በምታደርገው ተጋድሎ ድጋፋችን እንደማይለይህ ከወዲሁ እናስታውቃለን፡፡

ሙሉ መግለጫው እንደሚከተለው ቀርቧል፦

አሸባሪው እና ተስፋፊው የትግራይ ወራሪ ኃይል የከፈተውን 3ኛ ዙር የወረራ ጦርነት አስመልክቶ ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ።

የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጭ ግንባር (ትሕነግ) በምስረታ ሰነዱ የአማራን ሕዝብ በጠላትነት የፈረጀ እና የአማራን ሕዝብ ማኅበራዊ እረፍት መንሳት የሚል ፋሽስታዊ የፖለቲካ ፕሮግራም ቀርጾ እና ከአማራ ዋና ዋና ግዛቶች ውስጥ ለም እና ስትራቴጅካዊ ጠቀሜታ ያላቸው ቦታዎች ወደ “ታላቋ ትግራይ” ለማካተት በማወጅ ደደቢት በርሃ መውረዱ ይታወቃል፡፡ ቡድኑ የሽምቅ ተዋጊ ከነበረበት ወቅት ጀምሮ እጅግ በተጠና መንገድ የነቁና ተሰሚነት ያላቸውን አማሮችን በመግደል ፣ ጅምላ ግድያዎችን በመፈጸም እና በመሰወር የዘለቀ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ በለስ ቀንቶት ከ1983 ዓ.ም ጀምሮ ከአጋሮቹ እና ምስለኔዎቹ ጋር ሆኖ ኢትዮጵያን የመግዛት ሥልጣን እጁ ላይ ከወደቀበት ጊዜ ጀምሮ ደግሞ የአማራን ሕዝብ የማጥፋት ፍላጎቱን መዋቅራዊ ፣ ተቋማዊ እና የሕግ መሰረት እንዲኖረው በማድረግ አማራ ጠልነትን በፊታውራሪነት ሲመራ ቆይቷል፡፡

በአማራ ጥላቻ አዕምውን የሳተው የትሕነግ ቡድን ባቆመው ሕገ-መንግሥታዊ ሥርአት እና የአስተዳደር መዋቅር በሁሉም የሀገራችን አካባቢዎች የአማራ ሕዝብ ከስደተኛ ሰዎች ያነሰ መብት እንዲኖረው ተደርጎ ለማያቋርጥ ጭፍጨፋ ፣ መፈናቀል እና የንብረት ውድመትና ዘረፋ እንዲዳረግ አድርጓል፡፡ የአማራ ሕዝብ በነጻነት የመንቀሳቀስ ፣ በሕይወት የመኖር እና ንብረት የማፍራትና በላቡ ባፈራው ንብረት የመጠቀም መብቱ በሌሎች በጎ ፈቃድ ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ያደረገ ሥርአት ያቆመ እና ለሥርአቱም ጥብቅና የቆመ ድርጅት መሆኑም ይታወቃል፡፡

ቡድኑ በመላ ኢትዮጵያውያን የተባበረ ክንድ እና ትግል ከማዕከላዊ መንግስት ስልጣን ከተወገደ በኋላ መቀሌ በመመሸግ ኢትዮጵያን የመበተን እና የአማራን ሕዝብ የፖለቲካ ኅልውና የማክሰም ግብ በመያዝ ሲሰራ የቆየ ሲሆን ፣ “ታላቋን ትግራይ” እመሰርታለሁ በሚል የቀን ቅዠት ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም እኩለ ሌሊት ላይ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊ ሰሜን እዝ ሁሉም የጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት በመፈጸም ሠራዊታችንን ያረደ ሲሆን ፣ በተመሳሳይ ሰአትም አማራ ክልል ላይ በሁለት አቅጣጫ የወረራ ጦርነት መፈጸሙ ይታወቃል፡፡ በወቅቱ በጀግንነት በተዋጋው የአማራ ሕዝባዊ ሠራዊት ፣ የአማራ ልዩ ኃይል እና የጀግናው መከላከያ ሠራዊት አስደናቂ ጥምረት እና ጀብድ የተሞላበት ተጋድሎ ወረራውን በመቀልበስ የሽብር ቡድኑ የመሸገበት ድረስ በመዝለቅ ፣ ቡድኑ እንዲበታተን ማድረግ መቻሉ ይታወቃል፡፡

የመከላከያ ሠራዊታችን በሰኔ ወር 2013 ዓ.ም ትግራይን ለቆ መውጣቱን ተከትሎ አሸባሪው እና ተስፋፊው ቡድን እራሱን እንደገና በማደራጀት እና በይፋ “ከአማራ ሕዝብ ጋር ሂሳብ እናወራርዳለን” በሚል ፋሽስታዊ መሪ ቃል የሕዝብ ማዕበል አስከትሎ በፈጸመው ጥቃት በአማራ ሕዝብ እና የአፋር ሕዝብ ላይ መጠነሰፊ ፣ በዕቅድ የተመራ እና የተደራጀ ሰብዓዊ ሰቆቃ ያደረሰ ሲሆን ፣ በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የምርመራ ሪፖርት እንደተረጋገጠው በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸሙ ወንጀሎችን እና የጦር ወንጀሎችን ፈጽሟል፡፡ ከህጻን እስከ መነኮሳት ድረስ እህቶቻችን እና እናቶቻችን ላይ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ፈጽሟል ፣ በቡድን ደፍሯል፣ በመቶ ቢሊየኖች የሚቆጠር የግለሰብ እና ሕዝብ ንብረት ዘርፏል ፣ አውድሟል፡፡

በመላው ኢትዮጵያውን ተጋድሎ ፣ በጀግናው ጥምር ጦር እና በጀግናው መከላከለያ ሠራዊታችን በተከፈተው የመልሶ ማጥቃት እና የኅልውና ዘመቻ ጠላት የተከፈተበትን የመልሶ ማጥቃት መቋቋም ተስኖት በየአቅጣጫው ነብስ አውጭኝ ብሎ የፈረጠጠ ቢሆንም ፣ ጠላት በወረራ ከያዛቸው የአማራ እና የአፋር አካባቢዎች (ራያ ፣ አበርገሌ ፣ ጠለምት ፣ ከፊል አዳርቃይ እና አብዓላና በርካታ የአፋር ወረዳዎች) ሙሉ በሙሉ ሳይጸዳ የኅልውና ዘመቻው እንዲቆም በመደረጉ በወረራ ስር የቀረው ሕዝባችን የጠላት የበቀል በትር እንዲያርፍበት ከማድረጉም በላይ ጠላት ድጋሚ ከሰሞኑ የቀሰቀሰውን ጦርነት በወገን መሬት ላይ እንዲያደርግ በር ከፍቷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት እና ጥምር ጦሩ ወደ ትግራይ ዘልቆ ለመግባት እና ጥቃት ለመክፈት ፍላጎት የለውም የሚል ግምት የወሰደው እና ያለጥይት ጩኸት ውሎ ማደር የማይችለው የሽብር ቡድኑ የተዘረጋለትን የሰላም ዘንበባ ረግጦ 3ኛውን የወረራ ጦርነት በሕዝባችን እና ሀገራችን ላይ በይፋ አውጇል፡፡ስለሆነም ፓርቲያችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የሚከተለውን ጥሪ ያስተላልፋል፥

ለተከበርከው የአማራ እና የአፋር ሕዝብ ፤

ምንም እንኳ አሸባሪው እና ተስፋፊው ትሕነግ የሁሉም ኢትዮጵያውያን ጠላት ቢሆንም ፣ የአማራ እና የአፋር ሕዝብ የቡድኑ ወረራ ቀጥተኛ ሰለባ እና ገፈት ቀማሽ በመሆኑ ጦርነቱን የመመከት ድርብ ኃላፊነት ያለበት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ጥቃቱ በተከፈተባቸው ግንባሮች እና ሌሎች አካባቢዎች የሚገኝው ሕዝባችን ለጠላት ፕሮፖጋንዳ ጀሮ ባለመስጠት ፣ ለጥምር ጦሩ እና ለጀግናው መከላከያ ሠራዊታችን ያልተቆጠበ የስንቅ እና የሞራል ድጋፍ እንዲሰጥ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

ለተከበርከው የትግራይ ሕዝብ፤

በስምህ የሚነግደው አሸባሪው እና ተስፋፊው የትሕነግ ቡድን ፣ ከመላው ኢትዮጵያውያን ጋር ያለህን ትስስር ለመበጠስ እና ከኢትዮጵያዊ ማንነትህ ለመንቀል በማያባራ ጦርነት ውስጥ እንዳስገባህ ይታወቃል፡፡ የሽብር ቡድኑ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ በተለይም በአማራ እና በአፋር ሕዝብ ላይ ካደረሰው ጉዳት ያልተናነሰ ጉዳት በትግራይ ሕዝብ ላይ እንዳደረሰ ምስክር እና አስረጅ እንደማያስፈልግህም የታወቀ ነው፡፡ በመሆኑም ልጆችህን ከጉያህ እየነጠቀ ፣ ጥሪትህን እያሟጠጠ እና አግቶ በመያዝ ከሌሎች ኢትዮጵያውን ጋር በአንድነት እና በሰላም እንዳትኖር ጋሬጣ የሆነብህን ደም-የማይጠግብ የሽብር ቡድን ከራስህ ላይ አሽቀንጥረህ በመጣል ራስህን ነጻ እንድታወጣ ጥሪያችንን እያስተላለፍን ፣ ከሽብር ቡድኑ እገታ ነጻ ለመውጣት በምታደርገው ተጋድሎ ድጋፋችን እንደማይለይህ ከወዲሁ እናስታውቃለን፡፡

ለተከበራችሁ ኢትዮጵያውያን ፤

የአሸባሪው እና ተስፋፊው ቡድን ዓላማ ኢትዮጵያን ለመበተን እና መላ ኢትዮጵያውያን እርስ በርስ ለማባላት ቆርጦ የተነሳ ጠላት መሆኑ የታወቀ እና በሁሉም ኢትዮጵያውያን ግንዛቤ የተያዘበት ጉዳይ ቢሆንም ፣ ቡድኑን ልንዋጋው የሚገባው ገና ከመነሻው እንጅ በእያንዳንዳችን በር ላይ ሲደርስ ባለመሆኑ ፤ ሁሉም ኢትዮጵያዊያን የሽብር ቡድኑን እና የሽብር ቡድኑ ተከፋይ ከሆኑ ሚዲያዎች ሃሰተኛ ፕሮፖጋንዳ እራሱን እንዲጠብቅ እና በጀግንነት እየተዋጋ ላለው ጥምር ጦራችን እና ለጀግናው መከላከለያ ሠራዊታችን ሙሉ ድጋፉን እንዲሰጥ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

ለፌዴራል እና ለክልል መንግስታት፤

ሽብርተኛው እና ተስፋፊው የሽብር ቡድን እያሰለሰ በሚከፍተው የወራራ ጦርነት ሀገራችን ኢትዮጵያ እና ሕዝቦቿ በተለይም የወረራው ቀጥተኛ ገፈት ቀማሽ የሆነው የአማራ እና የአፋር ሕዝብ ከፍተኛ ዋጋ እየከፈሉ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ስለሆነም የፌዴራል እና የክልል መንግስታት ተስፋፊው እና ሽብርተኛው የትሕነግ ኃይል በየጊዜው የሚደቅነውን የጦርነት ስጋት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እልባት የሚያገኝበትን እና የሽብር ቡድኑ ኅልውና መክሰምን ግብ ያደረገ የጦር ፣ የዲፕሎማሲ እና የፕሮፖጋንዳ እቅድ ስራ ላይ እንዲያውል ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አዲስ አበባ ፣ ሸዋ ፣ ኢትዮጵያ ነሐሴ 20 ቀን 2014 ዓ.ም

Exit mobile version