ETHIO12.COM

“ልጃችሁ ፋኖ ነው ተብለው ወላጆች ተገድለዋል”ቢቢሲ “የቆቦ ሕዝብ እውነቱን ያውቃል” አቶ ጌታቸው

“እኔ የማውቃቸው ቢያንስ 20 ሰዎች በግፍ ተገድለዋል። የተገደለቡት ምክንያትም የልጅህን መሣሪያ አምጣ፣ ባልሽ የት ነው የተደበቀው? ልጃችሁ ፋኖ ነው? በሚል ምክንያት ነው” ሲል የቆቦ ነዋሪ እማኝነቱን ለቢቢሲ ገልጿል። ትናንት በድምጸ ወያኔ ወቅታዊ መልዕክት ያሰራጩት የትህነግ ከፍተኛ አመራር አቶ ጌታቸው “እውነቱን የቆቦ ህዝብ ያውቀዋል” ሲሉ ተሰምተዋል።

ቀደም ሲል ዘ ጋርዲያን ቆቦ ዳግም ከተወረረች በሁዋላ የተፈጸመውን የመብት ጥሰት በስፋት “የትግራይ አማጺያን” ብሎ የዘገበ ሲሆን ቢቢሲ ተከትሎ የአካባቢውን ሰዎች ቦታና ስም ጠቅሶ በዝርዝር ምን እንደተከሰተ አስነብቧል። በተደጋጋሚ ሚዛን በሳተ ዘገባ ለትህነግ እንደሚደግፉ ያረጋገጡት ሚዲያዎች ከዘገቡት በተቃራኒው አቶ ጌታቸው “የሰሜን ወሎ ሕዝብ እውነቱን ያውቃል” ቢሉም በዝርዝር ወዳጆቻቸው የነበሩት ሚዲያዎች ስለጻፉት ማስተባበያ አልሰጡም።

ትህነግ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ፋኖ የቅርብ ወዳጁ፣ አማራ አካሉ፣ ጦርነቱ ከሰሊጥ ነጋዴዎች ጋር በምሆኑ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደማያገባው በተደጋጋሚ ሲያስታውቅ፣ በተመሳሳይ ከኦነግ ሸኔና ከሌሎች እሱ ካደራጃቸው ጋር በመሆን የጥምር ጥቃት እንደሚያካሂድ ማስታወቁ አይዘነጋምል። የቢቢሲን ዘገባ ከታች ያንብቡ


Tigray rebels tortured and killed civilians in renewed fighting, survivors claim

Tigrayan rebel forces have killed dozens of civilians during their latest occupation of a town in the Amhara region, survivors claim, after fighting resumed last month in the northern area of Ethiopia.


ባለፈው ዓመት ነሐሴ ወር አጋማሽ ላይ መልሶ ያገረሸው ጦርነትን ተከትሎ የትግራይ ኃይሎች ለሁለተኛ ጊዜ በተቆጣጠሯት የሰሜን ወሎ ከተማ ቆቦ ውስጥ የዘፈቀደ ግድያን እና የመብት ጥሰቶችን ፈጽመዋል ሲሉ ነዋሪዎች ተናገሩ።

በሰሜን ወሎ ዞን የራያ ቆቦ ወረዳ ውስጥ የምትገኘው የራያ ከተማ በትግራይ ኃይሎች ቁጥጥር ስር በነበረችበት ከአንድ ወር በላይ ጊዜ ውስጥ ታጣቂዎቹ ግድያ፣ መድፈር፣ ማሰቃየት እና ዘረፋ እንደፈጸሙ ነዋሪዎች ለቢቢሲ ገልጸዋል።

የትግራይ ኃይሎች ወደ ከተማዋ እንደገቡ የአካባቢው ሚሊሻዎች ናቸው ያሏቸውን ንብረቶች ባመጧቸው መኪኖች ጭነው እንደወሰዱ የሚናገሩት ነዋሪ “በርካታ ሰዎችን ገድለዋል። የሚሊሻ አባላት ልጆች ናቸው ያሏቸውን ሴቶች ወደ ጫካ ወስደው ደፍረዋል” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

አሁንም ለደኅንነት ስጋት እንዳላቸው በመናገር ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉት ግለሰቡ በራያ ቆቦ ውስጥ በግብርና ሥራ ይተዳደር የነበረው ወንድሙ በትግራይ ኃይሎች መገደሉን ይናገራል። በአካባቢው ያገረሸውን ጦርነት ሲሸሽ በታጣቂዎቹ ተገድሏል ሲል ገልጿል።

“ታላቅ ወንድሜን እና ጓደኛውን መንገድ ዳር ነው የገደሏቸው። መገደላቸውን የሰማነው አስከሬናቸውን ከቀበሩ ሰዎች ነው።”

ዳግም ባገረሸው የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ከፍተኛ ውጊያ ከተካሄደባቸው አካባቢዎች መካከል ከትግራይ ክልል ጋር የሚዋሰነው የራያ ቆቦ አካባቢ አንዱ ነው።

ከነሐሴ 18/2014 ዓ.ም. ጀምሮ በእዚህ ግንባር ከፍተኛ ጦርነት እንደተደረገ ነዋሪዎች ይናገራሉ። ይህንንም ተከትሎ የትግራይ ኃይሎች አብዛኛውን የራያ ቆቦ አካባቢ ለመቆጣጠር ችለው ቆይተዋል።

ጦርነቱ አሁንም በተለያዩ ስፍራዎች እየተካሄደ ሲሆን፣ ከአንድ ሳምንት በፊት የትግራይ ኃይሎች ከቆቦ ለቀው ቢወጡም በከተማዋ እና በነዋሪዎች ላይ ጉዳት አድርሰዋል ሲሉ ይከሳሉ።

ቢቢሲ ከነዋሪዎች ባሻገር ከሌሎች አካላት እንዲሁም ከአካባቢው አስተዳዳሪዎች ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ያደረገው ጥረት አልተሳካለትም።

የትግራይ ኃይሎችም ቆቦ ውስጥ ተፈጸመ ስለተባለው ጉዳይ ያሉት ነገር ባይኖርም፣ ከዚህ በፊት የቀረቡባቸውን ክሶች በማስተባበል በገለልተኛ ወገን ምርመራ እንዲደረግ መጠየቃቸው ይታወሳል።   

ግድያ እና ሽሽት

የቆቦ ከተማ በህወሓት ተዋጊዎች ቁጥጥር ስር ስትገባ ለሁለተኛ ጊዜ በመሆኑ፣ በርካታ ሰዎች እዚያው ለመቆየት ሲወስኑ ሌሎች ደግሞ ወደ ሌሎች አካባቢዎች ሸሽተው ቆይተዋል።

የትግራይ ኃይሎች ነሐሴ 21/2014 ዓ.ም. ከቆቦ በስተደቡብ 17 ኪሎ ሜትር አካባቢ የምትርቀውን ሮቢት ከተማን ሲቆጣጠሩ በቦታው እንደነበረ የሚናገረው ዓለሙ ተሰማ ታጣቂዎቹ በርካታ ሰላማዊ ነዋሪዎችን መገደላቸውን ይናገራል።

“ቅዳሜ ነሐሴ 21 ሮቢትን ከተቆጣጠሩ በኋላ ብዙ ሰዎችን ገድለዋል፤ በርካቶችንም አሰቃይተውናል” የሚለው ዓለሙ፣ በዕለቱ “በተለይም ወንዶችን ሰብስበው ለረጅም ጊዜ ሜዳ ላይ አንበርክከው አቆይተው ለቀውናል” ብሏል።

ቀን ላይ እንግልት ካደረሱበት በኋላ ቢለቀቅም “በሌሊት መጥተው ድጋሚ በሕይወቴ ላይ አደጋ ደቅነውብኝ ነበር” በማለት ዕለቱን ያስታውሳል።

“ሌሊት 4፡30 ላይ ቤቴን አንኳኩ። ሊገድሉኝ እንደመጡ በመረዳት በመስኮት ዘልዬ ወጣሁ። ከእዚያም በዱር በገደል አድርጌ ሌሊቱን በእግር ተጉዤ በማግሥቱ ወልዲያ መግባት ችያለሁ።”

“እኔ ሮቢት በነበርኩበት ወቅት ብዙ ጓደኞቼ እና ሰላማዊ ነዋሪዎች ከቤታቸው እየተጎተቱ እየወጡ በህወሓት ወታደሮች ተገድለዋል” የሚለው ዓለሙ፣ ሮቢት ውስጥ ብቻ አብዛኞቹን በስም የጠቀሳቸው ቢያንስ 18 ሰዎች መገደላቸውን ተናግሯል።

ዓለሙ በስም እየጠራ የሚገልጻቸው ሟቾች ሰላማዊ ሰዎች በሚሊሻነትም ሆነ በውትድርና ውስጥ ያልተሳተፉ እንደነበሩ የተናገረ ሲሆን፣ የህወሓት ታጣቂዎች ወደ ሮቢት ከመግባታቸው በፊት “ሲቪል ነው የወጋን ስለዚህ ሲቪል መመታት አለበት” በሚል በቀል እንደገደሏቸው ይናገራል።

ከሮቢት በቅርብ ርቀት በምትገኘው አራዱም በተባለች አነስተኛ ከተማም በተመሳሳይ ከ15 በላይ ሰዎች መገደላቸውን አቶ ዓለሙ ተናግሯል። በአራዱም የተገደሉት ሰዎችም በተመሳሳይ ንጹሃን ነዋሪዎች ሲሆኑ በቅርብ የሚያውቃቸው ጓደኞቹም እንደሚገኙበት ገልጿል።

የትግራይ ኃይሎች የራያ ቆቦ አካባቢን ከተቆጣጠሩ በኋላ በተለይ ወንዶችን ኢላማ አድርገው ፈጽመውታል የተባለውን ጥቃት ተከትሎ በርካታ ነዋሪዎች ባገኙት መንገድ ሁሉ ወደ አቅራቢያ ከተሞች መሸሻቸውን አንዲት እናት ለቢቢሲ ገልጸዋል።

በዚህም ሳቢያ በማሳ ላይ ያለ ሰብል መበላሸቱን እና ከአንድ ወር በላይ አስቸጋሪ ጊዜን ማሳለፋቸውን ሁለት ወንድ ልጆቻቸው ወደ ወልዲያ ሄደው የነበሩ እናት ተናግረዋል።

ዘረፋና የመሳሪያ ንጥቂያ

አራጋው በሚል ተለዋጭ ስም እንድንጠቅሳቸው የጠየቁት የቆቦ ነዋሪ የተፈጸመውን ግድያ “ጭካኔ ነው” በማለት ከዚያ ባሻገር በነዋሪዎች ላይ የደረሰው እንግልትና የንብረት ንጥቂያን አምርረው ይናገራሉ።

“ሕጻናት ላይ መሣሪያ ደግነው የታጣቂዎችን ቤት እንዲጠቁሙ በማስገደድ ሲያሰቅቁን ነበር። ዋነኛ የሚፈልጉት ነገር መሳሪያ እና ብር ነው።”

አቶ አራጋው እንዳሉት “መሣሪያ የለንም ወይም ደግሞ መሣሪያ አለው የተባለው ሰው በቦታው እንደሌለ ሲነገራቸው ደግሞ ድብደባ እና ግድያ ይፈጽማሉ” ብለዋል።

ከእዚህም ባለፈ ታጣቂዎቹ ቤት ውስጥ ገብተው መሣሪያ ካላገኙ እና የለንም የሚሉትን ሰዎችን ያላቸውን ገንዘብ እንዲያመጡ ያስገድዱ ነበር በማለት፣ ሁኔታው አስጨናቂ እንደነበር ገልጸዋል።

ነሐሴ 18 ጦርነቱ ዳግም ሲቀሰቀስ ወዲያውኑ ውጊያ ከተጀመረባቸው የራያ ቆቦ ቀበሌዎች መካከል ራማ የሚባለው ዋነኛው ነው። ቢቢሲ ያነጋገረው የአካባቢው ተወላጅ አበበ [ስሙ የተቀየረ] በሰው እና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን ተናግሯል።

አበበ እንደሚለው በጦርነቱ ሂደት የሞቱ ሰዎች እንዳሉ ሆኖ፣ አካባቢውን የህወሓት ወታደሮች ከተቆጣጠሩ በኋላ ሆን ብለው ጥቂት የማይባሉ ንጹሃንን ገድለዋል።

“እኔ የማውቃቸው ቢያንስ 20 ሰዎች በእዚሁ ቀበሌ በግፍ ተገድለዋል። የተገደለቡት ምክንያትም የልጅህን መሣሪያ አምጣ፣ ባልሽ የት ነው የተደበቀው? ልጃችሁ ፋኖ ነው? በሚል ምክንያት ነው” ብሏል።

እነዚህ ሰዎችም የጦርነት ተሳትፎ ያልነበራቸው የአብዛኛዎቹ እድሜም ከ70 ዓመት በላይ የሆኑ አዛውንቶች ናቸው ብሏል።

“የ80 ዓመት እናቴን ሦስት/አራት ጊዜ ቤቷ በመሄድ ‘የልጅሽን መሣሪያ ካላመጣሽ ቤትሽን ዘግተን እናቃጥልሻለን’ ተብላ ወንድሜ ካለበት ተፈልጎ መሣሪያ አስረክቦ ነው እናቴ የተረፈችው” የሚለው አበበ፣ የአርሶ አደሩን ንብረት ከመመገብ እና ከማውደም ባለፈ ግመሎቻቸውን ለእቃ መጫኛ በሚል እንደወሰዱባቸው ገልጿል።

በቀበሌው በተለይ የ5 እና የ6 ዓመት ህጻናትን እንዲሁም አረጋውያንን በመሣሪያ አፈሙዝ እያስገደዱ የሚሊሻ እና ታጣቂ ቤት እንዲጠቁሙ ያደርጓቸዋል። ታጣቂዎቹን ካገኙ በኋላም ሌላ ታጣቂ ጠቁም በሚል ከፍተኛ ድብደባ ይፈጽሙባቸዋል ብሏል ለቢቢሲ በነበረው ቆይታ።

ሌላው የራያ ቆቦ ነዋሪ ሆን ተብለው በትግራይ ኃይሎች ተገድለዋል ስለሚባሉ ሰዎች መረጃ እንደሌለው በመግለጽ፣ የትውልድ አካባቢው በሆነችው ሸወይ ማርያም ተብሎ በምትታወቀው ቀበሌ ውስጥ ግን ጦርነቱ ሲካሄድ ብዙ ሰዎች ተገድለዋል ይላል።

አካባቢውን ለመቆጣጠር በተደረገው በጦርነቱ ወቅት በተተኮሱ ከባድ መሳሪያዎች ቢያንስ ከ10 በላይ ሰዎች መገደላቸውን መስማቱን፣ ከሟቾቹ መካከልም ብዙዎቹ አዛውንቶችና ሕጻናት ናቸውን ተናግሯል።

አካባቢውን በተለይም የገጠሩን ቀበሌ የህወሓት ወታደሮች ከተቆጣጠሩ በኋላ “የአርሶ አደሩን ንብረት እያወደሙ፣ እየወሰዱ እና እየተመገቡ ቆይተዋል” ብሏል።

በምሳሌነት የሚጠቅሰው ቤት ውስጥ የሚገኝን ማንኛውንም ምግብ ነክ ነገር ከመውሰድ ባለፈ የአርሶ አደሩን የቁም እንስሳት በኃይል በመቀማት ለምግብነት እንዳዋሏቸው ይህ ሁኔታም የእራሱን ቤተሰብ ጨምሮ በሌሎችም ሰዎች ላይ እንዳጋጠመ የግለሰቦች ስም ጠቅሷል።

ሁለት ዓመት ሊሞላው የተቃረበው ጦርነት ተሳታፊዎች በትግራይ፣ በአማራ እና በአፋር ክልሎች ውስጥ በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተፈጸሙ ግድያዎችን፣ ጾታዊ ጥቃቶችን እና የንብረት ዝርፊያ እንዲሁም ውድመት በመፈጸም ይከሰሳሉ።

Exit mobile version