Site icon ETHIO12.COM

የሰላም ስምምነቱ ተከትሎ ተያያዥነት ያላቸው ዘገባዎች የሚሠሩበትን መመሪያ ተዘጋጀ

ሀሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግር ለሰላም ሀሳቦች የሚጠቅም ስላልሆነ ሊገታ ይገባዋል ያሉት ዋና ዳይክተሩ፤ መመሪያው በሰላም ስምምነቱ የተቀመጠውን ግዴታ መሠረት አድርጎ የተዘጋጀ ነው። መመሪያውን መነሻ በማድረግም ባለስልጣኑ ሁሉም መገናኛ ብዙኃን የሚኖራቸውን የሞራል፣ የሙያና ሕጋዊ ግዴታዎችን አክበረው እንዲሠሩ በየጊዜው የክትትልና ድጋፍ ሥራ በመሥራት የማስተካከልና ወደ ትክክለኛው መስመር እንዲመጡ የማድረግ ሥራ እንደሚሠራ ገልጸዋል።

መገናኛ ብዙኃን ከሰላም ስምምነቱ ጋር የተያያዙ ዘገባዎችን በምን መልኩ መሥራት እንዳለባቸው የሚጠቁም መመሪያ እየተዘጋጀ መሆኑን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን አስታወቀ።

የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ መሐመድ ኢድሪስ በተለይ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ በሰላም ስምምነቱ ከተጠቀሱ ጉዳዮች አንዱ ስምምነቱን ከሚረብሹ ዘገባዎች መታቀብ የሚለው ይገኝበታል። እንዲሁም የሰላም ስምምነቱን ተከትለው የሚወጡ ዘገባዎችም በመልካም እይታና በሚገባቸው ልክ መዘገብ ይገባል። ከዚህ መነሻ ሁሉም መገናኛ ብዙኃን ከሰላም ስምምነቱ ጋር የተያያዙ ዘገባዎችን በምን መልኩ መሥራት እንዳለባቸው የሚጠቁም፣ ለተቋማቱ አቅም የሚፈጥርና እንደ ማጣቀሻ ሊጠቀሙበት የሚችል መመሪያ በባለስልጣኑ እየተዘጋጀ ነው ብለዋል።

ሀሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግር ለሰላም ሀሳቦች የሚጠቅም ስላልሆነ ሊገታ ይገባዋል ያሉት ዋና ዳይክተሩ፤ መመሪያው በሰላም ስምምነቱ የተቀመጠውን ግዴታ መሠረት አድርጎ የተዘጋጀ ነው። መመሪያውን መነሻ በማድረግም ባለስልጣኑ ሁሉም መገናኛ ብዙኃን የሚኖራቸውን የሞራል፣ የሙያና ሕጋዊ ግዴታዎችን አክበረው እንዲሠሩ በየጊዜው የክትትልና ድጋፍ ሥራ በመሥራት የማስተካከልና ወደ ትክክለኛው መስመር እንዲመጡ የማድረግ ሥራ እንደሚሠራ ገልጸዋል።

መመሪያው በዚህ ሳምንት ውስጥ ተጠናቆ መገናኛ ብዙኃን፣ ሕዝቡና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እንዲያውቀው ይደረጋል ያሉት ኃላፊው፤ ሁሉም መገናኛ ብዙኃን የሰላም ግንባታ ላይ የሚጠቅባቸውን ሚና እንዲወጡ የሚያግዝ መሆኑንም ጠቁመዋል።

የሰላም ጉዳይ የሕዘብ ጉዳይ ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በሰላም መረጋገጥ ላይ መገናኛ ብዙኃን የሚኖራቸው ሚና የማይተካ ስለሆነ ያላቸው ኃላፊነት ከሙያዊ ሥነምግባርና ከሞራልም ጭምር የሚመነጭ መሆን እንዳለበት አመልክተዋል።

የመገናኛ ብዙኃን ሚና የሰላም ስምምነቱ ተሳካቶ ወደ ልማት ለመግባትና ጉዳት የደረሰባቸውን የኅብረተሰብ ክፍሎች እንዲያገግሙ ለማገዝ ምን አወንታዊ ሚና ልጫወት ከሚል እሳቤ የሚመነጭ መሆን ይኖርበታል ብለዋል።

መገናኛ ብዙኃን የሰላም ስምምነቱ ወደ መሬት ወርዶ ሕዝቡ ተጠቃሚ እንዲሆን በኃላፊነት መንቀሳቀስ እንዳለባቸው ጠቁመው፤ ስምምነቱን ከአውዱ ውጪ ባለመተርጎምና አገሪቱ ላይ የነበረው ነባራዊ ሁኔታ እንዲቀየር የሚያግዝ ሥራ ላይ ማተኮር እንዳለባቸው ጠቁመዋል።

እያንዳንዱ የመገናኛ ብዙኃን ተቋም የተጎዱት እንዲበረቱና የማኅበረሰቡ የርስ በርስ መስተጋብር እንዲጠናከር በማድረግ የሰላም ስምምነቱ ከግብ እንዲደርስ የሚጠበቅባቸውን አዎንታዊ ሚና መጫወት እንዳለባቸውም መልዕክት አስተላልፈዋል።

ፋንታነሽ ክንዴ

አዲስ ዘመን  ጥቅምት 30/ 2015 .

Exit mobile version