Site icon ETHIO12.COM

ፈይሳ ሌሊሳ ሸኔን በመቃወሙ እንደ ሃጫሉ?

” ዜናው አስደንጋጭ ነው። ሃጫሉም በተመሳሳይ ማስፈራራት ደርሶበት ነበር። ጀግናውና ጭቆናን ዓለም አደባባይ በቢሊዮን ህዝብ ፊት ገሃድ ያወጣው ፈይሳ ሸኔን በመቃወሙ ሳቢያ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ባሉ ሰዎች ማስፈራራት ከደረሰበትና ይህንኑ ይፋ ካደረገ ምን ቀረ? ታዬ ደንደአ እንዳለው፣ የትህነግ ደጋፊዎች ተስፋ እንደሚያደርጉት ሸኔ በጉያችን ነው ማለት ነው። ጨዋታው ከወለጋ አብዬት አልፎ ድፍን ኦሮሞን የመጫንና ዳግም ለትህነግ አሳልፎ የመስጠት ሩጫ ለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም። ኦሮሞ የሆነ ሁሉ ይህን ጉዳይ ይመርመር። በሃጫሉ የደረሰ ዳግም በሌሎች ጀግኖቻችን ላይ ሊደርስ አይገባም” ሲሉ ቁጣቸውን እየገለጹ ነው።

የኦሎምፒክ የማራቶን ጀግናው አትሌት ፈያሳ ሸኔን ለመዋጋት ባለው ጠንካራ አቋም ምክንያት በአንዳንድ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ባሉ አካላት ጥላቻና ጫና እንደሚደርስበት በይፋ ተናገረ። ሸኔ የዘራፊ ቡድን እንደሆነ፣ ይህ ዝርፊያ የለመደ ቡድን ወደ ሰላም ለመለስ አስቸጋሪ እንደሚሆንም አመልክቷል። ይሁን እንጂ አመራሩ አይታወቅም እንጂ ቢታወቅና የፖለቲካ ግቡ ግልጽ ቢሆን ለሰላማ መነጋገሩ ተገቢ እንደነበር አመልክቷል።

አትሌቱ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጸው፤ እንደ ሀገር ሸኔ በህዝብ ላይ ያደረሰው ተጽእኖ ከባድ ቢሆንም በኦሮሞ ሕዝብ ላይ በተለይ በኦሮሞ አርሶ አደር ላይ የሚፈጽመውን ግፍ ለመናገር እንኳ የሚከብድ ዘግናኝ መሆኑን አመልክቷል።

አትሌቱ በይፋ በዓለም አደባባይ ኦሎምፒክን ካሸነፈ በሁዋላ በወቅቱ የነነበረውን የትህነግ አገዛዝ ሲቃወም ሸኔ ከትህነግ ጋር ተመሳስሎ ያለ ተቃውሞ ተቀምጦ እንደነበር በርካቶች ዛሬ ላይ ሸኔ መሳሪያ ያነሳበት ምክንያት እንደማይገባቸው ሲናገሩ የሚያስታውሱት እውነት ነው።

ሃጫሉ ቀደም በተመሳሳይ ሸኔ ላይ በያዘው አቋም ማስፈራሪያ ይደርሰው እንደነበር ሲገልጽ እንደነበር ይታወሳል። በገሃድ መንግስትን በመቃወም ለሕዝብ ውግናውን በማሳየት የሚታወቀው ሃጫሉ የደረሰበትን የሚያስታውሱ ለአትሌት ሌሊሳ ፈይሳ በተመሳሳይ ስጋታቸውን እየገለጹ ነው።

“ቀደም ሲል የቡድኑ እንቅስቃሴ እና የሚፈጽመው ግፍ በተወሰኑ አካባቢዎች ብቻ ነበረ” ሲል ለአዲስ ዘመን የገለጸው አትሌት ፈይሳ፤ አሁን ላይ ግን ግፉም እንቅስቃሴውም በጣም ስለጨመረ ለጉዳዩ ተገቢ ትኩረት ካልተሰጠ መዘዙ ከተለመደው ይልቅ የከፋ እንደሚሆን አሳስቧል።

“ለአገሪቱ ሰላምና ለሕዝቡ እፎይታ እስከ ሆነ ድረስ ከሸኔ ጋር በሰላማዊ መንገድ በመነጋገር መረጋጋት ከሰፈነ መነጋገር መልካም ነበር። ይሁንና ቡድኑን የሚመራ አካል በውል በማይታወቅበትና የትግሉም ዓላማ ግልጽ ባልሆነበት ሁኔታ ሰላማዊ መንገድ መፍትሄ ይሆናል የሚል እምነት የለኝም” ሲል አትሌቱ የሸኔ ቁመና አመልክቷል። ስጋቱንም ገልጿል።

በተጨማሪም ሰውን በማገት በአንዴ በርካታ ብሮችን እጁ የሚያስገባና የሽፍታነት ባህሪ ያጎለበተ ታጣቂ በድርድር ወደ መደበኛ ኑሮ ይመለሳል ብሎም ማሰብ እንደሚከብደው የተናገረው አትሌት ፈይሳ፤ ከዚህ አንጻር ምናልባት የተወሰኑትን ወደ ሰላም ማምጣት ከተቻለ ቀሪው ላይ የኃይል ርምጃ ማጠናከር እንደሚቻል አስገንዝቧል::

እንደ አትሌት ፈይሳ ማብራሪያ፣ በመጀመሪያው አካባቢ አንዳንድ አካባቢዎች ላይ ሕዝቡን ከቡድኑ ጋር የመፈረጅ አዝማሚያዎች ነበሩ:: በሌላ በኩል ደግሞ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ሆነውም ከሸኔ ጋር የሚሰሩ አካላት አሉ::

በመንግስት መዋቅር ውስጥ ያሉ አመለካከቶች ሸኔን መስመር ለማስያዝ የሚደረገውን እንቅስቃሴ ውስብስብ እንደሚያደርጉት የጠቆመው አትሌቱ፤ ከዚህ አንጻር ሸኔን ለመዋጋት ባለው ጠንካራ አቋም ምክንያት በአንዳንድ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ባሉ አካላት ጥላቻና ጫና እንደሚደርስበትም

በተጨማሪም ቡድኑ ላይ የሚደረገው ኦፕሬሽን በተወሰነ መልኩ ቁርጠኝነት እንደሚጎድለውም ጠቁሟል::

ቀደም ሲል እሱ ባለበት አካባቢ ሲንቀሳቀስ የነበረውን የኦነግ ሰራዊትም ሆነ አሁን ያለውን የሸኔ ቡድን እንደሚያውቃቸው የተናገረው አትሌት ፈይሳ፤ ነባሩ የኦነግ ሰራዊት ቅጠላቅጠልና ሥራሥር እየበላ ለዓላማው ከመንቀሳቀስ ውጪ ሕዝቡን አስቸግሮ እንደማያውቅ ጠቁሟል:: ሆኖም አሁን ያለው የሸኔ ቡድን አባላት ሕዝብን እየገደለና እየዘረፈ የራሱን ምቾት ለመጠበቅ የሚንቀሳቀስ የዘራፊ ስብስቦች ነው ሲል በንጽጽር ገልጿል::

በሌላ በኩል በኢትዮጵያ መንግስትና በሕወሓት መካከል የተደረገው የሰላም ስምምነት የሚደነቅ ነው ያለው አትሌት ፈይሳ፤ ነገር ግን ያ ሁሉ ሕይወት ከመጥፋቱ፣ ንብረት ከመውደሙና ብዙ ዋጋ ከመከፈሉ በፊት ቢሆን ብዙ ችግሮችን መቅረፍ ይቻል እንደነበርም ጠቁሟል::የስምምነቱን ተግባራዊነትና ዘላቂነት ማስጠበቅ ቀጣዩ ትኩረት መሆን እንዳለበትም አሳስቧል::

“ሰይጣን ካልሆነ ሰላም የሚጠላ ሰው አይኖርም” ያለው አትሌት ፈይሳ፤ ሸኔም ቢሆን ለሰላም ተገቢውን ትኩረት በመስጠት ከያዘው መስመር ቢወጣ ለሕዝቡ ጠቃሚ ነው፤ ነገር ግን ሕዝቡ ከዚህ በላይ በዚህ ቡድን መቸገር የለበትም፤ ችግሩን ለመፍታት በቁርጠኝነት መስራት ይገባል ብሏል::

በጋዜጣው ሪፖርተር

አዲስ ዘመን ህዳር 14/2015

Exit mobile version