Site icon ETHIO12.COM

ሸኔ ጉቦ ወስዶ ያፈናቸውን ሰላማዊ ሰዎች ፈታ፤ “የኦሮሞ ጥያቄ ይህ ነው?”

Ethiopia has for years been fighting a rebellion by OLA in western Oromia, the largest and most populous region in the country. (Reuters Archive)

ራሱን የኦሮሞ ነጻ አውጪ በሚል የሚጠራው፣ ነገር ግን መንግስትና ተበዳዮች “ሸኔ” የሚሉት ታጣቂ አግቷቸው ከነበሩ የዳንጎቴ ሰራተኞች ላይ የገንዘብ ጉቦ ተቀብሎ መፍታቱን ቢቢሲ “ምንጮቼ ነገሩኝ” ሲል ዘገበ። ቢቢሲ ቀደም ብሎም እገታው መፈጸሙን በተመሳሳይ “ምንጮች” በሚል ጠቅሶ ዘግቦ ነበር። ጎን ለጎን “የኦሮሞ ያልተመለሰ ጥያቄ ይህ ነው” የሚሉ እየበረከቱ ነው።

ይኸው መቀመጫውን አዲስ አበባ አድርጎ የሚንቀሳቀሰው የእንግሊዙ ቢቢሲ እንዳለው ሸኔ የሚባለው ታጣቂ በተመሳሳይ ሰዎችን እያፈነ በድርድር ጉቦ እንደሚወስድ ተበዳዮችን አስታውሶ አመልክቷል። የክልሉ መንግስትም በዝርፊያ ላይ የተሰማራና ፖለቲካዊ ዓላማ የሌለው ድርጅት እንደሆነ መግለጹ ይታወሳል።

ይህ በንጹሃን ግድያ፣ አፈናና ጉቦ የሚከሰሰው የአንጋቾች ቡድን ለምን ይህ ተግባር እንደሚፈጽም በግልጽ መግለጫ ሰጥቶ አያውቅም። ድርጅቱም ሆነ ታጣቂ ሃይሉ ለየትኛው የኦርሞ ማህበረሰብ እንደቆመ፣ ኦሮሞ ምን እንደጎደለበትና በአሁኑ ሰዓት ምን ፖለቲካዊ ጥያቄ እንዳለው በገሃድ ሰነድ አስደግፎ አቅርቦ አይውቅም። በቢቢ ላይ ቀደም ሲል “ዘረፋ አልፈጽምም” ብሎ ከማስተባበሉና፣ በቪኦኤ በተደጋጋሚ “እኔ አልገደልኩም” ከሚል የተቀነባበረ ማስተባበያ ውጭ ተሞግቶም አይውቅም። ያም ሆኖ አሁን ላይ በሚከሰስባቸው ጉዳዮች ሁሉ ማስተባበል የማይችልበት ደረጃ መድረሱን የተበዳዮችና ተፈናቃዮች እንዲሁም ቤተሰቦቻቸውን ያጡ ምስክሮች ያረጋግጣሉ።

አሁን በርካቶች የሚጠይቁት ይህ ድርጅት ስሩ ወለጋ መሆኑና መላውን የኦሮሞ ህዝብ ስለማይወክል ጉዳዩም ክሱም ወደ ወለጋ መዛወር እንዳለበት ነው። እንድውም “የመካከለኛው ኦሮሚያ ለዘብተኛ ፖለቲከኞች ለምን ወደ ስልጣን ይመጣሉ፣ ትክክለኛ ኦሮሞ ወለጋ ነው። ወለጋ ስልጡን ነው” ከሚሉ አመለካከቶች ጋር በማገናኘት ኦሮሞ በህብረት ድርጅቱ እንደማይወክለውና የተወሰኑ አካባቢ ኦሮሞዎችን ስም የሚጠቀም መሆኑንን በገሃድ አቋም ወስደው ማስታወቅ እንዳለባቸው የሚናገሩ እየበረከቱ ነው። ክልሉን የሚያስተዳድረውም አካል በግልጽ ይህንን ለህዝብ መንገር እንዳለበት አመልክተዋል። ትህነግም በገሃድ ሸኔን ልክ አብሮ መስራቱን እንዳወጀ ሁሉ አሁንም አብሮ እንደማይሰራና ድርጊቱን በማውገዝ እንዲፈርጅ መደረግ እንዳለበት ጠቁመዋል።

” በኦሮሞ ስም ነጻ አውጪ ነን” በሚል ተደራጅተው በሰላማዊ ነዋሪዎች፣ አርሶ አደሮችና የፋብሪካ ሰራተኞች ላይ ጥቃት እየፈጸሙ ያሉት ክፍሎች በኦሮሞ ስም ይህን ድርጊት ሲፈጽሙ ዝም ብሎ ማየት አግባብ አይደለም” የሚሉ ” ሸኔ የቀጠረውን አካልና መሰረቱ ያለበት ወለጋ አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎች ሊያስቡበት ይገባል። ከአማራ የተዋለደው ኦሮሞ ክፉኛ እየተበሳጨ ነው” ብለዋል።

“የአማራ ሕዝብ ላይ በስም የሚታወቅ ድርጅት በተደጋጋሚ ጥቃት ሲፈጽም በኦሮሞ ስም የተደራጁም ሆነ ድፍን የኦሮሞ ሕዝብ ገሃድ ወጥተው ሊቃወሙት ይገባ ነበር፣ አንዴም ሳይሆን በተደጋጋሚ” ሲሉ የሚከሱ፣ ቢቢሲ እንዳለው ንጹሃንን እያፈኑ ጉቦ መጠየቅ የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ ተደርጎ፣ በዚህ ታላቅ ሕዝብ ስም የተበላሸ ታሪክ እየተጻፈና ለልጅ ልጅ የሚተርፍ ቂም እየተቀመጠ መሆኑንን እንዴት መረዳት እንዳዳገታቸው ይገልጻሉ።

በኦሮሚያ ምዕራብ ሸዋ ዞን በሸኔ ታግተው የነበሩት የዳንጎቴ ሲሚንቶ ፋብሪካ ሠራተኞች ከፍተኛ የማስለቀቂያ ንዘብ ከፍለው እንደተለቀቁ ያመለከተው ቢቢሲ የሰላማዊ ዜጎችን እገታ አስመልክቶ የታጣቂ ቡድኑ ቃል አቀባይ በጉዳዩ ላይ ምላሽ እንዲሰጡ ተጠይቀው እስካሁን ያሉት ነገር እንደሌለ አስታውቋል። ምንጮች ያላቸውም የገታውን ዓላማና በትግል ስም ህዝብ ማገት ትግል የሚባለውን ነገር የት ድረስ ያደርሰዋል በሚል ጠይቆ አስተያየቱ አላስቀመጠም።

የታጣቂ ቡድኑ አባላት ካገቷቸው በፋብሪካው አውቶብስ ተሳፍረው ሲጓዙ ከነበሩት ሠራተኞች አነስተኛ ገቢ ያላቸውን ለቀው አስራ ሰባት የሚሆኑትን አግተው እንደከረሙ በዝገባው ተመልክቷል። ቢቢሲ በምዕራብ ሸዋ ላለፉት ሁለት ዓመታት ሰላም እንዳልነበርና አሁን መባባሱን በአስተያየቱ አስፍሯል። ቦታዎቹን ግን አላስታወቀም። ይህ ንጹሃንን አፍኖ የጉቦ ጥያቄ የቀረበበት ቦታም ከአዲስ አበባ ዘጠና ኪሎሜትር መሆኑን በማሳየት ወንጀሉ አዲስ አበባ አፍንጫ ስር መፈጸሙን አመክቷል።

የሠራተኞች እገታ ባጋጠመ ወቅት የዳንጎቴ ሲሚንቶ ፋብሪካ ሁለት ኃላፊዎች 17 ያህል ሠራተኞች የትንዳሉ እንደማያውቁ ቢነገሩትም፣ ቢቢሲ ከምንጮቹ እንዳጣራው በታጣቂዎቹ ታግተው ለቀናት የቆዩት ሠራተኞች ከ300 ሺህ እስከ 500 ሺህ ብር የማስለቀቂያ ገንዘብ ከፍለው ባለፈው ቅዳሜ እና ዕሁድ መለቀቃቸውን አትሟል።

ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱ ነዋሪ እና የፋብሪካው ኃላፊዎች ሠራተኞቹ የሲሚንቶ ግብዓት ተቆፍሮ ወደሚወጣበት ስፍራ በድርጅቱ የሠራተኞች ማመላለሽ አውቶብስ እየተጓዙ ሳለ ነበር በታጣቂ ቡድኑ አባላት የታገቱት።

እራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ብሎ የሚጠራው ቡድን በስፋት በሚንቀሳቀስበት በዚህ አካባቢ ከፍተኛ የደኅንነት ስጋት ያለ ሲሆን፣ ከዚህ ቀደምም በዚህ አካባቢ ሰዎችን አግቶ ገንዘብ መጠየቅ በተደጋጋሚ እየተከሰተ ያለ ጉዳይ መሆኑን ነዋሪዎች ተናገረዋል።

ከእንዲህ አይነቶቹ የእገታዎች ጋር ስሙ የሚነሳው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት አባላቱ በእንዲህ ያለ ድርጊት ውስጥ እንደማይሳተፉ አስተባብሎ ነበር።

በቢቢሲ ይህንና ተመሳሳይ የእገታ ድርጊቶችን በተመለከተ ከአካባቢው እና ከክልሉ ኃላፊዎች ምላሽ ለማግኘት ያደረገው ጥረት አልተሳካም።

ባለፈው ሳምንት የኦሮሚያ ክልል ኮምዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ታጣቂ ቡድኑ በተለያዩ አካባቢዎች ከሚፈጽመው ጥቃት ባሻገር ሰዎችን በመያዝ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብን ለማስለቀቂያነት እንደሚጠቅ ገልጸው ነበር። ባለሥልጣኑ ጨምረውም ታጣቂው ቡድን በተለያየ አካባቢ የተበታተነ እና እርስ በእርሱ ግጭት ውስጥ ያለ መሆኑን በመግለጽ፣ ምንም አይነት “ፖለቲካዊ አጀንዳ የላቸውም” ብለዋል።

Exit mobile version