ETHIO12.COM

ባይቶና “የትግራይ ክልላዊ መንግስት ፈርሷል፤ እንቅስቃሴው ጸረ ሰላም ነው”

ራሱን በትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪነት ሰይሞ ለግማሽ ምዕት የተጓዘው ትህነግ የፈረሰ አስተዳደር እንዳለውና ማናቸውንም ህጋዊ የክልል መንግስትነት ስራ መስራት እንደማይችል ጠቅሶ ባይቶና መግለጫ አሰራጨ። “ከሰላም ከስምምነት ፌርማ ቦኃላ በትግራይ የሚደረግ የህዝብ ተወካዮች ምክርቤት ጉባኤ ህገወጥና ፀረሰላም እንቅስቃሴ ነው” ብሏል።

ባይቶና የሚባለውና በፕሮግራምም ሆነ በፖለቲካ እምነት ከትህነግ ይህ ነው የሚባል ልዩነት የሌለው የትግራይ ክልል ተፎካካሪ ድርጅት ትህነግን እንደ ክልል መንግስት እንደማይቀበለው ያስታወቀው ህግና አንቀጽ ጠቅሶ ነው።

“በጥቅምት ወር 2015 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ አንቀፅ 10 ቁጥር 1 መሠረት በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራስያዊ ሪፐብሊክ መንግስትና በትህነግ መካከል የተደረገው የሰላም ስምምነት ላይ ትህነግን ወክሎ የተደራደረው አካል ህጋዊ መንግስት በትግራይ አለመኖሩን አምኖ፣ ያካሄደው ምርጫ ህገወጥ እንደሆነ ተቀብሎ፣ የትግራይን ክልላዊ መንግስት ምክር ቤትን አፍርሶ እንደመጣ ባይቶና በመግለጫው አስቀምጧል።

በዚህ መነሻ “ከሰላም ከስምምነት ፌርማ ቦኃላ በትግራይ የሚደረግ የክልል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጉባኤ ህገወጥና ፀረሰላም እንቅስቃሴ ነው” ሲል ትህነግ ያደረገውን ስብሰባ በጸረ ህዝብነት ፈርጇል።

የትግራይ ክልል ምክር ቤት በሰላም ድርድሩ ትግራይን የሚወክሉ የተደራዳሪ ቡድን አባላት ማጽደቁን ህዝባዊ ሓርነት ትግራይ «ህወሃት» ማስታወቁን ተከትሎ ነው ባይቶና ተቃውሞውን ያሰማው።

ምክር ቤቱ አካሄድኩ ባለው 6ኛ ዘመን 3ኛ አመት አስቸኳይ ስብሰባ የትግራይ ክልልን መንግስትን ወክለው በሰላም ድርድሩ የሚደራደሩ ተደራዳሪ አባላት ለማቋቋም፣ እንዲሁም የሚያከናውን ተግባር እና ሀላፊነትን በተመለከተ ለመወሰን በተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅ ላይ መወያየቱን ምደባ መፈጸሙን ተመክቷል። እ

ከውይይቱ በኋላ በትህነግ ሊቀመንበርና በክልሉ መሪ ዶ/ር ደብረፅዮን የተደራዳሪ ብዱኑ አባላት መሆናቸውን ገልጸው ያቀረቡትን ዝርዝር ስም አሰምተዋል። በዚሁ መሰረት አቶ ጌታቸው ረዳ ፤ ታጋይ ፃድቓን ገብረትንሳኤ፤ ዶክተር ፍስሃ ሃፍተፅዮን፤ ኣምባሳደር ወንድሙ ኣሳምነው፤ የቀድሞው ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ፤ ወይዘሮ ያለም ፀጋይ ፤ አቶ በየነ ምክሩ እንዲሁም ተባባሪ ፕሮፌሰር መረሳ ፀሃየ በሰላም በድርድሩ ትግራይን ክልልን እንደሚወክሉ ተመክቷል።በተጨማሪ ሁለት ከትግራይ ዲያስፓራ ማህበረሰብና አንድ ከተቀናቃኝ የፓለቲካ ፓርቲዎች ጨምሮ በሰላም ድርድሩ ትግራይን የሚወክሉት ልኡካን ቡድን 11 አባላት ያሉት እንዲሆን ቀርቦ በአብላጫ ድምፅ እንደጸደቀ ትህነግ ይፋ አድርጓል።

የባይቶና አመራሮች ስለምርጫው የሰጡት አስገራ አስተያየት ቅንጫቢ ፊልም

ይህንኑ ተከትሎ ነው ትህነግ በድምጽም ሆነ ባማናቸውን ዓይነት ደረጃ በፈረሰ ምክር ቤትና የክልል መንግስት ውስጥ ሚና እንደሌለው ያስታወቀው። ትህነግ ደቡብ አፍሪካ ላይ በተደረገው ስምምነት ህገወጥ ምርጫ ማካሄዱን፣ በአገሪቱ ህግ መሰረት ምርጫ ቦርድ ብቻ ምርጫ የማካሄድ ስልጣን እንዳለው አምኖ በፌደራል መንግስት ዕውቅና ያለው አዲስ ህጋዊ ምርጫ ለማካሄድ መስማማቱ የሚታወስ ነው። ባይቶናም ይህን ጠቅሶ ነው ተቃውሞ ያሰማው። ለባይቶና ቅሬታ በይፋ የተሰጠ ምላሽ የለም። ባይቶና ቀድሞውንም ትህነግ ያካሄደው ምርጫ በገለልተኛ ተቋም ያልተመራና የተጭበረበረ መሆኑ ጠቅሶ ቅሬታ ማሰማቱ የሚታወስ ነው።

በሌላ የትግራይ ዜና አቶ ጌታቸው ረዳ ለመንግስት ስጋት ድፍን ምላሽ ሰጥተዋል። የፌዴራል መንግሥት “የመከላከያ ሠራዊት ባልደረሰባቸው የትግራይ አካባቢዎች በተለይም በመቀሌ ከተማ በፓትሮል ጭምር የታገዘ ከፍተኛ ዝርፊያ መኖሩን አስታውቋል። መንግሥት ለሕዝብ እና ለሀገር ሰላም ሲባል በሰላም ስምምነቱ የገባውን ቃል ሳይውል ሳያድር በመተግበር ላይ መሆኑን በቅርቡ በሰጠው መግለጫ አስታውቆ ለስምምነቱ መከበር ሁሉም ወገኖች በእኩል ደረጃ ሊተባበሩ እንደሚገባ አመልክቶ ነበር። አያይዞም የትግራይ ህዝብ ደህንነት ሊጠበቅ እንደሚገባ አስታውሶ ካልሆነ ግን አስፈላጊ ያለውን እርምጃ ሊወስድ እንደሚችል አሳስቦ ነበር

አቶ ጌታቸው ረዳ “እኛ ልንፈታው የማንችለው፣ ሕዝባችን ሊፈታው የማይችለው ማንኛውም አይነት የደህንነት ሥጋት ማንም ሊፈታው አይችልም” በማለት ትዊተር አውዳቸው ላይ ምላሽ ሰጥተዋል። ይሁን እንጂ በፓትሮል የተደገፈ ዝርፊያ የለም ሲሉ አላስተባበሉም። እንዴት ችግሩ እንደሚፈታም አላመላከቱም።

ይህንን ተከትሎ ግን ዕርዳታ ከገባ በሁዋላ ትህነግ ጦርነት እየሸተተው እንደሆነ በስፋት ስጋታቸውን የሚገልጹ በዝተዋል። በትግራይ የሰላም አየር እየታየ ባለበት፣ ህይወት እየለመለመና አዲስ ተስፋ መታየት በጀመረበት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲህ ያለው ግልጽ ያላለ ምልልስ በተለይ በርካታ ልጆቻቸውን ላጡ፣ በጨለማ ለኖሩና ድርቅ ላጠቃቸው ክፍሎች ክፉ ዜና ሆኗል።

Exit mobile version