Site icon ETHIO12.COM

የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች የኢትዮጵያ አየር ኃይልን ጎበኙ

የኢትዮጵያ አየር ኃይል ተልዕኮን የመወጣት ብቃቱን ይበልጥ በማሳደግ ለአከባቢውና ለቀጠናው ሰላም በትኩረት እየሰራ ነው ሲሉ የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ ገልፀዋል።

በዛምቢያዊው ብርጋዲዬር ጀኔራል ሙዬሰርዳ ናቲጊያ የተመራው በኢትዮጵያ የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ቡድን በኢፌዴሪ አየር ኃይል ጉብኝት አድርጓል።

የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ፣ የኢትዮጵያ አየር ኃይል በአመሰራረት ታሪኩ የአቭዬሽን ቴክኖሎጂን በመጠቀም በኩል ከአህጉሪቱም አልፎ በአለም አቀፍ ደረጃም ቢሆን አንጋፋ የአቭዬሽን ተቋም ነው። በሰላም ማስከበር ተሳትፎ ግንባር ቀደም ኃይል መሆኑን አስረድተዋል።

በአቭዬሽን ቴክኖሎጂ በኩል ከሌሎች የአለም ሀገራት ጋር ተባብሮ በመስራት ለሚታወቀው የኢትዮጵያ አየር ኃይል የወታደራዊ አታሼዎቹ ጉብኝት ፋይዳው የጎላ ነው ሲሉ ሌተናል ጀኔራል ይልማ ተናግረዋል፡፡

ይህን መልካም ግንኙት በቀጣይነትም ከየሀገራቱ ወታደራዊ አታሼዎችና ባለሙያዎች ጋር ለጋራ ተጠቃሚነት ሲል ግንኙነቱን አጠናክሮ ለማስቀጠል ተቋሙ ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆኑንም አስረድተዋል።

በኢትዮጵያ የውጭ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ማህበር ዋና ፀሐፊ ብርጋዳዬር ጀኔራል ሙዩሶርዳ ናቲጊያ ጉብኝቱን በማስመልከት በሰጡት አስተያዬት የኢትዮጵያ አየር ኃይል ከመዋቅራዊ አደረጀጀቱ ጀምሮ በሰው ኃይል አቅምና በዘመናዊ የአቭዬሽን ትጥቅ በኩል ራሱን በማዘመን በአስደናቂ የለውጥ ጉዞ ላይ እንደሚገኝ ገልፀዋል፡፡

ኮሎኔል ማርኮ ፖዲ በኢትዮጵያ የጣሊያን ወታደራዊ አታሼ እንዲሁም ኮሎኔል ዢያን ማርክ ኦዘን የፈረንሳይ ወታደራዊ አታሼ ሀገሮቻቸው በወታደራዊና በሌሎችም መስኮች ከኢትዮጵያ ጋር ጥብቅ ትስስር ካላቸው ሀገራት ቀዳሚዎቹ ሀገራት መሆናቸውን ገልፀው በኢትዮጵያ አየር ኃይል ያካሄዱት ጉብኝትም በተለይ በአቭዬሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ የልምድና የእውቀት ሽግግር በሀገራቱ መካከል ለማድረግ የሚረዳ መሆኑን ተናግረዋል።

በዕለቱም ኮሎኔል ብሩክ ሰይፉ የአየር ኃይል ህዝብ ግንኙነት ዋና ክፍል ኃላፊ ስለተቋሙ የስኬት ጉዞ ለወታደራዊ አታሼዎቹ ገለፃ ያደረጉ ሲሆን በጉብኝቱ ማጠቃለያ የወታደራዊ አታሼዎቹ ማህበር ያዘጋጁትን ስጦታ በተወካያቸው አማካኝነት ለኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ለሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ መስጠታቸውን ከሀገር መከላከያ ሠራዊት ማህበራዊ ትስስር ገጽ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

Exit mobile version