Site icon ETHIO12.COM

” በቅርቡ 10 ኤጲስ ቆጶሳትን እንሾማለን ” የትግራይ ቤተክህነት

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፤ ሌላው ፈተና ነው የተባለው በትግራይ ክልል የሚገኙ ሊቃነጳጳሳት እንቅስቃሴ ጉዳይ አሁንም መቀጠሉ ተነግሯል።

በሰሜን ኢትዮጵያ በተከሰተው ጦርነት ምክንያት በትግራይ ያሉ አባቶች ቤተ ክህነት ማቋቋማቸውን ማሳወቃቸው ይታወቃል።

ሊቃነ ጳጳሳቱ በዛሬው ዕለት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ፤ ” በቅርቡ 10 ኤጲስ ቆጶሳትን እንሾማለን ” ብለዋል።

በቅርቡ 10 ኤጲስ ቆጶሳትን በአገር ውስጥና በውጭ እንደሚሾም የተናገሩት ሊቃነ ጳጳሳቱ አዲሶቹ ተሿሚዎች በቅርብ ጊዜ ውስጥም ወደ ሥራ ይገባሉ ሲሉ ማሳወቃቸውን ትግራይ ቴሌቪዥን ዘግቧል።

በትግራይ ክልል የሚገኙት ሊቃነ ጳጳሳት መሥርተነዋል ያሉትን ቤተ ክህነት ካቋቋሙበት ጊዜ ጀምሮ ስለ ኤጲስ ቆጶሳት ሢመት ጉዳይ ያሉት ነገር ባይኖርም አሁን ላይ ኤጲስ ቆጶሳትን እንደሚሾሙ አሳውቀዋል።

ተዋህዶ ሚዲያ ማዕከል ፤ በጉዳዩ ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ጠቅላይ ጽ/ቤትም ሆነ ቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት አስተያየታቸውን እንዲሰጡ ሙከራ ማድረጉን ነገር ግን እንዳልተሳካ ዘግቧል።

በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ምክንያት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ሥር በትግራይ በሚገኙ አኅጉረ ስብከት መካከል የነበረው ግንኙነት መቋረጡን ይታወቃል።

በቅዱስ ሲኖዶስ በኩል በትግራይ ክልል ለሚገኙ ብፁዓን አባቶች የግንኙነት ማስቀጠያ ደብዳቤዎች ሲጻፉ ቢቆዩም ውጤት ግን ሊያመጡ አልቻሉ።

በቅርቡም ቅዱስ ሲኖዶስ ከብፁዓን አባቶች፣ ከሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ ከታዋቂ ሰዎችና ከምዕመናን የተወጣጣ ኮሚቴ ሰይሞ የነበረ ሲሆን ግንኙነቱን ለማስቀጥል ያመች ዘንድ አንድ ልዑክ ወደ ትግራይ እንደሚልክ ተነግሮ ነበር፤ ነገር ግን ከዚህ በኃላ የተሰማ አዲስ ነገር የለም።

@tikvahethiopia

Exit mobile version