Site icon ETHIO12.COM

መከላከያ “ለሁሉም ልክ አለው፤ ሁለት ቦታ ረግጠው የሚያስወጉና የሚያዋጉ ላይ ማናቸውም ዓይነት እርምጃ ይወሰዳል”

“የትህነግን መጨረሻ ያየ ከመከላከያ ጋር አጉል አይላፋም፤ ከአገር መከላከያ ጋር መጣላት እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ቤት እሳት መለኮስ ነው”

“የኢትዮጵያ ህዝብ የመጨረሻ ህልውናዬ” የሚለውና ከአብራኩ በውወጡ ልጆቹ ያቆመውን የአገር መከላከያ ሰራዊት ስም ማጠልሸት ከአሁን በሁዋላ በዝምታ እንደማይታይ፣ በአገር ሰላምና ልማት እንቅፋት በሚፈጥሩ አካላት ላይም እገሌ ከእገሌ ሳይል የማያዳግም እርምጃ እንደሚወሰድ የተቋሙ ህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ “በቃ” ሲሉ ያስታወቁት ከወትሮው በከረረ መልኩ ነው። “ሃሳብ ሲነጥፍ ነፍጥ አንስቼ እዋጋለሁ ካለ መከላከያ አያርፍም” ሲሉ ስም ባይጠቅሱም የህግ ከለላ ያላቸውም ይሁን ሌሎች፣ ከሃዲድ ወርደው በሁለት እግራቸው የሚረግጡ የወጉና የሚያስወጉ ላይ የትኛውም ዓይነት እርምጃ እንደሚወሰድ ሲያስታውቁ ” በገጠሙን መጥን ስለምንገጥም ወዳጅ ዘመድ ሃይ ይበል” በሚል ምልጃም ጭምር ነው።

በሸኔ ላይ አስፈጊ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑንን አመልክተው፣ አባ ገዳዎች፣ የአገር ሽማግሌዎችና ህዝብ ከመከላከያ ጋር ሆኖ ቁጥራቸው የበዛ የሸኔ ታጣቂዎች እጅ እየሰጡ ወደ ሰላማዊ መንገድ መግባታቸውን አመልክተዋል። ከመከላከያ ዱላ የተረፈው ሃይል ተገዶ ወደ ሰላም እስካልመጣ እጣ ፈንታው መጥፋት እንደሆነ ኮሎኔሉ አመልክተዋል።

ኮሎኔሉ ይህን ያሉት የአገር መከላከያ ሰራዊትን አሁናዊ ሁኔታ በማስመልከት መግለጫ በሰጡበት ወቅት ነው። እንደ እሳቸው ገለጻ አሁን ላይ መከላከያ ያለበትን ደረጃና ቁመና ከበፊቱ ወይም ከዛሬ አምስት ወይም ሁለት ዓመት በፊት እንዳልነበረ ጠቅሰው ዘመኑንን በሚመጥን ደረጃ ራሱን እያበቃ በመገሰገስ ላይ ስለሆነ ከቀድሞ ጋር በማመሳሰል ስህተት ውስጥ የገቡ ሀይሎች ወደ ቀልባቸው ሊመለሱ እንደሚገባ ጠቁመዋል። መከላከያ ባለበት የቆመ የመሰላቸውን ” እነሱ ባሉበት የቆሙ ናቸው” ሲሉ ኮሎኔሉ ማስገንዘቢያ ሰጥተዋል። የአገር መከላከያን መስዋዕትነትና በደምና አጥንቱ ያስመዘገበውን ድል ማሳነስም ከህዝብ ጋር መጣላት እንደሆነ የመከላከያ መኮንኖች ” አይበጅም” ሲሉ ደጋግመው በተለያዩ መድረኮች ከህዝብ ጋር ሲመከሩ መናገራቸው አይዘነጋም።

የመግለጫው ዋነኛ ዓላማም ሕዝብ መረጃ እንዲደርሰው ለማድረግና በጠራ መረጃ ቅጥፈትን እንዲመዝን ታስቦ መሆኑን ያመለከቱት ኮሎኔል ጌትነት፣ “እውነተኛ” ሲሉ በክብር የጠሩት የፋኖ ሃይል ከመከላከያ ጋር ዋጋ የከፈለና አብሮ በመናበብ የሚሰራ መሆኑንን አመልክተዋል። ይሁን እንጂ በስሙ የሚነገዱት የማህበራዊ ገጽ ጀግኖች ያልሆነውንና የልተደረገውን በማወጅ መሬት ላይ ካለው እውነት በተለየ የአየር ላይ ማጠልሸት ዘመቻ ላይ መጥመዳቸውን መከላከያ ሊታገሰው ከማይችልበት ደረጃ መድረሱን ገልጸዋል።

“እስከአሁን ደረስ ራሳችንን ከመግለጫ ያቀብነው ሰራዊታችን የሚያከናውናቸው ተግባራት በራሳቸው ገላጭ ስለነበሩና በማህበራዊ ሚዲያውም የዚህን ህዝባዊ ሰራዊት መልካም ስራ በመደገፍ ስም የማጥፋት ዘመቻው ሲከሰተም የሚሟገቱ የእውነት ዘቦች በመኖራቸው ነው” ካሉ በሁዋላ “አሁን ግን” አሉ ኮሎኔሉ፣ ” አሁን ግን ሰራዊታችንን ፊት ለፊት ገጥመው ማሸነፍ ያልቻሉ ሀይሎች በተለያየ መንገድ በጀግናው ሰራዊታችን ላይ የሚጎነጉኑት ሴራ ከፍ እያለ በመምጣቱ ውሸት ሲደጋገም እውነት የሚመስላቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ሊኖሩ ስለሚችሉ ሰራዊቱ ሸሽቷል ፣ተማርኳል፣ በዚህ ወቷል፣ በዚህ ገብቷል የሚለው መረጃ ከእውነት የራቀ መሆኑን ለህዝብ ማሳወቅ አስፈላጊ ሆኗል” ሲሉ የመረጃውን አስፈላጊነት አስታውቀዋል።

“ማንም ይሁን ማን” አሉ ኮሎኔሉ፣ ” የመንግስት ሃላፊም ሆነ ሌላ” ካሁን በሁዋላ አስፈላጊ ነው የተባለ ህጋዊም ሆነ የሃይል እርምጃ እንደሚወሰድበት ሊታወቅ እንደሚገባ ” በቃን። ትዕግስትም ልክ አለው” የሚል አዝማሚያ ያለው መልዕክት አስተላልፈዋል። ለሰላም ሲባል መከላከያ ብዙ ጉዳዮችን ሲያስታምም እንደቆየ ያመለከቱት ኮሎኔሉ ይህ አካሄድ ካሁን በሁዋላ እንደማይቀጥል ይፋ አድርገዋል።

በአማራ ክልል አንዳንድ ስፍራዎችን ስም በመጥራት የተዘገቡ ዜናዎችን ” ፍርዱን ለአካባቢው ህዝብ ትቼዋለሁ” በማለት እንዳስታወቁት ከሆነ የሚወራው ወሬ መሬት ላይ ካለው ጋር ዝምድና ቀርቶ ግንኙነት እንደሌለው ነው። ለማሳያ ያህል አካባቢዎችን ጠቅሰው ምን ተፈጥሮ፣ እንዴት መላ እንደተበጀ ካስረዱ በሁዋላ ” ካሁን በሁዋላ ሃዲስ የሳተ አዋጊም ይሁን ተዋጊ፣ አክቲቪስትም ሆነ ፌስቡከኛ አስፈላጊው እርምጃ ይወሰድበታል” ሲሉ በግልጽ ተናግረዋል።

ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ተከበው ነበር፣ በሄሊኮፕተር አመለጡ፣ ጀነራሎች በሃሳብ ተለያዩ፣ ከተማ ነጻ አወጣን … ወዘተ በሚል የሚሰራጩ የዓየር ላይ ወሬዎች እንደሆኑ ካመለከቱ በሁዋላ አጥብቀው ያሳሰቡት ” መከላከያን ማጠልሸት የትም ይሁን የት፣ ማንም ይሁን ማን ይጠየቃል፣ እርምጃ ይወሰድበታል” በሚል ማስጠንቀቂያ ነው። በተለያዩ ወቅቶች “መከላከያ ራሱን ከሚዲያ አዋጊዎች ሊጠብቅና ስሙን ሊያስከብር ይገባል” የሚል ጥያቄ በተቆርቋሪዎች ሲነሳ መቆየቱ አይዘነጋም።

የሰራዊታችን አሁናዊ ቁመናም ሲታይ በወታደራዊ ትብብር፣በውጭ የትምህርት እድሎች፣በዓለምአቀፋዊ እና አህጉራዊ የሰላም ማስከበር ተልእኮዎች አመርቂ ውጤት ማምጣት የቻለ ከዚህ ቀደም በነበሩት ሀገርን የማዳን ዘመቻም ኢትዮጵያን ከመፍረስ በመታደግ የጠላቶቻችንን ህልም ቅዠት ማደረግ የቻለ ትጉህ ሰራዊት እንደሆነ አብይ ማስረጃ አመላክተው ኮሎኔል ጌትነት አዳነ አስረድተዋል። ይህ አቅምና አቋም አስፈላጊ ሲሆን በማናቸውም ወቅቶች ማንም ላይ እንደሚደገም ሳያቅማሙ አመልክተዋል።

“የተለያዩ ግጭቶች በሚስተዋልባቸው አካባቢም ‘ሰራዊቱ ትእዛዝ አልተሰጠንም በማለት የሰው ህይወት እንዲጠፋና ንብረት እንዲወድም አድርጓል’ የሚሉ ትችት ለሚሰነዝሩ አካላት የሰራዊቱን ሕዝባዊ የግዳጅና የግዳጅ አፈጻጸም መርሆች በየደረጃው ጠንቅቆ ካለማወቅ የሚመነጭ እንደሆነ አስታውቀዋል። ካለማወቅ በዘለለም ሆን ተብሎ ሴራ በመጎንጎን የሚመረት የስም ማጠልሸት እንደሆነና ይህ ተራ ስም ማጥፋት ኢትዮጵያን በደሙና አጥንቱ እየተከላከለ ለሚያጸናው ሰራዊት እንደማይመጥን ማስተዋል ለሚችሉ ሁሉ በማሳሰቢያ መልኩ ነግረዋል።

“አድርግ ተብሎ ትእዛዝ በተሰጠው ቦታ ሁሉ ውጤታማ ግዳጅ ሲፈፅም የቆየ ወደፊትም ለታላቅ ተልእኮ ከጊዜ ወደ ጊዜ ራሱን እያዘመነ የመጣ፣ በሰላም ጊዜ የልማት ሰራዊት፣ በጦርነት ጊዜ ደግሞ የጦር ሰራዊት ሆኖ ሀገሩን ከጠላት መንጋጋ በመከላከል በቅንነት ህዝቡን የሚያገለግል ጀግና ሰራዊት ነው” ሲሉ የኢትዮጵያ ሕዝብ አለኝታ የሆነውን የአገር መከላከያ ሰራዊት ስብዕና ያመላከቱት ኮሎኔል ጌትነት፣ ካሁን በሁዋላ ይህን ስብእና በሚጥስና በሚያቆሽሽ መልኩ ለሚደረግ ማናቸውን ተልዕኮ አንጋቢዎች አስፈጊ ምላሽ እንደሚሰጥ አጠንክረው አስገንዝበዋል።

የመከላከያ ሰራዊቱ በአገር ሰላም እና ልማት እንቅፋት በሚፈጥሩ አካላት ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ፣ በኢትዮጵያ ልማትና ሰላም ላይ ቀልድ እንደሌለ ያመለከቱት ኮሎኔሉ፣ ” የተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎችን በመጠቀም የሰራዊቱን ስም የሚያጠለሹ አካላት ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ” ሲሉ ከወዲሁ መክረዋል። መከላከያን መንካት ጉዳዩ የኢትዮጵያን ህዝብ የመጨረሻ ቀይ መስመርና የአገሩን ኢትዮጵያን ህልውና መገዳደር እንደሆነ ትህነግ የአገር መከላከያ ላይ ክህደት ፈጽሞ ጥቃት ባደረሰ ወቅት ህዝብ ከዳር እስከዳር በቁጣ መነሳቱ የሚታወስ ነው።

“ነፍጥ በማንገብ በሀገር ሰላምና ልማት ላይ እንቅፋት ለመፍጠር በሚሰሩ አካላት ላይ ሰራዊቱ እርምጃ ይወስዳል” ሲሉ በግልጽ ያስታወቁት ኮሎኔል ጌትነት ቃል በቃል ባይናገሩትም እስከ አፍንጫው ታጥቆና ሚሊሻ ሰብስቦ ኢትዮጵያን ለመበተን የተነሳውን ትህነግን በደፈናው ማሳያ በማድረግ አሁን ላይ መከላከያ የደረሰበትን ደረጃ አክለው መከላከያን እየተነኮሱ ያሉትን አስጠንቅቀቀዋል።

የመከላከያ ሰራዊት አገራዊ፣ ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎችን መሰረት አድርጎ ግዳጁን በብቃት እየተወጣ ለህዝብ ይፋ አድርገዋል። በቅርቡ አቶ ዮሐንስ ቧያለው መከላከያ ከአማራ ክልል እንዲወጣ በይፋ መጠየቃቸው ይታወሳል። አቶ ዮሐንስ በአማራ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ መከላከያን “አሸባሪና ወራሪ” ሲሉ ጠርተዋታል። እሳቸው ይህን ቢሉም ኮሎኔል ደመቀ ወዲያውኑ “ከመከላከያ ጋር ተስማምተን እየሰራን ነው። በአካባቢያችን ምን ጦርነት የለም” ሲሉ ለሪፖርተር መናገራቸው ግራሞት ፈጥሮ ነበር።

አዲስ አበባና በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚኖሩ መከላከያን የሚያራክስ መረጃ ሲያሰራጩ መስማትና ማየት፣ ለዩቲዩብ ገበያ ከተመቸ ምንም ሆነ ምን እንደሚሰራጭ የሚጠቅሱ መንግስት ዝምታ መምረጡ ያመጣው ጣጣ እንደሆነ ገልጸው በርካቶች ቅሬታቸውን ሲገልጹ እንደነበር ይታወሳል። መንግስትን መቃወም፣ መተቸትና ማጋለጥ መረጃ ላይ ተደግፎ ለህዝብ አሳልፎ መስጠት የሚደገፍና የሚበረታታ ቢሆንም ይህ ሲሆን እንደማይታይ አብዛኞች ይስማማሉ።

አቅዶ፣ መርምሮና ሰርስሮ ለህዝብ በሚተቅም ደረጃ የሚሰሩ ሚዲያዎች ባለመኖራቸው ህዝብ ለአሉባልታ፣ ለስድብ፣ ለግልብ አመለካከትና ለፈጠራ ወሬ መጋለጡን የሚናገሩ “አንዳንዶች በዩኒቨርስቲና ታላላቅ ተቋም የሚሰሩ ወገኖች ሳይቀር የንፋስ ዘራሽ ወሬ አስተላላፊና ፈጣሪዎች ሲሆኑ ታይቷል። ይህ ገደብ ሊበጅለት ይገባል። ሁሉም አልፎ ዛሬ መከላከያ ላይ ተደርሷል። መከላከያ ከተነካ ምን ቀረ?” የሚል አስተያየት ስም እየጠቀሱ የሚሰጡም ጥቂት አይደሉም። እነዚህ ወገኖች ” መከላከያችን ሳይነካ መንግስትን እርቃኑ እስኪቀር ለመተቸትና ለማጋለጥ ትንሽ መንቀሳቀስ ለሚወዱ ሚዲያዎች ሁሉ ከበቂ በላይ አጀንዳዎች አሉ” የሚል አሳብም አላቸው።

“የትህነግን መጨረሻ ያየ ከመከላከያ ጋር አጉል አይላፋም፤ ከአገር መከላከያ ጋር መጣላት እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ቤት እሳት መለኮስ ነው” ሲሉ አንድ አባት ትህነግ መከላከያ ላይ እጁን ባነሳ ማግስት ማስታወቃቸው ይታወሳል።

Exit mobile version