Site icon ETHIO12.COM

መከላከያ በኦሮሚያና አማራ ክልል የማጽዳት ስራ እንደቀረው አስታወቀ፤ አማራ ክልል መዋቅሩን እያጠራ ነው፤

የአገር መከላከያ ሠራዊት ይፋ እንዳደረገው ከሆነ በኦሮሚያና በአማራ ክልል የሚንቀሳቀሱ የታጠቁ ሃይሎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ወደ መቃረም ወይም ማጽዳት ተሸጋግሯል። ይህንን ተከትሎ በሁለቱም ክልል ታጣቂዎች በኩል በይፋ ቦታ፣ ስምና አድራሻ ተተቅሶ የተሰጠ ማስተባበያ አልተሰማም። አማራ ክልል የጸጥታ መዋቅሩን እያጸዳ መሆኑ ተገለጿል።

የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ስለሀገሪቱ የፀጥታ ሁኔታ በተለይም በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች የሚንቀሳቀሱ ጽንፈኛ ኃይሎች አሁን ላይ ስጋት ወደማይሆኑበት ደረጃ መድረሳቸውን ያስታወቁት ከመከላከያ ሚዲያ ጋር በነበራቸው ቆይታ ነው።

የጀነራሉን መግለጫ የተከታተሉ እንዳሉት ከሆነ የአንድ አገር የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም የአንድን ኦፕሬሽን ውጤት ለህዝብ ይፋ ሲያደርግ ሃሰት ነው ብሎ መናገር ወይም መከራከር አስቸጋሪ ነው። ብርሃኑ ጁላ የሰጡት ጥቅል መረጃ ሲሆን፣ በቀጣይ የበታች መኮንኖች ዝርዝር መረጃ የሚሰጡበት አካሄድ እንዳለ አመላካች በመሆኑ መከላከያ ባካሄዳቸው ዘመቻዎች ሙሉ ሪፖርት በመረጃ ተደግፎ እንደሚቀርብ ይጠበቃል።

የመከላከያ ሰራዊቱ ጥበብ በታከለበት ወታደራዊ እንቅስቃሴ ተከስተው የነበሩ የፀጥታ ችግሮችን እየቀረፈ መሆኑን የገለፁት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ በአማራ ክልል የህዝቡን የመብት ጥያቄ ካባ በማድረግ ፍላጎቱን በኃይል ለማሳካት የተንቀሳቀሰው ኃይል ላይ እየተወሰደ ባለው እርምጅ አመርቂ ውጤት መመዝገቡን ነው የመከላከያ ፌስ ቡክ ያመለተው። መከላከያ ኦፕሬሽኑን ያካሄደው ካለው ሃይል አስር በመቶ በሚሆነው ብቻ እንደሆነም ገልሰዋል።

እሳቸው ይህን ከማለታቸው በፊት ቢቢሲን ጨምሮ የተለያዩ ሚዲያዎችና ስለጉዳዩ በቂ መረጃ ያላቸው መከላከያ ከተሞችን ጨርሶ ወደ ዞንና ወረዳ ወርዶ የማጽዳት ስራ የጀመረባቸው አካባቢዎች እንዳሉ ማስታወቃቸው ይታወሳል።

የተከበረውን የፋኖ ስም መጠቀሚያ በማድረግ የክልሉን ፀጥታ ሲያውኩ የነበሩ ኃይሎችን በተመለከተም ሲናገሩ ከጥንት ጀምሮ እንደሚታወቀው ፋኖ ሀገር ተወረረች ሲባል ጦርና ጋሻ ይዞ ለኢትዮጵያ ነፃነት የሚሰለፍ እንጂ መልሶ የሀገሩ ሰራዊት ላይ ጦር የሚመዝ አይደለም። አሁን ላይ በፋኖ ስም እየተንቀሳቀሰ ያለው ኃይል በዘረፋ ተግባር ላይ የተሰማራና መንገዶችን በመዝጋት የህዝቡን ሰላም የሚያወክ ነው ብለዋል።

ህዝቡን ሰላም ሲነሳ የነበረው ኃይልም የሰራው የሀሰት ፕሮፖጋንዳ መልሶ እርቃኑን እንዲቀር እንዳደረገውና ይህን ኃይልም የመከላከያ ሰራዊቱ እግር በእግር እየተከታተለና እያሳደደው እንደሆነ ገልፀዋል። አሁን ከህዝቡ እየተነጠለ ያለውን ይህን ኃይል አቅሙን በማዳከም ስጋት ከማይሆንበት ደረጃ ማድረስ ተችሏልም ሲሉ ገልፀዋል።

አገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር ሆነው የሀሰት ፕሮፖጋንዳ የሚነዙ ኃይሎች ለሀገርና ለህዝብ ሲል ውድ ህይወቱን እየከፈለ ሰላም የሚያረጋግጠውን ሰራዊት ስነ-ልቦና ያልተረዱ ናቸው ያሉት ኢታማዦር ሹሙ ሰራዊቱ በተሰማራባቸው የግዳጅ ቀጠናዎች ሁሉ ህገ-መንግስታዊ ተልዕኮውን በአስተማማኝ እየተወጣ ነው ብለዋል፡፡

የፅንፈኞች የሀሰት ፕሮፖጋንዳን የተገነዘበው ህዝባችን ከመከላከያ ሰራዊቱ ጎን በመሆን ለሰላሙ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ መሆኑን የተናገሩት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ በሀሰተኞች ሴራ ተታለው ከፅንፈኞች ጋር የተሰለፉ ወጣቶች በሰላማዊ መንገድ ወደ ህዝቡ እንዲመለሱም ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

መከላከያ በ2015 የበጀት ዓመት ተልዕኮውን በሚገባ መፈፀሙን የገለፁት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በ2016 የበጀት አመትም እንደ ተቋም የተያዘውን እቅድ ለማሳካት ከምን ጊዜውም በላይ ዝግጁ ነው ብለዋል፡፡

ዜናውን አስመልክቶ ከፋኖዎች፣ ከኦነግ ሸኔም ሆን ከንቅናቄዎቹ ጀርባ የሚታወቁ ሚዲያዎችና እንደ መሪ መረጃ በማቅርብ የሚታወቁ በይፋ ቦታና ስም ጠቅሰው መግለጫውን ይህ እስከተጻፈ ድረስ አላስተባበሉም። የፋኖን የጦር ሜዳ ውሎ የሚያቀርቡና ሄሊኮፕተር፣ ታንክና ጀነራሎች መማረካቸውን፣ መቶ ሺህ ሰራዊት መግደላቸውን ሲዘግቡ የነበሩ የጀነራሉን ንግግር በአስተያየት መልክ ከመወርፈና፣ ብልጽግና አክትሞለታል ከማለት የዘለለ ያሉት ነገር የለም።

ይህ በንዲህ እንዳለ የአማራ ክልል የመዋቅር ማጥራት ስራውን በማጠናከር አዳዲስ ሹመት መስጠቱ ተሰምቷል። በዚሁ መሰረት ከነሐሴ 22 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ በስራ ላይ የሚውል የተለያዩ ጸጥታ ዘርፍ ሹመት እንደሚከተለው ተዘርዝሯል።

  1. ኮሚሽነር ደስዬ ደጀን ወልዴ የአብክመ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር
  2. ኮሎኔል ግርማ ገሰሰ ገ/መስቀል የአብክመ ሚሊሻ ጽሕፈት ቤት ኃላ
  3. ኮሚሽነር ሀብታሙ ሲሳይ ገዳሙ የአብክመ ማረሚያ ቤቶች አገ/ኮሚሽን ኮሚሽነ
  4. ዶ.ር እሸቱ የሱፍ አየለ በቢሮ ኃላፊ ደረጃ የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ
  5. ደጀኔ ልመንህ በዛብህ በቢሮ ኃላፊ ደረጃ የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ
  6. በሪሁን መንግሥቱ ከበደ የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ
  7. ዳኛው በለጠ ጎኔ የአብክመ ሚሊሻ ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላ
  8. ገደቤ ኃይሉ በላይ የአብክመ ሚሊሻ ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ

9.  ኮሚሽነር ውበቱ አለነ የፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነርና የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ኃላፊ

  1. ኮማንደር አያልነህ ተስፋዬ የፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነርና የሰው ኃይል አስተዳደር ዘርፍ ኃላፊ
  2. ም/ኮሚሽነር ሰይድ አህመድ የፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነርና የሎጀስቲክስ ዘርፍ ኃላፊ ሆነው መሾማቸው ተዘግቧል፡፡

በተመሳሳይ ዜና ምስራቅ ጉጂ ዞን እና ምስራቅ ቦረና ዞን በአሸባሪው ሸኔ ላይ እየተወሠደ ያለውን እርምጃ አጠናክሮ ቀጥሏል። የክፍለ ጦሩ የሠራዊት አባላት ከአካባቢው የፀጥታ አካላት ጋር በጋራ በመሆን የጥፋት እጁን በመዘርጋት ሠላምን አልቀበልም ያለውን የሸኔ ቡድን ላይ እየወሠዱት ያለውን ርምጃ ተጠናክሮ መቀጠሉን የክፍለ ጦሩ አዛዥ ተናግረዋል።

የክፍለ ጦሩ አዛዥ ኮሎኔል ታደሰ ጉተማ መንግስት በሀገራችን ላይ ሠላም ሠፍኖ ህዝቡ የልማት ተጠቃሚ መሆን እንዲችል ለሸኔ እና መሠል ዓላማ ላላቸው ሃይሎች የሠላም ጥያቄ ቢያቀርብም ጥያቄውን ወደ ጎን በመተው ከሠላም ይልቅ ጦርነትን ከአንድነት ይልቅ መለያየትን የመረጡ የአብሮነት ጠንቆች ሠላም መርጠው ከድርጊታቸው እስካልተቆጠቡ ድረስ ርምጃዎች የሚቀጥሉ መሆናቸውም ገልፀዋል።

በተመሳሳይ

በኦሮሚያ ክልል የሊበን ፣ የጉሜል ደሎ እና የኔጌሌ ወረዳ የፀጥታ ዘርፍ አካላት ከመከላከያ ሰራዊት አባላት ጋር በመቀናጀት በኦነግ ሸኔ ቡድን ላይ እየተወሰደ በሚገኘው እርምጃ ላይ ከሰራዊቱ ጎን በመሰለፍ ጀግንነት እየፈፀሙ እንደሚገኙ ዘመቻውን በመምራት ላይ የሚገኙ አንድ የሰራዊቱ ከፍተኛ አመራር ተናግረዋል።

የሊበን ወረዳ ፀጥታ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ኢብራሂም አቼ በበኩላቸው ከሊበን ፣ ከጉሜል ደሎ እና ከኔጌሌ ወረዳ አካባቢ የተወጣጡ የፀረ ሽምቅ ፣ የፖሊስ እና ሚሊሻ ፀጥታ ሃይሎች ከሰራዊት አባላት ጋር በመቀናጀት ፈታኝ በሆኑ የአየር ፀባይና መልክዓ ምድር ላይ ግዳጃቸውን በፍፁም ጀግንነት እየተወጡ ይገኛል ብለዋል። ኦእነግ ሸኔ ይን አስመልክቶ ያለው ነገር የለም።


Exit mobile version