Site icon ETHIO12.COM

በአማራ ክልል የተነሳው ጦርነት በሰላም ሊቆጭ እንደሚችል ተሰማ

በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ጦርነት በሰላማዊ መንገድ የሚቋጭበት አግባብ ተስፋ ሰጪ ደረጃ መድረሱ ተሰማ። የኢትዮ12 የዜና አቀባዮች እንዳሉት ሰላም ወደድ የሆኑ ዜጎች ችግሩን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት እያደረጉ ያለው ጥረት ውጤታም እየሆነ መሆኑንን ነው ያመለከቱት።

በሰላም ጥረቱ ውስጥ የሚሳተፉትን ወገኖችና የሰላም ንግግር አመቻች የሆኑትን ክፍሎች ሳይጠቅሱ የዜናው ሰዎች እንዳሉት ጥረቱ ብዙ መንገድ ተጉዟል።

“ከዚህም ሆነ ከዚያ የሚጠፋው የኢትዮጵያ ልጆች ናቸው፤ በዚህ ጦርነት አሸናፊም ሆነ ተሸናፊ የሚወደስበት አይደለም። የአንድ እናት ልጆች ጉዳያቸውን በጠረጰዛ ዙሪያ ሊፈቱ የገባል” ከሚል ቀናነት እስከ ጫካ በመውረድ እርቅ እንዲወርድ እየሰሩ ያሉ ወገኖች፣ በተለይ ከአማራ ልዩ ሃይል አፈንግጠው ከወጡት አካላት ጋር እጅግ ተስፋ ሰጪ በሚባል ደረጃ ተደጋጋሚ ግንኙነት ማድረጋቸው ነው የተገለጸው። በስም ካልተገለጹ የአካባቢያቸው ታዋቂ የቡድን መሪዎች ጋርም ሽምግልና የጀመሩ ቀና ምላሽ ማግኘታቸው ተጠቁሟል።

ለመነጋገር ፈቅደኛ ያልሆኑ እንዳሉ ያመለከቱት ክፍሎች እንዳሉት ከሆነ በስም ከሚታውቁ አደረጃች መካከል አሉ በሚባሉ ችግሮች ዙሪያ በቂ ዋስትና የሚሰጥ ከሆነ ለመነጋገር ዝግጁ መሆናቸውን ያስታወቁም አሉ።

በውጭ አገር ያሉና ራሳቸውን የአማራ ንቅናቄ መሪና አቅጣጫ ሰጪ እንደሆኑ የሚገልጹ ለውይይት እንዳልተጋበዙ፣ ይልቁኑም ሰላማዊ ንግግር የሚባል ነገር ሊኖር እንደማይገባ በመጥቀስ ጫና እንደሚያደርጉ የዜናው ሰዎች ገልጸዋል።

የአማራ ክልል በሰፊ ማህበራዊ ቀውስ ውስጥ የከረመ፣ የዘንድሮ እርሻው የተስተጓጎለበት፣ በዚህ ቀውስ ውስጥ ከቀጠለ በከፍተኛ ደረጃ ሊጎዳና ማገገም የማይችልበት ደረጃ ሊደርስ እንደሚችል ስጋት ያላቸው በሰጥቶ መቀበል መርህ ወደ ሰላም ለመምጣት የሚደረገውን ጥረት መደገፍ ከሁሉም ወገን እንደሚጠበቅ ይገልጻሉ።

በመንገድ መስትጓጎል፣ በዝርፊያ፣ በህክምና እጥረት፣ በግብዓት መቀነስና በመሳሰሉት ችግሮች የክልሉ ህዝብ የከፋ ችግር ላይ እንደወደቀ እየተሰማ ነው። እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ወገኖች ጋር መድረስ የማይቻልበት ሁኔታም እንዳለ እየተገለጸ ነው። ቀይ መስቀል እንኳን በነጻነት መንቀሳቀስ እንደማይችል፣ ተሽከርካሪዎቹን የተነጠቀ መሆኑንን ገልጿል። እርዳታ ፈላጊዎች ችግራቸው ወደ ረሃብ እያደገ መሆኑም ተመልክቷል። በዚህ ሁኔታ ውስጥ ለሚገኝ ህዝብ ሲባል የሰላም አማራጭን መከተል ግድ እንደሆነ ቀና አሳቢዎቹ እየገለጹ ነው።

ከመንግስት ወገንም ፈቃደኛነቱ ስላለ አሁን ካለው የኢትዮጵያ አወቃቀር አንጻር ” መንግስት ካልሆንኩ” የሚለውን እሳቤ በመተው ለጊዜው አማራ ክልል ሰላም የሚሆንበት አግባብ ላይ መስማማት ግድ እንደሆነ በማስጠንቀቂያ ጭምር የሚገልጹ፣ አሁን ላይ ከዚህ በላይ አሳሳቢ ጉዳይና ታላቅ ውሳኔ እንደሌለ ይገልጻሉ። መጪው ጊዜ እጅግ እንደሚከብድ በርካታ ምልክቶች እንዳሉ ባለሙያዎች እያሳሰቡ ነው።

ይህ በንዲህ እንዳለ በምዕራብ እና ምሥራቅ ጎጃም ዞኖች አንዳንድ አካባቢዎች፣ ከትላንት ማክሰኞ ከቀትር በኋላ ጀምሮ፣ የስልክ አገልግሎት በመቋረጡ፣ ለዘመዶቻቸው ስልክ ደውለው ማግኘት ያልቻሉ የባህር ዳር ነዋሪዎች አመልክተዋል። በተለያዩ የሚዲያ አውታሮች እንድተሰራጨው ከሆነ በክልሉ አንዳንድ ከተሞች መንገድ ዝግ ነው። አልፎ አልፎም ተኩስ የሚሰማባቸው አካባቢዎች እንዳሉ ነዋሪዎችን ዋቢ የሚያደርጉ ይገልጻሉ።

ይህ በንዲህ እንዳለ በምዕራብ ጎጃም መሸንቲ ሙስሊሞች መዘረፋቸውና መታገታቸው ተሰምቷል። እገታውና ዝርፊያው እንድተፈጸመ መረጃ እንዳላቸው የገለጹ፣ ለይቶ ሙስሊሞችን ማገትና መዝረፍ የተፈለገበት ምክንያት ምን እንደሆነ ለጊዜው ይፋ አላደረጉም። አክለውም ማስፈራሪያ የሚሰነዘርባቸው እንዳሉ ገልጸው እንዲህ ያለው አካሄድ እጅግ የከፋ መዘዝ እንደሚያስከትል ጠቁመዋል። ነገ ዛሬ ሳይባል ሊቆም እንደሚገባ ጠቁመዋል።

በሌላ ዜና የደሴ ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሞላልኝ በመኖሪያ ቤታቸው ተገደሉ በሚል የተሰራጨው ዜና ሃሰት መሆኑን ቤተሰባቸውን አነጋግሮ ያረጋገጠ እማኝ ለኢትዮ 12 የአዲስ አበባ ተባባሪ አመልክቷል።


Exit mobile version