Site icon ETHIO12.COM

ትግራይ፡ የተባበሩት መንግስታት ለተጎጂዎች የ36 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ አደረገ

የተባበሩት መንግሥታት በሰሜናዊ ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ባለው ግጭት ምክንያት ለተጎዱ ሰዎች የሚሆን 36 ሚሊየን ዶላር የድንገተኛ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቋል።

የተባበሩት መንግስታት እንዳለው 25 ሚሊየን ዶላር የሚሆነው የድጋፍ ገንዘብ የታመሙትንና ጉዳት የደረሰባቸውን ለማከም የሚረዱ መድሀኒቶችን ለመግዛት እንዲሁም ምግብና ንጹህ የመጠጥ ውሃ ለማቅረብ የሚውል ነው።

ቀሪው 10.6 ሚሊየን ዶላር ደግሞ በጎረቤት አገር ሱዳን ለሚገኙ በሺዎች ለሚቆጠሩ ስደተኞች መጠለያዎችን ለመገንባት፣ የጤና አገልግሎት ለመስጠት እና ንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ለማረጋገጥ ይውላል ተብሏል።

” እንዲህ አይነት ግጭቶች አንድ ጊዜ ከቁጥጥር ውጭ ከሆኑ በኋላ ለማስቆም ከባድ ናቸው። የሞቱትን መመለስ አይቻልም፤ ሰዎች ላይ የሚደርሰውም ሀዘን ለዘላለም የሚኖር ነው። በአሁኑ ሰአት ህጻናት እርዳታ ማግኘት አልቻሉም። ምንም ገደብ በሌላው መልኩ እንድንንቀሳቀስ ሊፈቀድልን ይገባል” ብለዋል በተባበሩት መንግስታት የድንገተኛ እርዳታ አስተባባሪው ማርክ ሎውኩክ።

በሌላ በኩል በትግራይ ክልል ባለው ግጭት ምክንያት 2.3 ሚሊዮን የሚሆኑ ህፃናት ከሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ውጪ መሆናቸውን የተባበሩት መንግሥታት ከትናንት በስቲያ ማስታወቁ የሚታወስ ነው።”ከእነዚህ ውስጥ አብዛኛዎቹ ስደተኛና የተፈናቀሉ ናቸው። በአጠቃላይ ህፃናቱን መጠበቅ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ሥራ ነው” በማለት የተባበሩት መንግሥታት የዓለም አቀፉ የህፃናት መርጃ ድርጅት (ዩኒሴፍ) ኃላፊ አስታውቀዋል።

ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር የሰብዓዊ እርዳታዎችን ለማድረስ ስምምነት ላይ ቢደረስም ድርጅቶቹ በክልሉ የእርዳታ አቅርቦት ለማድረስ አልተቻለም እያሉ ነው።

የኢትዮጵያ መንግሥት ከትግራይ ኃይሎች ጋር የገባበት ግጭት የተቀሰቀሰው ጥቅምት 24/ 2013 ዓ.ም እንደነበር የሚታወስ ሲሆን በዚህ ግጭት በርካታ ሰዎች ሲገደሉ ከ60 ሺህ በላይ የሚሆኑ ደግሞ ወደ ጎረቤት አገር ሱዳን መሰደዳቸው ይነገራል።

“ለህፃናቱ የሚሰጠው እርዳታ አቅርቦት በዘገየ ቁጥር፣ ምግብ፣ በችግር ለተጋለጡት ህፃናትን ለማድረስ የሚያስፈልጉ ሌሎች አልሚ ምግቦች፣ ህክምና፣ ውሃ፣ ነዳጅና እና ሌሎችም አስፈላጊ ነገሮች እያጠሩ ወደ ከፋ ሁኔታ ያመራሉ” ብሏል ዩኒሴፍ ባወጣው መግለጫ።

አክሎም “አፋጣኝ፣ ዘላቂ፣ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ማንንም ባላገለለ መልኩ የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት ለየትኛውም ቤተሰብ በያሉበት እንዲመቻች እንጠይቃለን” ብሏል ድርጅቱ።

ባሳለፍነው ሳምንት ደግሞ የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ተቋም በትግራይ ወታደራዊ ግጭት ከተከሰተ በኋላ በክልሉ የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች ሁኔታ አሳስቦኛል ማለቱ የሚታወስ ነው።

ድርጅቱ ኤርትራውያን ስደተኞች መገደላቸውን እንዲሁም በግድ ታፍነው ወደ ኤርትራ እየተወሰዱ እንደሆነ የሚያሳዩ ሪፖርቶች እጅግ እንዳሳሰበው አስታውቋል።

የተመድ የስደተኞች ክንፍ ኃላፊ ፊሊፖ ግራንዲ ስደተኞቹን እንዳጋጠሙ የተጠቀሱት ድርጊቶች ተፈጽመው ከሆነ ከፍተኛ የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ነው ብለዋል።

ባሳለፍነው ሳምንት አርብ ዕለት ኤርትራውያን ስደተኞችን በተመለከተ የኢትዮጵያ መንግሥት፤ የተካሄደው ወታደራዊ ዘመቻ ምንም አይነት ስጋትን የሚደቅን እንዳልሆነ አመልክቶ፤ ነገር ግን በተሳሳተ መረጃ ሳቢያ ከካምፖቻቸው ወጥተው ወደ አዲስ አበባ የሄዱ ስደተኞች እንዳሉ ገልጿል።

ጨምሮም በትግራይ ክልል ከሚገኙ የስደተኞች መጠለያዎች ወደ አዲስ አበባ የሄዱ ስደተኞችን እየመለሰ እንደሆነም አስታውቋል።

ትግራይ በሚገኙ የስደተኛ ማቆያዎች ካምፖች ውስጥ በአገራቸው ፖለቲካዊ እስርና አስገዳጅ ወታደራዊ አገልግሎትን የሸሹ ወደ 100 ሺህ የሚጠጉ ኤርትራውያን ስደተኞች እንደሚገኙ ይነገራል።

BBC Amharic

Exit mobile version