Site icon ETHIO12.COM

በትግራይ ለ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዜጎች እርዳታ ቀረበ- 9 ሚሊየን የኮቪድ19 ክትባት ሊገባ ነው

በትግራይ ክልል ለ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዜጎች የምግብ እና ምግብ ነክ ያልሆኑ እርዳታ እየቀረበ መሆኑን የአደጋ እና ስራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ ተናግረዋል።

ህግ ከማስከበሩ በፊት በክልሉ 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ዜጎች እርዳታ ፈላጊ እንደነበሩ ያነሱት ኮሚሽነሩ ህግ ማስከበሩ ከተጠናቀቀ በኋላ 780 ሺህ ዜጎች ተጨማሪ እርዳታ ፈላጊ ሆነዋል ብለዋል። በዚህም እስከ ትናንት ድረስ ለ2 ሚሊየን 7 ሺህ ዜጎች እርዳታ መቅረቡን ገልጸዋል።

200 ሺ ኩንታል ስንዴ እና የመንግስት 690 ሺህ የልማታዊ ሴፍቲኔት ስንዴ ጅቡቲ ወደብ መድረሱን በመጥቀስም በቅርቡ ለህብረተሰቡ ይሰራጫል ብለዋል። እርዳታ በማከፋፈሉ ረገድ የትራንስፖርት እና እርዳታን በፍትሃዊነት የማከፋፈል ችግር መኖሩን ጠቅሰዋል፡፡

አሁን ላይም ችግሩን ማህበረሰቡን እና የትራንስፖርት ድርጅቶችን በማስተባበር ለመፍታት እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል።

ዶክተር ሊያ ታደሰ

በሌላ ማህበራዊ ዜና በመጋቢት ወር መጨረሻ አልያም ሚያዚያ ወር መጀመሪያ ላይ እስከ 9 ሚሊየን የኮቪድ19 ክትባት ወደ ሃገር ቤት እንዲገባ እየተሰራ መሆኑን የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ ታደሰ ገለጹ፡፡

የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ ታደሰ በክትባቱ እና “እንድናገለግልዎ ማስክዎን ያድርጉ” በሚሉት ዘመቻዎች ዙሪያ መግለጫ ሰጥተዋል።

ለክትባቱ በዋናነት ቅድሚያ የሚሰጣቸው ዜጎችን የመለየት ስራ እየተሰራ ነውም ብለዋል። በዚህም የጤና ባለሙያዎች፣ የማህበራዊ ጤና ሰራተኞች፣ የህዝብ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ አካላት ቅድሚያ ይሰጣቸዋል ነው ያሉት፡፡

FBC

Exit mobile version