Site icon ETHIO12.COM

የጎተራ ማሳለጫ የመንገድ ፕሮጀክት ላይ የመሰላል መገጣጠሚያ ቱቦዎችን የሰረቀዉ ግለሰብ በፅኑ እስራት ተቀጣ


ተከሳሹ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. የወንጀል ህግ አንቀፅ 669/2/መ/ ስር የተመለከተውን ድንጋጌ በመተላለፍ በከባድ የስርቆት ወንጀል በተመሰረተበት ክስ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ በፅኑ እስራት እንዲቀጣ ተወስኖበታል፡፡

በአናፂነት ሙያ ተሰማርቶ ሲሰራ የነበረው የ30 አመቱ ተከሳሽ መገርሳ ናጌ የማይገባውን ብልፅግና ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ ጥር 20 ቀን 2013 ዓ.ም ከምሽቱ በግምት 4፡00 ሰዓት ሲሆን በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 04 አስተዳደር ክልል ልዩ ቦታው ቄራ አካባቢ አዲስ በመሰራት ላይ ከሚገኘው የጎተራ ማሳለጫ መንገድ ዋሻ ውስጥ ነዉ ስርቆቱን የፈጸመዉ፡፡

ንብረትነታቸው ተከሳሹ በቀን ሰራተኝነት ተቀጥሮ ሲሰራበት የነበረዉ ሲ.ኤፍ.ኤች.ኢሲ. የመንገድ ፕሮጀክት የሆኑ ጠቅላላ የዋጋ ግምታቸው 11,550 (አስራ አንድ ሺህ አምስት መቶ ሀምሳ ብር) የሚያወጡ ብዛታቸው 33 የመሰላል መገጣጠሚያ ቱቦ ብረቶችን ማዳበሪያ ውስጥ ሞልቶ ተሸክሞ በመሄድ ላይ እያለ እጅ ከፍንጅ የተያዘ በመሆኑ በፈፀመው ከባድ የስርቆት ወንጀል መከሰሱን የዓቃቤ ህግ የክስ መዝገብ ያስረዳል፡፡

በዐቃቤ ህግ የቀረበውን ከባድ የስርቆት ወንጀል የክስ መዝገብ የተመለከተው በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቂርቆስ ምድብ የወንጀል ችሎት ተከሳሹ በእማኝነት የቀረበበትን የሰው ምስክሮችንና የኢግዚቢት ማስረጃን በማስመልከት እንዲከላከል ቢያዝም ተከሳሽ ማስተባበያ ማቅረብ ባለመቻሉ የካቲት 01 ቀን 2013 ዓ.ም በዋለው ችሎት ተከሳሽ መገርሳ ናጌን በ5 አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ወስኖበታል፡፡

የጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ድረ ገጽ

Exit mobile version