Site icon ETHIO12.COM

በቤኒሻንጉል ከ45 በላይ አመራሮች በህግ ጥላ ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው ነው

“በመተከል ዞን ከ60 በላይ በሚሆኑ ቀበሌዎች የአስተዳደር እና የፀጥታ መዋቅሩ በአዲስ መልኩ እንዲደራጅ ተደርጓል”

አቶ ተስፋዬ ቤልጂጌ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማዕከል ማስተባበሪያ ዘርፍ ኃላፊ ሚኒስትር

ወርቁ ማሩ

አዲስ አበባ ፦ በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል መተከል ዞን ከ60 በላይ ቀበሌዎች የአስተዳደር እና የፀጥታ መዋቅሮች እንደአዲስ መዋቀራቸው ተገለፀ።

የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማዕከል ማስተባበሪያ ዘርፍ ኃላፊ ሚኒስትር እና በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተዋቀረው የተቀናጀ ግብረሃይል የፖለቲካና ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ ቤልጂጌ በተለይ ከአዲስ ዘመን ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ እንደገለፁት፣ ግብረሃይሉ ስራ በጀመረበት ወቅት በአካባቢው ከፍተኛ የፀጥታ ችግር እንደነበር አስታውሰው፣እነዚህን ችግሮች ለመፍታት የተለያዩ እርምጃዎች ተወስደዋል።

የመተከል ችግር የተለያዩ የውስጥና የውጭ ሃይሎች የተሳተፉበት ነበር ያሉት አቶ ተስፋዬ፣ በውስጥ በየደረጃው ያለው የመንግሥት እና የፀጥታ መዋቅር የተሳተፈበት መሆኑ ችግሩን ውስብስብ እና አስቸጋሪ እንዳደረገው ጠቁመዋል። ከዚህ አንጻር መሳሪያ ጭምር ለጥፋት ሃይሎች የሚያቀብሉ የፀጥታ አካላት እንደነበሩ ማረጋገጥ መቻሉንም ጠቁመዋል፡

ችግሩን ከመሰረቱ ለመፍታትና የዞኑን ሰላም ለመመለስ ከተወሰዱ እርምጃዎች ውስጥ አንዱ የችግሩ አካል የሆኑ አመራሮችና የፀጥታ አካላትን የመለየትና ተገቢውን እርምጃ የመውሰድ ስራ አንዱ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ተስፋዬ፤ ህብረተሰቡን የሚመስል የአስተዳደር እና የፀጥታ መዋቅር እንዲኖር ለማድረግ ሰፊ ስራ ተሰርቷልም ብለዋል።

ከዚህ አንጻር በክልሉ ከ45 በላይ አመራሮች በህግ ጥላ ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሆነና የማጥራት ስራው ከህብረተሰቡ ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሆነ ገልጸዋል።

በዞኑ የሚገኘው የመንግሥት እና የፀጥታ መዋቅር ህብረተሰቡን በሚመስል መልኩ ሁሉንም በማካተት ማዋቀር ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠት ጠቃሚ በመሆኑ በ61 ቀበሌዎች አስተዳደሩን እና የጸጥታ መዋቅሩን የማጥራትና በአዲስ መልኩ የማደራጀት ስራ መሰራቱን ገልፀዋል።

የመተከል ዞን በርካታ ብሄር ብሄረሰቦች የሚኖሩበት የኢትዮጵያ ተምሳሌት ነው ያሉት አቶ ተስፋዬ፤ ይህንን ታሳቢ በማድረግ የፀጥታ መዋቅሩ ህብረተሰቡን ባሳተፈ

 ሁኔታ አዳዲስ የሚሊሻ ሰራዊት አባላትን ምልመላ በማካሄድ የማሰልጠንና ወደስራ የማስገባት ስራ መሰራቱን ጠቁመዋል።

በዞኑ ከሚገኙ ወረዳዎች ሰባት ወረዳዎች ስድስቱ ችግር የነበረባቸው እንደነበሩ የጠቁሙት አቶ ተስፋዬ፣ በነዚህ ወረዳዎች ውስጥ 75 ሺህ ከሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ውይይት በማድረግ ችግሩን የመለየት ስራ መሰራቱንም አመልክተዋል።

እንደ አቶ ተስፋየ ገለፃ፣ የኦፕሬሽን ስራዎች በተሳካ ሁኔታ እየተካሄዱ ሲሆን በዚህም ጫካ የገባው ህዝብ በሰላማዊ መንገድ ወደቤት እየገባ ያለበት ሁኔታም እየተፈጠረ ይገኛል። ከዚህም ባሻገር በተሳሳተ መንገድ ከጥፋት ሃይሉ ጋር የተሰለፉ አንዳንድ ሃይሎችም እጃቸውን በሰላማዊ መንገድ ለጸጥታ ሃይሉ በመስጠት ወደሰላማዊ ህይወት እየተመለሱ ነው። 

እስካሁን ድረስ በነበረው ችግር የተፈናቀሉ ዜጎች ከ124ሺህ በላይ መሆናቸውን የተናገሩት አቶ ተስፋዬ፤ ለነዚህ ወገኖች ሰብአዊ ድጋፍ የማቅረብ እና በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ወደቀዬአቸው ለመመለስ እየተሰራ ነው ብለዋል።

ከዚህ ጋር ተያይዞ ግን እነዚህ ዜጎች ወደቀደመው ቤታቸው ሲመለሱ ዳግም ሌላ ችግር እንዳይከሰት የቅድመ ዝግት ስራዎች እየተሰሩ እንደሆነ ፣ ከዚህም ጎን ለጎን የእርቅ፣ የአብሮነትና ቁስል የማከም ስራዎች እንደሚሰሩ አብራርተዋል።

እንዲህ አይነት ግጭቶች ለማንም አይጠቅሙም ያሉት አቶ ተስፋዬ፣ በአካባቢው በተፈጠረው ችግር በርካታ ዜጎች ሞተዋል፤ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩት ተፈናቅለዋል፤ ሃብት ንብረት ወድሟል፣ስለዚህ ከዚህ ትምህርት ወስደን ለዘላቂ ሰላም መስራት ከሁሉም ይጠበቃል ብለዋል። በዞኑ በተፈጠረው ችግር በአካባቢው 42 ፕሮጀክቶች መቆማቸውንም ጠቁመዋል።

አዲስ ዘመን የካቲት 8/2013

Exit mobile version