ETHIO12.COM

የአምነስቲ ” ሽንቁረ ብዙ” ሪፖርት የተከፋዮች የቲውተር ዜና ድምር

አገር መከላከያ ባላሳበው መንገድ ተጨፍጭፏል። በመኪና ተጨፍልቋል። እንደጠላት ” ሌባ ” እየተባ ባዶ እግሩን መሳሪያ ተወድሮበት ተተፍቶበታል፤ ብወልቃይት ጠገዴ፣ በራያ የሚኖሩ ሰዎች ላይ የተፈጸመው ግፍ፣ በማይክድራ በቢላ የሰው ልጆች ሲታረዱ ወዘተ መረጃ እያለ አምነስቲና የዓለም ሚዲያዎች አልጮሁም። እርግጥ በአክሱም ጥፋት ተፈጽሞ ሊሆን ይችላል። ሰዎች ተገድለው ሊሆን ይችላል። የአምነስቲ የተዋከበ ሪፖርት ግን ዓላማው ፍትሃዊ የማይመስለው በመግቢያው በተቀመጠው መሰረት ነው።

የአገር መከላከያ ሰራዊት በባዶ እግራቸው በትግራይ

አምነስቲ ተክለፍልፎ ይፋ ያደረገው ሪፖርት ያለማመንታት ኤርትራን በከባዱ ኢትዮጵያን በመጠኑ ጥፋተኛ አድርጎ በግምት ተገደሉ ላላቸው 200 የሚጠጉ የአክሱም ነዋሪዎች ፍትህ ጠያቂ ሆኗል። ሪፖርቱ የእነ ማርቲን ፕላውትና የሌሎች ተከፋዮች ጩከት ድምር ቢሆንም እነሱ ከማይካድራው የቢላና የገጀራ ጭፍጨፋ ጋር ለማመሳሰል 800 ወይም ከዛ በላይ ይደርሳል ሲሉ ቢከርሙም አምነስቲ 200 አድርጎ ቁጥሩን ማሳነሱ የሚመታውን ከበሮ መጠን የቀነሰው ሆኗል።

የአምነስቲ ኢንተርናሽናል የአፍሪቃ ቀንድ ተመራማሪ አቶ ፍስሃ ተክሌ እንዳሰባሰቡት የሚነገርለት ይህ ሲጀመር የስልክ መረጃ አምነስቲን ተዓማኒ እንደማያደርገው የሚያምኑ በርካታ ናቸው። እንደውም አቶ ፍስሃ ታሪካዊ ሃላፊነታቸውን እየተወጡ እንደሆነ ከሪፖርቱ ጎን ለጎን ከፍተኛ ጩኸት እየተሰማ ነው።

ቀደም ሲል አቶ ፍስሃ ኦነግ ሸኔ የፈጸመውን ጥቃት ያለ በቂ ማስረጃ በስልክ ምስክር ሰማሁ በሚል መንግስት ላይ አላከው ሲያበቁ ድርጅታቸው ይቅርታ ጠይቆ ነበር። ለውጡን ተከትሎ አዲሱ መንግስት ላይ ክራንቻቸውን ካሾሉት ተቋማትና ሚዲያዎች አንዱ የሆነው አምነስቲ ዛሬ ይፋ ያደረገው ያላላቀ ሪፖርት፣ መንግስት ሰባት የሚሆኑ ሚዲያዎችን በጋበዘበት ማግስት መሆኑ ጥርጣሬውን አግዝፎታል። ከተፈቀደ በደንብ አጣርቶ መስራትን ምን ከለከለው የሚለው ሃስብም ሚዛን የሚደፋ እየሆነ ነው።

መንግስት ዘግይቶም ቢሆን በሩን ከፍቶ በርዳታ እህል ስርጭትና መድሃኒት አቅርቦት ላይ ሲነሳበት የነበረውን ሃሜት በአካል ተገኝተው ምስክር በሆኑ የዓለም ዓቀፍ ተቋማት አንደበት ማመጣጠን ተችሏል። በዚህም ዛሬ ላይ 3.5 ሚሊዮን የትግራይ ህዝብ እህል እያገነ፣ ተመሳሳይ እርዳታ እየቀረበለት ነው። ይህ እንደ መልካም ሲነሳ ግን አይታይም።

በትግራይ የተካሄደው ህግን የማስከበር ዘመቻ መነሻ ምክንያቱ በመከላከያ ሰራዊት ላይ በተከፈተ የክህደት ጭፍጨፋ፣ ዘግናኝ ግፍና ሊታመን የማይችል በደል መሆኑ የጸሃይ ላይ እውነት፤ መንግስት በቁጥር ያልነገረን የአገር መከላከያ ሰራዊት አባልት ጭፍጨፋ ለዓለም መገናኛዎችም ሆነ ዓለም አቀፍ የመብት ተከራካሪዎች አጀንዳ አለመሆኑ ዜጎችን አሳዝኗል። ምክንያቱንም እንዲመረመሩ አድርጓቸዋል።

ከምንም በላይ ታዛቢዎችና ሚዲያዎች ወደ ትግራይ ገብተው እንዲዘግቡ በተፈቀደ ማግስት አምነስቲ የህወሃት ወኪል ናቸው የሚባሉትን የእነ አቶ ተክሌን የስልክ ወሬ ብቻ ሰብስቦ በሳተላይት ምስል ብመአስደገፍ ግምቱን ማስቀመጡ ሌላው አነጋጋሪ ጉዳይ ነው።

“ቀዳዳ የበዛው የአምነስቲ ሪፖርት”  ሲሉ  የቅድሚያ አስተያየት የሰጡት በፊስ ቡክ አንቂነት የሚታወቁት Samson Michailovich ሳምሶን ሚካሎቪች ናቸው። የሪፖርቱ ቀዳዳዎች ሲሉ ያነሱዋቸው መሰረታዊ ነጥቦች

፩. አምነስቲ ኢንተርናሽናል አክሱም ላይ ግድያ የተጀመረው የኢትዮጵያና ኤርትራ ወታደሮች ለቀናት ከተማዋን ያለማቋረጥ በከባድ መሳሪያ ሲደበድቡ ነው ይላል። ነገር ግን ህወሃትም የኢትዮጵያ መንግስትም አክሱም ከተማ ላይ የረባ ጦርነት እንዳልተካሄደ አረጋግጠዋል።

ህወሃት የከተማው ህዝብ እንዳይጎዳ አክሱም ውስጥ ጦርነት አላደረግኩም ባይ ነው። መረጃዎች እንደሚያሳዩት ብርቱ የከተማ ጦርነት የተካሄደው በዛላምበሳ ፣ አዲግራትና ውቅሮ ከተሞች ውስጥ ብቻ ነው። ከዚህም በተጨማሪ Armed Conflict Location & Event Data Project የተባለ ዓለም አቀፍ ተቋም አክሱም ላይ የረባ ጦትነት አልተካሄደም የሳተላይት መረጃዎች ይህንን ክስ አይደግፉም ሲል ሪፖርት አቅራቢዎቹ ላይ ሂስ አቅርቧል።

፪. ሁለተኛው ጥያቄ ውስጥ የሚገባው ጉዳይ የኢትዮጵያ ሰራዊት አክሱምን ተቆጣጠረ ከተባለ በኃላ ተካሄደ የተባለው ” ጭፍጨፋ ” ነው። ብዙ የህወሃት የፕሮፖጋንዳ ኣውታሮች አክሱም ላይ ጭፍጨፋ የተካሄደው በአመታዊው የጽዮን ንግስ በአል ላይ የኤርትራ ወታደሮች ታቦተ ጽዮኑን ካልወሰድን በማለታቸው በተፈጠረ ግርግር መንስኤ ነው ይላሉ። የዛሬው የአምነስቲ ሪፖርት ደግሞ ” ጭፍጨፋው” የተካሄደው ከአክሱም ጽዮን ክብረ በአል አስር ቀናት ቀደም ብሎ ነው ይላል። መንስኤውም የህወሃት ሚሊሺያ የወታደሮችን ካምፕ በማጥቃቱ በተወሰደ ምላሽ ነው ይላል።  እነ Martin Plaut ‘ በጭፍጨፋው’ ከ 800 ሰዎች በላይ በአንድ ቀን አለቁ ይላል። አምነስቲ ኢንተርናሽናል ቁጥሩን ወደ 200 ያወርደዋል።

፫. የአምነስቲ ሪፖርት ትልቁ ክፍተት ምርመራውን አደረግሁበት ያለው ዘዴ methodology ነው። ዋናው የመረጃ ምንጩ ሱዳን ውስጥ በስደት ያሉ ከአክሱም መጣን ያሉ ሰዎች ጋር የተደረገ የስልክ ቃለመጠይቅ ነው። ከዚያ በተጨማሪ የሳተላይት ምስሎችን ተጠቅሜያለሁ ባይ ነው። ምስሎቹ ቤተክርስቲያን የተካሄዱ የቀብር ስፍራዎችን በማየት መረጃ ለማሰባሰብ የተካሄደ ሙከራ ነው። አምነስቲ አንድም የምርመራ ባለሙያ በአካል ወደ አክሱም አላከም።

ሱዳን ውስጥ ስደት ላይ ያሉት የትግራይ ተወላጆች ብዙሃኑ ከሁመራና አካባቢው የተሰደዱ መሆኑን ላጤነ ፣ የኢትዮጵያ መንግስት ሁመራን ከተቆጣጠረ በኃላ ወደ ሱዳን የሚካሄድ ፍልሰትን ማገዱን ላስተዋለ በእርግጥ ስደተኞቹ ከአክሱም የመጡ ናቸው ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው።

ማጠቃለያ :

አምነስቲ ዝርዝር ጉዳዮችን ያካተተ ሪፖርት አቀርባለሁ ብሎ ጥቅል እና እርስ በራሱ የሚጋጭ ሪፖርት መሰል ነገር አቅርቧል። በግሌ አምነስቲ የህወሃት ጥፋተኝነትን የማላከክ ዘመቻ blame shifting campaign ሰለባ ሆኗል ባይ ነኝ። ህወሃት ጦርነቱን በሙሉ ልብ አሸንፋለሁ ብሎ ጀምሯል ፣ ያ ሳይሆን ሲቀር አሸነፉኝ የሚላቸው ሀይሎች ላይ ክስ የማዝነብ ዘዴን እንደ መልስ ምት እየተጠቀመ ነው። የአክሱም ጉዳይ ሲገርመን በቅርቡ መንግስት ‘ አቶሚክ ቦምብ ‘ ተጠቅሟል የሚሉ ቀልድ የሚመስሉ የሀሰት ክሶችም ማድመጥ ጀምረናል።

ለማንኛውም ከአምነስቲ ሪፖርት ይልቅ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን እያዘጋጀው ያለውን ሪፖርት መጠበቅ ይሻላል። ኢሰመኮ ወደ አክሱም መርማሪዎችን የላከ ሲሆን በአካባቢው በተካሄደው ጦርነት የተሳተፉትን የሁሉንም አካላት መረጃ ስለሚያካትት ሪፖርቱ ለእውነት የቀረበና ሚዛናዊ ይሆናል ብዬ እጠብቃለሁ።

ከአቶ ሳምሶን ሃሳብ በተጨማሪ ኢዜአ የሚከተለውን ዘግቧል።

“አክሱም ከተማን በተመለከተ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ያወጣው ሪፖርት የተጠቀመው የመረጃ ምንጭ ፍትህን ለማስፈን ዓላማ አይጠቅምም” ሲል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ።

ተቋሙ ለመረጃ ምንጭነት የተጠቀመው በምስራቅ ሱዳን በስደተኞች መጠለያ ጣቢያ የሚገኙ ሰዎችን እንዲሁም ውስን የአክሱም ነዋሪዎችን በስልክ ቃለ መጠይቅ ማድረጉ የተሟላ ምስል ለመያዝ እንደማያስችል ተጠቁሟል።

አምነስቲ ኢንተርናሽናል ያወጣው ሪፖርት አስመልክቶ የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ህወሃት በኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ላይ እ.ኤ.አ ኖቬምበር 4 ቀን 2020 ያደረሰው ጥቃት ተከትሎ በትግራይ ክልል የህግ ጥሰትና ስርዓት አልበኝነት ተፈጥሯል ብሏል።

በክልሉ ውስጥ የተከሰቱት ውስብስብ ችግሮች ህወሃት የፈጸመው የክህደት ተግባር ቀጥተኛ ውጤቶች እንደሆኑ ገልጾ፤ “በክልሉ ለተፈጠረው የህግ ጥሰት ኃላፊነቱን መውሰድ ያለበት አካል ከህወሓት ውጭ ማንም የለም” ሲል በመግለጫው አመልክቷል፡፡

የህወሃት የጥፋት ቡድን በመከላከያ ሰራዊት ላይ ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎ በግድያ እና በሌሎች የወንጀል ድርጊቶች መሰማራቱንም አስገንዝቧል።

“መንግሥት በትግራይ ክልል የወሰደው ሕግ የማስከበር ሥራዎች አጠቃላይ ዓላማ በክልሉ ውስጥ ሕግና ስርዓትን ለማስፈን እና ወንጀለኞች ለፍርድ ለማቅረብ ነው” ያለው መግለጫው፤ ወንጀኞችን ለህግ ለማቅረብ የተካሄደው ዘመቻ በሲቪሎች እና በሲቪል ተቋማት ላይ ጉዳት እንዳያስከትል ከፍተኛ ጥንቃቄ መደረጉን አውስቷል።

በትግራይ ክልል በተለይም በአክሱም ከተማ ተፈጽመዋል የተባሉ ወሲባዊ ጥቃቶች እና ሌሎች ክስተቶችን ጨምሮ የደረሰው የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እጅግ አሳሳቢ ጉዳዮች መሆናቸውን ያመለከተው መግለጫው፤ ለዚህም መንግስት አስፈላጊውን ምርመራ ለማድረግ እና አጥፊዎችን በህግ እንዲጠየቁ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑንም አመልክቷል።

“በማይካድራ ከተፈፀመው ጭፍጨፋ ጋር ተመሳሳይ በሆነ መልኩ በአክሱም ከተማ ተፈጽሟል የተባለው የወንጀል ድርጊት በጥልቀት መመርመር ይኖርበታል” ብሏል ፡፡

የምርመራ ሥራውን ለማከናወን ከፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ እና ከፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የተውጣጣ ቡድን ወደ ትግራይ ክልል መሄዱን አመልከቷል።

የእነዚህ ምርመራዎች ውጤት እና ቡድኑ በሚያቀርባቸው ምክረ ሃሳቦች መንግስት ወንጀለኞችን ለፍርድ ለማቅረብ እና በክልሉ ተከስተዋል የተባሉ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እና ሁከቶችን በጥልቀት ለመፍታት ያስችላቸዋል ሲል ገልጿል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ በማይካድራ በንፁሃን ዜጎች ላይ በደረሰው ጭፍጨፋ በቀጥታ የተሳተፉ 36 ሰዎች በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት መቅረባቸው ልብ ሊባል ይገባል ብሏል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመግለጫው፡፡

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በሰብዓዊ መብቶች ጉዳዮች ላይ ምርመራ ሲያደርግ እና ሪፖርት ሲያቀርብ መቆየቱን ያመለከተው መግለጫው፤ “የኮሚሽኑ የምርመራ ውጤት በጊዜው ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ይፋ ይደረጋል” ብሏል፡፡

በአክሱም ከተማ ተከስተው ከነበሩት ክስተቶች ጋር ተያይዞ በቀረቡ ክሶች ላይ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ዛሬ ሪፖርቱን ይፋ ማድረጉን ያመለከተው መግለጫ፤ ሪፖርቱ በጣም አሳሳቢ የሆኑ ጉዳዮችን መዳሰሱን ጠቅሶ፤ “ነገር ግን ሪፖርቱን በማዘጋጀት ሂደት የተጠቀሙበት ዘዴ በምስራቅ ሱዳን ከሚገኙ ስደተኞች በተሰበሰበ መረጃ እና በአክሱም ካሉ ግለሰቦች ጋር በስልክ ቃለ-መጠይቅ ላይ የተመሠረተ ነው” ብሏል፡፡

ለአብነትም በሪፖርቱ ከተጠቀሱት ምንጮች መካከል አንዱ አምነስቲ ሪፖርት ላይ እንደተጠቀሰው ቄስ ሳይሆን በቦስተን የሚኖር ግለሰብ መሆኑንም በመግለጫው አመልክቷል።

ስለሆነም በእንደዚህ አይነት ምንጮች ላይ የተመሠረተ ዘገባ ፍትህን ለማስፈን ዓላማ አይጠቅምም ብሏል።

ከዚህ ይልቅ በህወሃት እና ግብረ አበሮቹ የሚነዛውን የተሳሳተ መረጃ እና ፕሮፓጋንዳ የበለጠ የማጠናከር አደጋ እንዳለው አሳስቧል።

አምነስቲ ኢንተርናሽናል ክልሉን በመጎብኘት እና የኢትዮጵያ መንግስት ባለሥልጣናትን በማነጋገር እውነቱን በማጋለጥ አስፈላጊውን የመስክ ሥራ ማከናወን ይገባው እንደነበርም በመግለጫው አመልክቷል።


Exit mobile version