Site icon ETHIO12.COM

ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ “የመደመር መንገድ” ማስታወሻ

ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ “የመደመር መንገድ” ብለው በሰየሙት መጽሐፍ የምረቃ መርኀ ግብር ላይ፣ ጽሑፋዊ ይዘቱን በተመለከተ ምልከታዬን እንዳቀርብ መድረክ አግኝቼ ነበር፡፡

በዕለቱ ለአቀራቤ የመጀመሪያ ርዕሰ ጉዳይ ያደረግኩት፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዐዲስ መጽሐፍ መጻፋቸውን የሰሙ አንዳንድ ወዳጆቼ እና በዕለቱ መድረክ እንዳለኝ የሚያውቁ ሰዎች፣ በጠየቁኝ ጥያቄ ነበር፡፡ ጥያቄውም፤ “ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጣም ሥራ የሚበዛባቸው ኾነው ሳለ፣ ብዙ ትርፍ ጊዜ እንዳለው ሰው መጽሐፍ በመጻፍ ለምን ጊዜያቸውን ያባክናሉ?” የሚል ነበር፡፡

ይህንን ጥያቄ፤ እንደ አንድ መምህር እና ሥነ ጽሑፋዊ ሥራዎችን እንደሚያደንቅ ብሎም እንደሚያከብር ሰው፣ ከግሌ ተነስቼ ያቀረብኩት ጥየቄ አልነበረም፡፡ ለዚህ ጥያቄ የግሌ ምክንያታዊ ምላሽ የነበረኝ ቢኾንም፣ ጠያቂዎቹ ምላሹን ከእኔ ከሚሰሙት ይልቅ፣ ከጉዳዩ ባለቤት ከደራሲው ዐንደበት ቢሠሙት የተሻለ ይኾናል ብዬ በማሰብ፣ ጥያቄውን በመድረኩ እንዳለ አቅርቤዋለሁ፡፡ እንዳሰብኩትም ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ተገቢውን ጊዜ ወስደው ለጥያቄው በቂ ምላሽ ሰጥተውበታል፡፡
እኔም ብኾን፤ ይህንን ጥያቄ እንዲሁ ወርውሬ ያለፍኩት አልነበረም፡፡ በመድረክ ዝግጅቴን ባቀረብኩበት ወቅት፤ በገጽ መዘለል ምክንያት ሐሳቡም አብሮ ተዘንግቶ አልቀረበም እንጂ፣ በዝግጅት ማስታወሻዬ ገጽ ሦስት ላይ እንደሚከተለው የራሴን ምላሽ ሰጥቼበት ነበር፡፡ (ይህንኑ የተዘለለውን ገጽ የማስታወሻ ጽሑፌን ከመድረኩ አዘጋጆች ለአንዱ በቫይበር ልኬለታለሁ፡

/ ዐቢይ አሕመድ፤ በጽሑፋቸው እና በተሠማሩበት የሥራ ዘርፍ መካከል ምንም ዓይነት ከሙያቸው የተነጣጠለ ክፍተት የለም፡፡ እንዲያውም፤ በመጽሐፉ ውስጥ የተነሱት ጥያቄዎች፣ ሐሳቦች እና ዐተያዮች ከሥራቸው ጋር በቀጥታ የተናበቡ ኾነው እናገኛቸዋለን፡፡ ይህንን ለማስረገጥ፤ በጽሑፋቸው ለትንታኔ የቀረቡትን ጥያቄዎች መመልከቱ ይበቃል፡፡ ኢትዮጵያዊነት ማለት ምን ማለት ነው? ሀገር ማለት ምን ማለት ነው? ኢትዮጵያን ወደ ብልፅግና እና ወደ ዴሞክራሲ እንዴት ልንወስዳት እንችላለን? ይቅርታ ለምን ይበጃል? ሰላማዊ ትግል ከዐመጽ እንዴት የተሻለ አካሔድ ሊኾን ይችላል? ከዚህ በፊት የፈፀምናቸውን ስኅተቶች እንዴት ልንሻገራቸው ወይም ልናርማቸው እንችላለን? የሚሉት በመጽሐፉ የተነሱት ጥያቄዎች፣ የድርሰቱን እና የሥራቸውን የገጽታ አንድነት የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡

የዶ/ር ዐቢይ መጽሐፍ ከሚሠሩት ሥራ በተነጠለ መልኩ፣ እንደ ውኃ ዋና ማሰተማሪያ፣ እንደ ልበ ወለድ፣ ወይም የቴኒስ ጨዋታ ሥልጠኛ ማንዋል ወዘተርፈ. ቢኾን ኖሮ፣ እኚህ ሰው፣ “ይህንን ለመጻፍ ጊዜውን ከየት አገኙት?” ይባል ነበር፡፡ “የመደመር መንገድ” ግን፣ በመጀመሪያ ለራሳቸው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የሐሳብ ጥራት ላይ ለመድረስ የጻፉት ሲኾን፣ በሌላ በኩል፤ ለዜጎች ግልጽ በኾነ መንገድ ሀገራቸውን በምን ዓይነት ፍልስፍና ላይ ተመርኩዘው እየመሯት እንደኾነ ለማስረዳት የተጻፈ መጽሐፍ ነው፡፡ ለዚህም ነው “መጽሐፉ የሥራቸው ክትያ እንጂ፣ ከሥራቸው ተነጥሎ ለብቻው የቆመ አይደለም፤” የምለው፡፡

Dr Dagnachew Assefa (ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ)

Exit mobile version