Site icon ETHIO12.COM

በማካይድራ ጭፍጨፋ ተሳትፎ አላቸው በተባሉ ተጠርጣሪዎች ላይ ዐቃቤ ህግ የቀዳሚ ምርመራ መዝገብ ከፈተ

በማካይድራ ለ229 ዜጎች ሞት፣ ለ10 ሴቶች መደፈር  እና ለ285 የአካል ጉዳት መድረስ ቀጥታ ተሳትፎ አላቸው በተባሉ ተጠርጣሪዎች ላይ ዐቃቤ ህግ የቀዳሚ ምርመራ መዝገብ መክፈቱን ገለጸ። ዐቃቤ ህግ ይህንን ያስረዳው ከ30 በላይ ተጠርጣሪዎች ዛሬ በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ የጊዜ ቀጠሮ ችሎት ለአራተኛ ጊዜ በቀረቡበት ወቅት ነው።

በዚህ ጊዜም የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል ምርመራ ቡድን ምርመራውን ማጠናቀቁንና የምርመራ መዝገቡን ለዐቃቤ ህግ ማስረከቡን አስታውቋል። ዐቃቤ ህግም ይህንን የምርመራ መዝገብ ተረክቦ ሌላ የመዝገብ ቁጥር 220760 የቀዳሚ ምርመራ መዝገብ መክፈቱን ገልጿል።

ተጠርጣሪዎቹ በማይካድራ ለ229 ዜጎች ሞት፣ ለ285 የአካል ጉዳት መድረስ እና በብሄራቸው እየተለዩ  ለ10 ሴቶች መደፈር እንዲሁም ከ7 ሚሊየን ብር በላይ የግልና የመንግስት ንብረት መውደም ተሳትፎ እንዳላቸውም አስረድቷል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ገጀራ፣ ቢለዋ እና የጦር መሳሪያ በመያዝ በቀጥታ ተሳትፎ እንደነበራቸው ነው ዐቃቤ ህግ ያብራራው ።

የማይካድራ ግፍ አንዱ ገጽታ

በዚህ ወንጀል በማነሳሳት የተሳተፉ አሉ ያለው ዐቃቤ ህግ በከፈትነው የቅድመ ምርመራ መዝገብም ተጠርጣሪዎቹ ከ15 ዓመት በላይ በሚያስቀጣ ወንጀል የተጠረጠሩ በመሆኑ ዋስትናቸው ውድቅ ተደርጎ በማረሚያ ቤት ይቆዩልኝ ሲል ጠይቋል።

የተጠርጣሪ ጠበቆች በበኩላቸው ከዚህ በፊት ፍርድ ቤቱ ተሳትፏቸው ተለይቶ ይቅረብ ብሎ ባዘዘበት ሁኔታ ተሳትፏቸው ሳይለይ የቅድመ ምርመራ መዝገብ መከፈቱ ተገቢነት የለውም ሲሉ ተከራክረዋል። ጉዳዩን የተከታተለው ፍርድ ቤቱም በወንጀል ስነስርዓት ህጉ 63/1 መሰረት የተጠርጣሪዎቹን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ በማድረግ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ አዟል።(ኤፍ ቢ ሲ)

Exit mobile version