Site icon ETHIO12.COM

መንግስት የአፍሪካ የሰብዓዊና ኮሚሽን ከኢሰመኮ ጋር በመተባበር በትግራይ ያለውን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እንዲያጣራ ፈቃደኛ ነው – ጠ/ሚዐቢይ

መንግስት የአፍሪካ የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮሚሽን ከኢሰመኮ ጋር በመተባበር በትግራይ ያለውን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እንዲያጣራ ፈቃደኛ ነው – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ

“የኢትዮጵያ መንግስት የአፍሪካ የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮሚሽን ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መመብት ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ጋር በመተባበር በትግራይ ያለውን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እንዲያጣራ ፈቃደኛ ነው” ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰሜን ኢትዮጵያ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ለአፍሪካ ህብረት ሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት ዝርዝር መግለጫ አቅርበዋል።

በመግለጫቸው የህወሃት ጁንታ በኢትዮጵያ ላይ ሲያደርስ የነበረውን ጥፋት ከመሰረቱ ጀምሮ ገልጸዋል።

ባለፉት ሶስት አመታት በአገሪቱ የመጣውን ለውጥ ለማደናቀፍ ሲያከናውን የነበረውን የጥፋት ድርጊትም አብራርተዋል።

የህወሃት ጁንታ ከጥፋት ድርጊቱ ታቅቦ ወደሰላማዊ መስመር እንዲገባ በተለያየ ጊዜ የተደረጉ ጥረቶችንም አውስተዋል።

ነገር ግን ቡድኑ ወደ ሰላማዊ መስመር ከመግባት ይልቅ ወደለየለት የወንጀል ድርጊት መግባቱን አውስተው፤ ህገ-መንግስታዊ ተቀባይነት የሌለው ምርጫ እስከማካሄድ መድረሱን አንስተዋል።

በመጨረሻም በአገር መከላከያ ሰራዊት የሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት በመፈጸም ሊታለፍ የማይችል ወንጀል በመፈጸሙ መንግስት ህገ መንግስቱንና የአገርን ሉዓላዊነት ለማስከበር ወደ ዘመቻ ለመግባት መገደዱን ገልጸዋል።

የህግ ማስከበር ዘመቻውን ተከትሎ በክልሉ የሰብዓዊ ድጋፍ እየተደረገ እንደሆነ ገልጸው፤ “84 ሜትሪክ ቶን ምግብ 4 ነጥብ 1 ሚሊዮን ለሚደርሱ ሰዎች እንዲከፋፈል ተደርጓል” ብለዋል።

በክልሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የፈጸሙ የህወሃት ቡድን አባላትን በቁጥጥር ስር የማዋልና በህግ ተጠያቂ የማድረግ ስራ እየተካሄደ እንደሆነም አመልክተዋል።

አህጉራዊ ተቋማትና የተቀረጹ የአሰራር ስርዓቶች እንዲተገበሩ ዝግጁ የሆነችው ኢትዮጵያ ተፈጸመ የተባለውን የመብት ጥሰት ከህብረቱ ጋር ለማጣራት መንግስት ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል።

“የኢትዮጵያ መንግስት የአፍሪካ የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮሚሽን ከኢሰመኮ ጋር በመተባበር በትግራይ ያለውን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እንዲያጣራ ፈቃደኛ ነው” ብለዋል በመግለጫቸው።

በኢትዮጵያ ባካሄደችው የህግ ማስከበር ዘመቻ ላይ የውጭ ጣልቃ ገብነትን እየተከላከለች እንደሆነ ገልጸው፤ ‘ለአፍሪካ ችግር አፍሪካዊ መፍትሄ የሚለው መርህ አሸናፊ እንዲሆን አፍሪካውያን ወዳጆቼ ከኢትዮጵያ ጎን እንድትቆሙ” እጠይቃለሁ” ብለዋል።

“በአፍሪካ ህብረት አባልነታችን እና የህብረቱ አባል አገሮች በዚህ ፈታኝ ወቅት ላሳያችሁን ህብረት እጅግ ደስተኞች ነን” ሲሉ ገልጸዋል።

“ለትግራይ ክልል ለሚደረገው የሰብዓዊ ድጋፍ ሂደትና አስተዳደሩን የማጠናከር ሂደት ያላችሁ ድጋፍና ግንዛቤ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በሙሉ ልብ እንተማመናለን” ብለዋል።

(ኢዜአ)

Exit mobile version