Site icon ETHIO12.COM

የኢ/እ/ኳ ፌዴሬሽን ለእነ ደራርቱና አሸብር ውዝግብ ከአቢጃ አስቸኳይ ውሳኔ ላከ፤ሙሉ ስራ አስፈጻሚው አቢጃ ምን ይሰራል?

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ስራ አስፈጻሚ አይቮሪኮስት ሆኖ በሁለት አመራሮቹ ላይ የእገዳ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቋል። ውሳኔው በጥድፊያ የተወሰነው ዶክተር አሸብርና ኮማንደር ደራርቱ የመራቸው ሰላማዊ ሰልፍ በኦሎምፒክ ኮሚቴ ጽህፈት ቤት መካሄዱንና ምርጫ መከናወኑንን ተከትሎ ነው። ከውሳኔው ፈጣንነት ይልቅ የስራ አስፈጻሚው ሙሉ በሙሉ ወይም ሶስት እጁ አይቮሪኮስት ተለቃቅሞ መሄዱ ዋና ዜና ህኗል።

እግር ኳስ ፌዴሬሽን እንዳለው በኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ምርጫ ላይ ውክልና ሳይኖራቸው ተሳትፎ አድርገዋል ያላቸው ሁለት አመራሮቹን አግዷል። ፌዴሬሽኑ ይፋ ያደረገው መረጃ የውክልና ደብዳቤ ለኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ በፈቃዳቸው ጽፈዋል ያላቸውን ጸሃፊም ለሃያ ቀን ቢሯቸው እንዳይገቡ አቢጃ ሆኖ ውሳኔ አስተላልፏል።

” የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ዛሬ መጋቢት 20/2013 ከቀኑ 10 ሰዓት በአቢጃ ኮትዲቯር ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ውክልና ሳይሰጣቸው በኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ምርጫ ተገኝተው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በመወከል ምርጫ የመረጡት የሴቶች እግር ኳስ ልማት እና ውድድር ኮሚቴ ሰብሳቢ 13ኛው ጠቅላላ ጉባዔ ድረስ ታግደው እንዲቆዩ ውሳኔ ተላልፎባቸዋል። በተጨማሪም ወ/ሮ ሶፊያ አልማሙን በምርጫው ተወዳዳሪ ሆነው እንዲሳተፉ ከኢእፌ እውቅና ውጪ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ሳይወስን ማንንም ሳያማክሩ ደብዳቤ የጻፉት የኢእፌ ም/ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ሰለሞን ገ/ስላሴ ይህ ስብሰባ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ ለ20 ቀናት ከስራ ታግደው እንዲቆዩ ውሳኔ ተላልፏል።” የሚል ደብዳቤ ከአይቮሪኮስት ያሰራቸው የግር ኳስ ፌዴሬሽን ይህን ውሳኔ ለመወሰን ኮረም የሚሞላ ከሆነ ጉዳዩ ሌላ አነጋጋሪ አጀንዳ ይሆናል።

ከአይቮሪኮስት ጋር የሚጫወተው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሆኖ ሳለ፣ ከድጋፍ ሰጪ አካላት ሃኪሞች፣ የቡድን መሪ፣ወጌሻ፣ አስልጣኞችና እጅግ አግባብ ያላቸው ካልሆኑ በቀር የስራ አስፈሳሚ ኮሚቴ አባላቱ ተንጋገተው ለቀናት አቢጃ የሚቀመጡበትና የዶላር አበል የሚወስዱበት አግባብ ሊያስተይቃቸው እንደሚገባ እየተነገረ ነው።

ምርጫ ከተደረገ በሁዋላ እግድ ማድረግ ምን ውጤት እንደሚያመጣ ባይታወቅም፣ እግዱ የሚጸናውና የታገዱት ጸሃፊ የጻፏቸው ደብዳቤዎች ህጋዊ የማይሆኑት ከታገዱ በሁዋላ የሚጽፋቸው ደብዳቤዎች ወይም ግንኙነትቶች ብቻ እንደሆኑ ስለ አሰራሩ የሚያውቁ ይናገራሉ።

ዶክተር አሸብር በተደጋጋሚ በፍጥነት ነገሮችን ህጋዊ ሽፋን አላብሶ የመከወን ችሎታ እንዳላቸው ከልምድ ይታወቃል። ይህንን የሚገነዘቡ ወገኖች እንደሚሉት እግር ኳስ ፌዴሬሽን እንደወከላቸው ደብዳቤ የተሳፈላቸው እንስት ምርጫ ተጠናቆ ስማቸው ለዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ከተላለፈ የአቡጃው የሽርሽር ደብዳቤ ” ተበሏል” ከሚል የዘለለ ፋይዳ የለውም።

ኮማንደር ደራርቱ ትላንት ደምቃ፣ ሰባት ሚሊዮን ብር ተሸላማ፣ 20 ሚሊዮን የሚያወጣ መኪና ተበርክቶላት ዜናው አየሩን በሞላበት ቅጽበት የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ስትመራ ውላለች። ለፖሊስ ቃሏን ሰጥታለች። ወይም ፖሊስ ዘንድ ሄዳለች። ዶክተር አሸብር ኦሊምፒክ ኮሚቴን አዘገተው የሚፈልጉትን አድርገዋል። የዝግጅት ክፍላቸን ማወቅ ያልቻለው አዲሱ ምርጫ ለኦሊምፒክ ኮሚቴ የመላኩን ጉዳይ ነው።

ከዚህ አንጻር ዶክተር አሸበር ነገሮችን ህጋዊ አድርገው በፈለጉት መልኩ አበጅተው ካሳወቁ ጉዳዩን ቀስ ብሎ ከህግ አንጻር መርምሮ የሚዳኙበትን ህጋዊ አግባብ መፈለግ እንጂ በግርግርና በሰለፍ የሚሆን ነገር አይኖርም። የተጣሰ ህግና ዓለም ዓቀፍ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ሊቀበልበት የሚችልበት አጋብብ ካለ አጥንቶና የህግ ባለሙያዎች መርመረውት ማስተካከያ እንዲደረግበት ማድረግ እንጂ በጋጋታ ውሳኔ ለማስቀልበስ መታደፍ ” ፖለቲከኞች ስፖርቱ ውስጥ ገቡ” ያስብልና ልክ በግር ኳሱ ዓለም እንደሳቀብን ሌላ ታሪክ እንደግማለን።

ዛሬ አገራችን በውጭ ምንዛሬ እጥረት በታነቀችበት ወቅት የእግር ኳ ፌዴሬሽን አመራሮች ለአንድ ሳምንት ሆቴል ተቀምጠው የሚቀለቡ፣ አበል በዶላር ወስደው ጫጉላ ላይ መሆናቸው ለዚህ ዘጋቢ ከዋናው ዜና በላይ ትልቁ ጉዳይ ነው። ለነገሩ እንደ ዱቤ አይነት የስፖርት መሪ ባለበት አገር ምንም የሚጠበቅ ነገር አለመኖሩን ለሚረዱ ዜናው ንዴት ከመፍጠር የዘለለ ምንም ለውጥ አያመጣም።

የኢትዮጵያ ብሄራዊ እግር ኳስ ቡድን ነገ ከአይቮሪኮስት ጋር የሚጫወት መሆኑንን አብረን ለማስታወስ እንወአለን። መልካም እድል።


Exit mobile version