Site icon ETHIO12.COM

የተበተነው የትህነግ ሰራዊት ወደ ወደ ተንቤንና አቢ አዲ ዳግም የመሰባሰብ እቅድ እንዳለው ተሰማ፤ የመከላከያ አባላት “ትንኮሳ ሰለቸን” ይላሉ

Ethiopian defense force

የአገር መከላከያ ሰራዊት በውሰደው ጠንካራ የህግ ማስከበር እርምጃ ከተደመሰሰው ውጭ ተበትኖ ወደ ጫካ የሸሸው የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ሰራዊት ሕዝብ ውስጥ ገብቶ ራሱን መልሶ እያደራጃና ቀን ሰላማዊ፣ ሲመሽ ታዋጊ በመሆን የትንኮሳ፣ ሲለውም የማጥቃት ሙከራ እንደሚያደርግ በስፍራው ካሉ የሰራዊቱ አባላት መካከል ለኢትዮ12 አመለከቱ።

በኢትዮ 12 “አማራ እና ኦሮሞን በካራ ሌላውን ብሄር በጥይት” በሚል ርዕስ የተጻፈውን መረጃ ካነበቡ በሁዋላ በቀጥታ ያነጋገሩን እንዳሉት የትህነግ ጭፍራ ሳይሆን እነሱን የመሸጉ ክፍሎች ናቸው ኦፕሬሽኑን ያራዘሙት። የመከላከያ ሰራዊት በወሰደው ማጥቃት ተበትነው ወደ ኮረምና ራያ ሸሽተው የነበሩት የትህነግ ሸማቂዎች አመቺ ጊዜ እየጠበቁ ከፍተኛ ጥቃት ለማድረስ ቢሞክሩም ስላልተሳካላቸው አሁን አዲስ ስልት ጀመረዋል።

ስለ ትህነግ የወቅቱ እንቅስቃሴ የሚያውቁ እንደሚሉት በኮረምና ራያ በኩል የመከላከያ ሰራዊት ከሰራው ከበባ ለማምለጥ የሞከረ የትህነግ ሃይል ክፉኛ በሺህ የሚቆጠሩ ሙት፣ ቁስለኛና ምርኮኛ ከሆኑ በሁዋላ ተንቤንና አቢ አዲ በረሃውን ሃይላቸውን የማጠናከር እቅድ እንደያዙ ተሰምቷል።

ታማኝ የመረጃ ምንጮች እንደሚሉት የመከላከያ የበላይ አዛዦች በዚሁ ጉዳይ የኦፕሬሽን ማስተካከያና አዲስ የአሰላለፍ አቅጣጫ ለማበጀት የሚያስችል እቅድ ለመንደፍ እየመከሩ ነው።

የሰራዊቱ አባላት እንደሚሉት “ሲቪል ሆነው ይዋጉናል፤ እርምጃ ሲወሰድ የሰብአዊ መብት ተጣሰ ብለው ይከሳሉ” ካሉ በሁዋላ ” መንግስት የሚረዳውን ስንዴ እያስፈጩና እየጋገሩ ሽፍቶቹን ይቀልባሉ” ሲሉ በተወሰኑት የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ ቅሬታቸውን ያሰማሉ። ” ለትግራይ ሕዝብ ደሙን ያፈሰሰ፣ እድሜውን የቀበሮ ጉድጓድ ውስጥ የፈጀ ሰራዊት እንዴት እንደታረደ፣ እንደተጨፈጨፈና ክህደት እንደተፈጸመበት ስናስብ ዛሬም ድረስ ያመናል” ሲሉ የበደል ስሜቱ እንዳልሻረላቸው አመልክተዋል።

” ይህ ሁሉ ሳያሽር” ይላሉ የሰራዊቱ አባላት ” ይህ ሁሉ ግፍ ሳያንስ ከሽፍታው ቡድን ጋር በድብቅ በማበር መከላከያን እያስቆጡ መሆኑንን፣ ይህ ደግሞ የበርካቶችን የትዕግስት ልክ እየተፈታተነ ነው” ብለዋል። 

” በተኛንበት እንድንታረደ ያዘዙ ሲማረኩ እግር እያጠበን፣ እግራቸውን እያሸን የተንከባከብነው ከሙያ ስነምግባርና ከኢትዮጵያዊ ጨዋነት መነሻ እንጂ እነሱ ደግ ስለሆኑ አልነበረም” ሲሉ አሁን በአንዳንድ ቦታዎች የሚስተዋለው ሁኔታ ሊታገሱት ከማይችሉበት ደረጃ መድረሱን አመላክተዋል። የእርዳታ ስራ ላይ የተሰማሩ አካላት በታጣቂ ማዟዟር ተግባር ላይ እጃቸው አለ ብለው እንደሚያምኑም ጠቁመዋል። አያይዘውም አንድ ውሳኔ ላይ ሊደረስ እንደሚገባ ጠቁመዋል። አገር ወዳድ ዜጎች ሌሎች ለጥፋት ከሚረባረቡት በላይ የመከላከያ ሰራዊትን ሊቀላቀሉ እንደሚገባና ይህንን ጥያቄ ለመንግስት ሊያቀርቡ እንደሚገባም አሳስበዋል።

በዚህ ጉዳይ የተሰባሰቡ መረጃዎችና ምን መደረግ አለበት የሚለውን ሙሉ የመፍትሄ ሃሳብ በተከታታይ እናቀርባለን።


Exit mobile version