Site icon ETHIO12.COM

አማራ ክልል በሚገደሉ ንጹሃን ጉዳይ መንግስት አስቸኳይ መፍትሄና እንዲሰጥ አሳሰበ፤

የተፈለገው ሁለቱን ክልሎችና የአንድ ፓርቲ አመራሮች የማተራመሱ እቅድ እየስመረ ይመስላል። ጥቃት እንደደረሰ በቅጽበት ውስጥ ዘገናኝ የቪዲዮ መረጃ የሚላክላቸው ተባባሪዎች “ኦሮሞ አማራን ገደለ” እያሉ የሚያሰራጩት የትርምስ እቅድ እየሰመረ ይመስላል። አማራ ክልል አሰቸኳይ መፍትሄና ውይይት ጠይቋል።

እንደሚከተለው ቀረቧል።የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አገኘሁ ተሻገር በሰጡት መግለጫ በአማራ ላይ የሚፈጸመው ግድያ እንዲቆም የክልሉ መንግሥት በጉዳዩ ላይ አስቸኳይ ውይይት እንደሚፈልግም አስታውቀዋል።ርእስ መሥተዳድሩ ባለፉት ዓመታት በአማራ ሕዝብ ላይ በተሠራው የጥላቻ ትርክት አማራ በሚኖርበት አካባቢ መገደል፣ መሳደድና መፈናቀል እየደረሰበት ነው፤ ይህ ጉዳይ እንዲቆም ከፌደራል እና ከክልል መንግሥታት ጋር በጋራ እየሠራን ነው ብለዋል። የፌዴራል የጸጥታ ኃይሎች መስዋዕትነት እየከፈሉ እርምጃ እየወሰዱ እንደሚገኙም ገልጸዋል።

በተለይም ኦነግ ሸኔ የተባለው ቡድን አማራን ነጥሎ በማጥቃት የሚታወቅ ነው ያሉት አቶ አገኘሁ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ነፃ አውጭ ነኝ የሚል ቡድንም በአማራ ላይ ያነጣጠረ ጥቃት እያደረሰ ነው ብለዋል።በአማራ ሕዝብ ላይ እየደረሰ ያለው ችግር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሆኑንም ተናግረዋል። ከሰሞኑ በደረሰው ግድያም የክልሉ መንግሥት አዝኗል ነው ያሉት። ይህ ጉዳይ ካልተሻሻለ የሀገሪቱን ዜጎች ተቻችለው ለመኖር ለችግር የሚያዳርግ በመሆኑ የክልሉ መንግሥት አሳስቦታል ነው ያሉት።

የፌዴራል መንግሥት የጀመረውን የጸጥታ ማስከበር ሥራ አጠናክሮ መቀጠል አለበት፤ ገዳዮቻችን የሚታወቁ ናቸው፤ በእነዚህ ላይ እርምጃ መወሰድ አለበት ብለዋል።የቤኒሻንጉል ክልል፣ የኦሮሚያ እና የፌዴራል መንግሥት በገዳዮች ላይ እርምጃ እንዲወስዱ አሳስበዋል። ክልሎች ሕግን ለማስከበር በሚያደርጉት እንቅስቃሴ አብረን ለመሥራት ዝግጁ ነንም ብለዋል።በሀገረ መንግሥት ግንባታ የፖለቲካ ልዩነት ሊኖር ይችላል ህፃናትና እናቶች ግን መሞት የለባቸውም ነው ያሉት።

የሀዘን መግለጫ ማውጣት ሰልችቶናል፣ በጉዳዩ ላይ እልባት እንዲሰጥ እንፈልጋለን፤ እንደ አማራ ክልል መንግሥት አስቸኳይ ምክክርም ንግግርም እንፈልጋለን ብለዋል። ይህ ጉዳይ እንዲቆምም አሳስበዋል።በአማራነታቸው ብቻ ለሚገደሉ ዜጎች የኢትዮጵያ ሕዝብ ከጎን እንዲቆምም ጠይቀዋል። ስሜታችንን መላው የሀገራችን ሕዝብ ሊረዳን ይገባልም ብለዋል። ይህን ወቅታዊ ሁኔታ ተጠቅመው የሀገራችን አንድነት ለመበታተን የሚጥሩ ኃይሎች ያስቡታል እንጂ አይሳካላቸውም፤ ይህ ጊዜ ያልፋልም ብለዋል።የክልሉ ሕዝብም የገጠመንን ፈተና እንደምናልፈው አውቆ በአንድነት መቀጠል መቻል ይገባልም ብለዋል። የፖለቲካ ፓርቲዎችና የማኅበረሰብ አንቂዎች በጋራ መቆም አለብን ነው ያሉት።

በጉዳዩ ትርፍ ለማግኘት የሚፈልጉ አካላት መኖራቸውንም አንስተዋል። የፌዴራል መንግሥት አስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጠን እንጠይቃለንም ነው ያሉት።ኦነግ ሸኔ ከኦሮሚያ ክልል አልፎ በክልላችን ገብቷል ያሉት ርእሰ መሥተዳድሩ አንዳንዶች ኦነግ ሸኔ ስለመኖሩና ስላለመኖሩ ሊነግሩን ይፈልጋሉ፤ ምን አይነት መግለጫ ማውጣት እንዳለብን ሊነግሩን የሚፈልጉ አሉ ይህ ተገቢ አይደለም ነው ያሉት።ያቀድናቸውን ለማሳካት ከፈለግን ግድያ መቆም አለበት። ችግሩን በአጭር ጊዜ ውስጥ እንፈታዋለን፤ መላው ሕዝብ ከጎናችን ይሁን ነው ያሉት።

ርእሰ መሥተዳድሩ በሰጡት መግለጫ አማራ በሀገረ መንግሥት ያለውን ድርሻ አጠናክሮ ይቀጥላል፤ አማራ የኢትዮጵያ አንድነት ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚፈልግና በኢትዮጵያዊነት የማይደራደር ሕዝብ ነውም ብለዋል።”ኢትዮጵያዊ አንድነታችን እንዳይፈርስ እንሠራለን፣ ደግሞም እናሸንፋለን” ነው ያሉት። ገዳዮቻችን የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ለሕግ እናቀርባቸዋልንም ብለዋል።የአማራ ሕዝብ ቂመኛ አይደለም ያሉት ርእሰ መሥተዳድሩ ወንድማማችነትን ያስቀድማል፤ እኛን በመግደል ስለ ኢትዮጵያ ያለንን አመለካከት ይቀይራል ብሎ የሚያስብ ካለም አይሳካለትም ነው ያሉት።

አማራ ሚዲያ ኮሙኒኬሽንዘጋቢ:- ታርቆ ክንዴ.


Exit mobile version