Site icon ETHIO12.COM

ትህነግ በዲፕሎማሲ ዘመቻ ቀውስ ገጠመው፤ “ በሃሰት መረጃ አሳፈራችሁን ” የቅርብ አጋሮቻቸው

በጦርነት የተመታውና ህልውና ሙሉ በሙሉ እንዳከተመለት የተነገረለት ትህነግ በዲፕሎማሲ አስደንጋጭ ቀውስ እንደገጠምው ተሰማ። ሌት ከቀን ሲሟገቱላቸው የነበሩ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች “ አዋረዳችሁን” ሲሉ ሃዘናቸውን እንደገለጹላቸው ታወቀ። አካሄዱን “ ትህነግ በዲፖሎማሲም ሞተ ማለት ነው” ተብሏል።

ውጭ አገር ሆኖ ትግሉን እየመራ እንደሆነ የሚናገረው የትህነግ የቀደመው መዋቅር በቀጥታ ተጠርቶ “አፍረናል፣ አዝነናል፣ ከፍተኛ ባለስልጣናትን አሳስተናል። እነሱም አዝነውብናል” በሚል ክፉኛ መወቀሳቸውን ለኢትዮ12 የገለጸው የቅርብ ሰው ነው።

አቶ ጌታቸው አሰፋ በጠና ታመው ጣር ላይ መሆናቸውን ከነዚሁ አካላት መረጃ በመውሰድ ለዝግጅት ክፍላችን አስቀድሞ የገለጸው የመረጃ አጋራችን እንዳለው ወቀሳው የቀረበው ለእነ አምባሳደር ብርሃነ ገ/ክርስቶስ ነው።



ድርድር፣ ተኩስ ማቆም፣ ሁሉ አቀፍ ውይይትና ከዛም ያለፈ ጥያቄ እንዲያቀርቡ ትግራይ ሙሉ በሙሉ ጦርነት ላይ እንደሆነች፣ የትህነግ ሃይል አብዛኛውን የትግራይ ክልል እንደሚቆጣጠር ተደርጎ ሲቀርብላቸው የነበረው መረጃ ስህተት መሆኑ ከታወቀ በሁዋላ ነው አጋሮቻቸው በዚህ ደረጃ ቅሬታቸውን የገለጹት።

በስምንት አቅጣጫ በድሮን፣ ሄሊኮፕተር፣ ሮኬትና ረዥም ተጓዥ መድፍ የታገዘ ጥቃት ተሰንዝሮበት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ትህነግ የተበጣጠሰ ሽፍታ እንጂ ጦር አሰልፎ ሊዋጋ የሚችል ሃይል እንዳልሆነ ሌ/ጄነራል ባጫ ደበሌ ከትናንት በስቲያ መናገራቸው ይታወሳል።

እሳቸው በዝርዝር አይግለጹት እንጂ በስምንት አቅጣጫ የተከፈተው የማጽዳት ዘመቻ መጀመሩን ተከትሎ በርካታ ከፍተኛ የጦር መኮንኖችና አገር መከላከያን የከዱ መማረካቸው፣ በሺህ የሚቆጠሩ ተዋጊዎች መማረካቸውና ከተደመሰሱት መካከል ማንነታቸው እንዳይታወቅ ከአስራ አምስት በላይ አንገታቸው መቆረጡን ታማኝ የመከላከያ ምንጮች መናገራቸው ይታወሳል።

ወደ ኢትዮጵያ የመጡት የአሜሪካ ፕሪዜዳንትና መልዕከተኛና የአውሮፓ ፓርላማ ተወካዮች በሚዲያዎች ከሰሙት በላይ በቦታው ተገኝተው ተፈጸመ የተባለውን ግፍ ያጋልታሉ ተብሎ ሲጠበቅ በተቃራኒው መሆኑ ወይም እጅግ የተላዘበ መሆኑ የትህነግ የዲፖሎማሲ ዘመቻ መወርዛቱን አመላካች እንደሆነ ቀድሞም አስተያየት ሲሰጥ ነበር።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይም የውጭ ሚዲያዎችና ታዛቢዎች ባሉበት ባደረጉት የፓርላማ ንግግር “ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻውም ይበናል” ሲሉ እውነት እንደሚገለጥ መናገራቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሚዲያ ፍጆታ እንዳይውል ዝምታን መርጠው የፕሬዚዳንት ባይደንን መልዕክተና ሴናተር ኩፎንን ለአምስት ሰዓት ማናገራቸው ከመሰማቱ በፊት ለሕዝብም ሆነ ለማንኛውም ሚዲያ ይፋ ያልሆነ የቪዲዮ መረጃ እንደሚመለከቱ ዝግጅት ክፍላችን ምንጮቹን ጠቅሶ ነበር።

ይህ ሁሉ ከሆነ በሁዋላና መልዕተኛው አሜሪካ ደርሰው ምስክርነታቸውን ከሰጡ፣ በአደራ የተሰጣቸውን መልዕክት ካደረሱ በሁዋላ “በተጨባጭ ያለው እውነትና የሚነገረን አንድ ባለመሆኑ አዝነናል። ተሳስተን አሳስተናል” ሲሉ አንድ ሴናተር መናገራቸውን ጠቅሰው አምባሳደር ብርሃነ ገብረክርስቶስ “ ክፉኛ ተውቅሰናል። የገነባነው መስመር ችግር ገጥሞታል።ካሁን በሁዋላ ያልተጣራ መረጃ አታምጡልኝ። ከፈለጋችሁ እሱን ለሚዲያ ብቻ ተጠቀሙ” ሲል የመረጃው ባለቤት መስማቱን አስታውቋል። ይህ የብርሃነ ገብረክርስቶስ ንግግር ሌሎችን እንዳበሳጨ አመልክቷል።



ከበረሃ በድርጅቱ አመራሮች ስም የሚወጣው መረጃና ምስልም “ አለን” ለማለትና ሕዝቡ እነሱን እያሰበ ተረጋግቶ እንዳይኖር ለማድረግ እንደሆነ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር አመራሮች በተደጋጋሚ ይገልጻሉ። መንግስትም በተመሳሳይ “ ትህነግ እንደ ዱቄት አየር ላይ ተበትኗል” ሲል በገሃድ አስታውቋል። የመከላከያ ሚኒስቴር የህ/ግንኙነት ክፍልም “ ስንዴ ዘረፋ ላይ የተሰማራ ሌባ” ሲል አበሻቅጦ ጠርቶታል። “ በዋለበት የማያድር፣ ባመሸበት የማይቆይ ተሹለከላኪ ደም የማይጠግብ …“ በሚል ዳግም ህልውና ሊኖረው የማይችል እንደሆነ አረጋግጠዋል።

በአሁኑ ሰዓት ትጥቅና ስንቅ አጥሮት ተከዜ ተበጣጥሶ “ ይዳክራል” የተባለው ሃይል በጦርነት ብቻ ሳይሆን በዲፕሎማሲው ዙሪያ ፈጥሮት የነበረው ጫና መደብዘዙ በውጭ አገር ያሉትን የመዋቅሩን መሪዎች አስደንግጧል። በዚሁም ሳቢያ ጣት መቀሳሰር ጀምረዋል። “መለስ ያባረራቸውን ጦረኞች ደብረጽዮን ሰብስቦ ጉድ አድረገን” በሚሉትና “ የድርጅቱ ሃብት ስራ ላይ ይዋል” በሚሉት መካከል መካረር መጀመሩን ምንጫችን ጠቁመዋል። ሙሉውን መረጃ እናስከትላለን።


Exit mobile version