Site icon ETHIO12.COM

በምርጫው ካሸነፍኩ የአርሶና አርብቶ አደሩን ኑሮ የሚያሻሽሉ አሰራሮች እተገብራለሁ – አብን

የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ካሸነፈ የአርሶና አርብቶ አደሩን ኑሮ የሚያሻሽል የገጠር ሽግግር እንደሚተገብር አስታወቀ።

ፓርቲው የ2013 የምርጫ ማኒፌስቶ ሰነዱን ዛሬ አስተዋውቋል።

ማኒፌስቶው የኢትዮጵያን ነባራዊ የምጣኔ ሃብት፣ ፖለቲካና ማህበራዊ ጉዳዮች በመዳሰስ ለችግሮች መፍትሄና የወደፊት አቅጣጫዎችን ያካተተ ነው ተብሏል።

የፓርቲው የፖለቲካ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ክርስቲያን ታደለ በጤና፣ በትምህርት፣ በሥራ እድል ፈጠራ፣ በግብርናና ገጠር ልማት እና ሌሎች ዘርፎች ፓርቲው ያቀረባቸውን አማራጭ የፖሊሲ ሃሳቦች ዘርዝረዋል።

በግብርናና ገጠር ልማት የሰብልና እንስሳት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ሰጥቶ ለመስራት አማራጭ ፖሊሲዎችን ማቅረቡን አስረድተዋል።

ፓርቲው የአርሶና አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ የኑሮ ሁኔታ የሚያሻሽል የገጠር ሽግግርን እንደሚተገብር ገልጸዋል።

እንደ ኃላፊው ገለጻ፤ ፓርቲው በምርጫው ካሸነፈ ኤሌክትሪክ፣ ውሃ፣ ትምህርትና ሌሎች መሰረታዊ የልማት አገልግሎቶች የተሟሉባቸው የገጠር ከተማ ማዕከላትን ለመፍጠር ይሰራል።

ለገጠሩ ማህበረሰብ ኑሮ አመቺ የሆኑ ተገጣጣሚ ቤቶች እንዲሰሩ አማራጮችን ለማቅረብና ኑሮውን የሚያዘምኑ ተግባራትን ለማከናወን አማራጭ ሃሳብ አቅርቧል።

አብን የአርሶና አርብቶ አደሩ የኑሮ ሁኔታ እንዲሻሻል የሚያደርጉና በአገሩ ፖለቲካ ቁልፍ ተዋናይ የሚያደርጉ አሰራሮችን እንደሚተገብር ኃላፊው ገልጸዋል።

የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ በለጠ ሞላ በበኩላቸው “አብን ለስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ለህዝቡ ያቀረባቸውን አማራጭ የፖሊሊ ሃሳቦች አዘጋጅቶ ጨርሷል” ብለዋል።

መራጩ ሕዝብ ፓርቲው ያቀረበውን አማራጭ ሃሳብ በመረዳት ድምጹን እንዲሰጥም ጠይቀዋል።

የማኒፌስቶው የአርትኦት ስራ ተጠናቆ በመጪው ሰኞ ለሕዝብ ተደራሽ እንደሚሆን ተገልጿል።

በመጪው ግንቦት መጨረሻና ሰኔ መጀመሪያ በሚካሄደው አጠቃላይ ምርጫ የሚሳተፉ የፖለቲካ ፓርቲዎች አማራጭ ሃሳቦቻቸውን የመገናኛ ብዙሃንና ሌሎች አማራጮችን በመጠቀም በማስተዋወቅ ላይ ይገኛሉ።

(ኢዜአ)

Exit mobile version