ETHIO12.COM

መከላከያን መነካካት አይስኬድም! ራሳቸውን ለገበያ ያዋሉ በበዙበት ውቅት መከላከያን መንካት ሃፍረት ነው!

“አንድ ግዳጅ ስንወጣ ቀምለን ነው የምንመለሰው። መታተብ የለም። እንደፈለግን ልብስ አንቀይርም። ከበርሃው ጋር መመሳሰል ግድ ነው። ካልሲ ጫማ ውስጥ ተጣብቆ፣ ሰውነት ዝሎ.. የትህነግ ሰዎችን ማደን ከባድ ስራ አይደለም። ከባዱ ነገር የሚሸሽጓቸውና የሚደብቋቸው አሉ። በዚህ አስቸጋሪ ፈተና ውስጥ እያለፍን ነው የሚሰማውን ድል ሁሉ የምንጎናጸፈው። ሃላፊነታችን ትልቅ ነው። አገራችንን ስለምንወድና ሕዝብ የሚሰጠን ክብር ስናይ ደስታችን ልዩ ነው። ሁሌም ድል ማብሰር ነው ሃሳባችን። “

ዝግጅት ክፍላችን ከወራት በፊት በራያ በኩል የተደመሰሰው የትህነግ ጭፍራ ወደ አማራ ክልል ሊገባ ሲተም በአማራ ክልል ሃይል መመታቱን እማኝ ጠቅሰን መዘገባችን ያታወሳል። ከዛም ቀድሞ ” ለእኛ የማትሆን ኢትዮጵያን እናፈርሳታለን። እናፈራርሳችኋለን” በሚል በፓልቶክ ሲተላለፍ የነበረ መልዕክት ማስነበባችን ይታወሳል። እሱ ብቻ ሳይሆን ትህነግ በተግባር ኢትዮጵያን መምራት ሲያቆም እንደሚያፈርሳት በተደጋጋሞ መነገሩ ይታወሳል። እንሱም አይክዱም።

“አጣዬ ላይ የጎረቤቴና የአጎቴ አስክሬን ዛሬ ሁለተኛ ቀኑ አልተነሳም፣እሽ ምን ልበልህ ፣እኔ ለስራ ሸዋሮቢት የድርጊቱ ቀን ጧት ወጥቼ በዛው ቀረሁ፣ቤተሰቤ ቀባሪ አጥቷል፣አሁን ሰው ስለመሆኔ እጠራጠራለሁ በድን ሁኛለሁ ተወኝማ” ሲል ለባልደረባው ግራ ግብቶት መልዕክት ያስተላለፈው የአጣዬ ነዋሪ ነው። ያስዝናል። ያማል። መተነፈስ እስኪሳነን ድረስ ይጨንቃል።

በተቃራኒው እዛው እሳት ውስጥ፣ የትውልድ ቀያቸው ገሃነብ የሆነባቸው የሚያሰሙትን የጣር ድምጽ በቪዲዮ እየቀረጹ የሚያቅራሩ ሲታይ “ሰው” ለሆኑ ሁሉ ሃዘኔታቸውን ወደ ቁጣ ይለውጥባቸዋል። ህመሙና ስብራቱ ሊገለጽ ወደማይችል አውሬነትም ሊቀይራቸው ይችላል።



“ አይኔ የጠፋው ዛሬ ነው” ያሉ እናት ከወለጋ በአልጋ ሸክም ነው የተሰደዱት። እኚህ አዛውንት እድሜያቸውን በገፉበት ወለጋ በተፈጥሮ አይናቸው ደክሞ ማየት አቁሟል። እኚህ እናት ሲፈናቀሉ አይናቸው ስለማያይ ልጆቻቸው በወሳንሳ ተሸክመው ነው ያወጧቸው። አሁን አማራ ክልል ገብተዋል። “ አይኔ የጠፋው ዛሬ ነው” ሲሉ መስማት በክፋት ስሜትም ይሞላል። ሊገነፍልም ይችላል።

በዚህ ደረጃ ክፋት የተሞላበት ተግባርን በሚስኪን ህዝብ ላይ መፈጸም ለምን አስፈለገ? አጣዬን ያነደዱ፣ ህዝብ የጨፈጨፉ ጥያቄያቸው ምንድን ነው? ምን እንዲሆንላቸው ነው የድሃ ጎጆ በለሊት መጥተው የሚያጋዩት? ሕጻናትን የሚገድሉት ምን ፈልገው ነው? አሮጊቶች፣ ሕጻናትና አዛውንት ምን በደሉዋቸው? አዛውንቶችን በጥይት መደብደብ ምን ይጠቅማቸዋል? ሁሉም ይሁን ስለምን ሃላፊነትን ወስደው በግልጽ ምን ማድረግ እንደሚፈልጉ አይናገሩም?

ዓለም ላይ ያሉ ነውጠኛ፣ አሸባሪና አክራሪ ሃይሎች ፍላጎታቸውን በሃይል ለመጫን ከአንድ ወንጀል ፍጻሜ በሁዋላ በግልጽ ሃላፊነት ወስደው ይናገራሉ። በአደባባይ “ጨፈጨፍኩ” በለው ያውጃሉ። የኛ አገሮቹ ይጨፈጭፋሉ። ሲጨፈጭፉና ሲያርዱ በባለሙያዎች ቪዲዮ ቀርጸው ይበትናሉ። የተጨፈጨፉት ባደባባይ ማን እንደጨፈጨፋቸው እየተናገሩ ቪኦኤ ላይ ወጥተው ያስተባብላሉ። ማንን እንመን? ስሙ ሲጎድፍ የሚቀይረውን አራጅ ወይስ የታራጅ ቤተሰቦችን?

በሌላ በኩል ደግሞ በዚህ ሁሉ ስቃይና የደም ጎርፍ ውስጥ እንደ ትል የሚዋኙ የሲኦል መልዕክተኞች ይወራጫሉ። በአጣዬ ጭፍጨፋ የመከላከያ ኦራል ላይ የኦነግ ባንዲራ ያነገቡ ሃይሎች ናቸው ወንጀሉን የሚፈጽሙት በሚል አንዱና አገራችንን በደሙ እየጠበቀ ያለውን መከላከያችንን ዘመቻ ይከፍቱበታል።

የመከላከያ ኦራል የኢትዮያን ባንዲራ እያውለበለበ የትህነግን የሽብር ሃይል ሲቀጠቅጥ የተንሳውን ምስል በፎቶ ሾፕ መቀየርና የኦነግ ባንዲራ እንዲደረግበት ለምን አስፍለገ? እንዲህ ያለ ምስል እልቂቱ እየተካሄደ በማህበራዊ ሚዲያ ማሰራጨት ምን ይነግረናል? ነገሩ አንድ ዓይን ያለው በአፈር አይጫወትም ነውና እናስብ። የአጣዬ ተጎጂዎች የትህነግ ሃይል በጥፋት ዘመቻው ላይ እንዳሉበት ነግረውናል።


“በመከላከያ ሠራዊት ወታደራዊ ተሽከርካሪ ላይ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አርማዎች ተሰቅለው የሚታይበት ፎቶ ትክክለኛ ነው? የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ንብረት የሆነ ኡራል ወታደራዊ ተሽከርካሪ ላይ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አርማዎች ተሰቅለው የሚታይበት ፎቶ ዛሬ በማህበራዊ ትስስር ገጾች በስፋት ሲዘዋወር ኢትዮጵያ ቼክ ተመልክቷል።”

This image has an empty alt attribute; its file name is defenc-fake.jpeg
ተጭበርብሮ የተሰራው ምስል

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ንብረት የሆነ ኡራል ወታደራዊ ተሽከርካሪ ላይ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አርማዎች ተሰቅለው የሚታይበት ፎቶ ዛሬ በማህበራዊ ትስስር ገጾች በስፋት ሲዘዋወር ኢትዮጵያ ቼክ ተመልክቷል።

ይህ ፎቶ በተደጋጋሚ ከተጋራባቸው የማህበራዊ ትስስር ገጾች አንዱ ‘Abebe Belew Group’ የተባለና ከ75 ሺህ በላይ አባላት ያሉት የፌስቡክ ቡድን ይገኝበታል።

በዚህ ቡድን ፎቶውን ካጋሩት መካከል አንዱ የሆነው ዋርካው ጎንደር “ሸዋ ላይ የታወጀው ጦርነት በመንግስት የሚደገፍ ስለመሆኑ ከዚህ በላይ ማረጋገጫ የለም!….በመከላከያ መኪና (ኦራል) ላይ ባንዴራውን እያውለበለበ ያለው ኦነግ ሸኔ (“የኦሮሚያ ልዩ ሀይል”) ነው። ይህ በኦሮምያ ክልል መንግስት፣ በኦነግ ሸኔና በመከላከያ መካከል ልዩነት እንደሌለ ያሳየናል” የሚል ጽሁፍ አስፍሯል።

ኢትዮጵያ ቼክ የፎቶ ፎረንሲክ መገልገያ መሳሪዎችን በመጠቀም ባደረገው ማጣራት ፎቶው የተጨቆነ (photoshopped) መሆኑን አረጋግጧል። በተጨማሪም ኢትዮጵያ ቼክ የሪቨርስ ኢሜጅ መፈለጊያ መተግበሪያዎችን በመጠቀም ባደረገው ማጣራት በትክክለኛው ወይንም ባልተጨቆነው ፎቶ የኢፌድሪ ሠንደቅ አላማ የሚታይ መሆኑን አረጋግጧል።


ልብ እንበል በቅርቡ በራያ በኩል የተመታው የትህነግ ጭፍራ ወደ አማራ ክልል ሰርጎ ሊገባ ሲል መመታቱን ተዘግቧል። ይህ ጭፍራ ሙሉ በሙሉ ይደምሰስ አይደምሰስ አልታወቀም። ዛሬ ለቢቢሲ የተናገሩት ወገኖች የትህነግ ጭፍሮችም እንዳሉ ሲናገሩ “ ሌሎች የትህነግ ሰራዊትና ኦነግ ሸኔ ጨፈጨፉን” ነው ያሉት።

በማዕከላዊ ጎንደር ትህነግ ያስለተናቸው ተነስተዋል። ቀን ሰላማዊ፣ ማታ ተዋጊ እየሆኑ አማራ ክልልን እያዝሉት ነው። ይባስ ተብሎ በፍኖተ ሰላም መኪና እስከማቃተል የደረሰ ግብግብ፣ ፖሊስ እስከመገደል የደረሰ ሁከት እየተካሄደ ነው። ከወለጋ ሰዎች ተፈናቀሉ ብሎ መኪና ማቃጠልና መንገድ መዝጋት፣ ፖሊስ መግደል ምን ፋይዳ አለው? ሰላማዊ ሰልፉ የአማራ ክልል ወለጋ ገብቶ ይጨፍጭፍ ለማለት ነው? ያሳፍራል። ያሳዝናል። ደግሞም ድንቁርና ነው።

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በክልሉ የሚኖሩ ነዋሪዎችን ሰላም ማስተበቅ አለመቻሉ ከአሳፋሪ በላይ ውድቀትም ነው። ማፈር የሚችሉ ከሆነና የሚያፍር ህሊና ካላቸው ማለት ነው። ከዚህ ባልተናነሰ የሚያሳዝነው ግን ይህን ህዝብ ለመምራት ብቁ መሆናቸውን የሚናገሩት ተፎካካሪዎች ናቸው።

እነዚህ ሃይላት መንግስት ለመሆን ካላቸው ስግብግብነት የተነሳ ወደ ጎን ከነማን ጋር አብረው ይሰሩ እንደነበር፣ እስካከናወኑት የስልጣን ክፍፍል መናገር ይቻላል። “ጠባብ” ከሚሉት ወገን ጋር ገጥመው መንግስት ለመናድ ሲዶሉቱ ነበር። ከዛ በፊትም ክልሉ ብቁ መሪዎች ወጡለት ሲባል እንዲቀጠፉ የነበራቸው ሚና ከሕዝብ የሚሰወር አይደለም። ዛሬም በዚሁ ቀውስ ውስጥ እንደ እሳት እራት እሳቱን እየተሽከረከሩ ነው። ወደ ላይ ደግሞ ልባቸውና ቀልባቸው ከተምቾቹ የኢየሱስ ከሃዲያን ጋር ስለመሆኑ መረጃ አለ።

እንደ ኦሮሚያ ክልል ሁሉ አማራ ክልል እንዴት የሕዝቡን ሰላም ማስተበቅ ያቅተዋል? ችግሩ የቆየ፣ ተደጋግሞ የተሞከረ፣ ከዛም በላይ የሚታወቅ ዓላማና መሪ ያለው እንደሆነ በቂ ግንዛቤ እያለ ለምን ተኛ? ዛሬ እንደሚሰማው ሸዋ ሮቢትም ስጋት አለ። በርካታ የአካባቢው ወረዳዎችና ከተሞች ተጠበዋል? የሰሜን ሸዋ ጀግና ራሱን መከላከል እንዴት አቃተው? ይህ ጥያቄ መመለስ አለበት።

ልክስክሶች ጥቅማቸው ለጎደለ እያሸረገዱ እስከመቼ? ክልሉ ከተራ ቀረርቶ በመውጣት ከላይ ከመሪው ጀምሮ በአግባቡ ራሱን ሊመመረምር ሊያርቅ ይገባል። ነገ ዛሬ ሳይል ሰላም ማስከበሩን እያከናወነ ማስተካከያ መውሰድ አለበት። ከዚም በላይ ክልሉን እየመሩ “አዲስ እንመጣለን” ከሚሉት ጋር የገጠሙትን መንቀል፣ እነዚህ ተቀናቃኝ ተብለው ወደ ጎንና ወደ ላይ የተላልኪነት ትሥሥር የፈተሩትን ጉዶች ማጋለጥና ለህዝብ አንዷሎ መስጠት ግድ ነው። ዛሬ ጊዜው የህፍረት ሳይሆን እውነት ገሃድ የሚሆንበት ነው።

መንግስት በዚህም ሆነ በሌሎች ጉዳዮች ሊወቀስ ግድ ነው። ግን መከላከያ ስንት ቦታ ይሁን? ሰራዊቱ በየቦታው ተበትኖ በግዳጅ መከራው እያየ ነው፣ ዛሬ መንግስትን የሚወቅሱት “ የኤርትራ ሰራዊት ይውጣ” እያሉ የሚጮሁ ናቸው። እነዚህ ወገኖች የኤርትራ ሰራዊት እንዲወጣ የሚጠይቁት የገር መከላከያ እንዲሳሳና እንዲመታ ብሎም ጌታቸው ህወሃት አፈር ልሶ እንዲነሳ ነው። እነዚህን አለቅላቂዎች የሚከተሉ ጭፍሮች በማህበራዊ ገጽ እንደ በቀቀን የሚያስተጋቡት ይህ ድምጽ የማን ነው? ብሎ መጠየቅ ግድ ነው።

ሌላ ሱዳን ከመሬት ወረራው ባሻገር ለሌላ ኦፕሬሽን ከግብጽ ጋር እያደሙ ነው። መከላከያችን እዛ አለ። የህዳሴ ግድብ የሚተበቀው በመከላከያ ሃይላችን ነው። በምዕራብ ወለጋ ሰራዊታችን ዋጋ እየከፈለ ነው። በምስራቅ ሁሌም ጥንቃቄ ስለሚያሻ ሰራዊታችን እዛም በረሃ ውስጥ ነቅቶ አገሩን ይጠብቃል። በትግራይ ታርዷል። የተረፈው አገግሞ አራጆቹን ቀጥቅጧቸዋል። እየቀጠቀጠ ነው። ግን ቀላል አይድለም። ብዙ መከራ አለው። የቀን ሰላማዊ፣ የማታ ተዋጊ ድራማ። እንዲሁም ሲቪል እየለበሱ የሚዋጉና ሲመቱ “ ሲቪል ተገደለ” በሚል የሚጮሁ። መከላከያችን ቢኒሻንጉል፣ ሁመራ፣ ጎንደር፣ ደቡብ … ይህ ሁሉ መከራ የተሸከመውን ሰራዊት መውቀስ ይቻላል?

የማሟያ ቅጥር ጥሪ ሲደረግ ምን ያህል ሰዎች ምላሽ እንደሰጡ እየታወቀ ዛሬ መከላከያ ላይ ጣት መቀሰር አግባብ ሊሆን አይችልም። አያስኬድም። አሳፋሪም ይሆናል። ይባስ ተብሎ የመከላከያን ስም ለማጉደፍ የሚለጣጠፉ ፎቶዎችን በማባዛት የሚፈረካከሰን ተግባር ላይ መተመዳችን ልብ ይነካል።

ለሚዲያዎች

ለማስብ፣ ለማስተዋል፣ ለማጣራት፣ ለመመርመር ጊዜ እንስጥ። እስኪ የተተፋውን ብቻ ሳይሆን እንደሚዲያ ጥልቅ ምርመራ ላይ አተኩረን እንስራ። ከርዕስ ጀመሮ ጨዋነት የሚጎድለውን አሰራራችንን እንፈትን። የማናውቀውን ጉዳይ ከማብራራትና ከመተንተን እንቆጠብ። በቀጥታ ስርጭት ህዝብ ሃዘን ላይ፣ የአገር ጉዳይ ላይ አንዛበት። እጅግ ጠንቃቃ ወገኖች በታም ትንሽ ቢሆኑም ክብር የሚገባቸው ይሆናል። ከዚያ ውጭ ግን እንደ ህንድ ፊልም የእልቂት ሬክላም በመለጠፍ ሳንቲም መልቀም ትርፉ ሞት ነው። እንደ አገርም እንሞታለን።

ምስክርነት

“አንድ ግዳጅ ስንወጣ ቀምለን ነው የምንመለሰው። መታተብ የለም። እንደፈለግን ልብስ አንቀይርም። ከበርሃው ጋር መመሳሰል ግድ ነው። ካልሲ ጫማ ውስጥ ተጣብቆ፣ ሰውነት ዝሎ.. የትህነግ ሰዎችን ማደን ከባድ ስራ አይደለም። ከባዱ ነገር የሚሸሽጓቸውና የሚደብቋቸው አሉ። በዚህ አስቸጋሪ ፈተና ውስጥ እያለፍን ነው የሚሰማውን ድል ሁሉ የምንጎናጸፈው። ሃላፊነታችን ትልቅ ነው። አገራችንን ስለምንወድና ሕዝብ የሚሰጠን ክብር ስናይ ደስታችን ልዩ ነው። ሁሌም ድል ማብሰር ነው ሃሳባችን። ” ስለዚ መከላከያን መንካትና መነካካት ነወር ነው። ውጤቱም ልክ አይሆንም።


Exit mobile version