ETHIO12.COM

በማህበራዊና በአለምአቀፍ ሚዲያዎች እየተሰራጨ ያለውን ሀሰተኛ መረጃ ለማረም የኢትዮጵያዊያን ግብረሀይል በአውሮፓ ተቋቋመ

በአውሮፓ አንዳንድ የፓርላማ አባላትና መንግስታት እያስተጋቡ ያሉትን የተዛባ መረጃ ለመከላከል፤ በማህበራዊና በአለምአቀፍ ሚዲያዎች እየተሰራጨ ያለውን ሀሰተኛ መረጃ ለማረም የሚያስችል “Defend Ethiopia” የሚል የኢትዮጵያዊያን ግብረሀይል በአውሮፓ ተቋቋመ፡፡

በዩናይትድ ኪንግደም የኢትዮጵያ አምባሳደር በወቅቱ እንደተናገሩት በዩይትድ ኪንግደም ከሰባ በላይ ከፍተኛ ምሁራንን እና ወጣት የማህበራዊ ሚዲያ አንቂዎችን ያሰባሰበው Defend Ethiopia በአውሮፓ ደረጃ ተጠናክሮ እና ተቀናጅቶ ቢቀጥል የፓርላማ አባላትን፣ ቲንክ ታንክ ቡድኖችን እና አለም አቀፍ ሚዲያዎችን የሚያሳድሩትን ተጽእኖ በቀላሉ ለመቀነስ ይቻላል ብለዋል፡፡

በትግራይ ክልል የተወሰደውን ህግ የማስከበር እርምጃ ተከትሎ የተከፈተውን የተዛባ መረጃ የማሰራጨት ተደጋጋሚ ጥረትን ለማረም የፓርላማ አባላትንና መገናኛ ብዙሃን የያዙትን የተሳሳተ አቋም ለማስተካከል መደራጀቱ ከፍተኛ አቅምን ይፈጥራል ብለዋል፡፡

ከግብረሃይሉ አባላት መካከል በምስል

አንዳንድ የአውሮፓ ሀገራት የፓርላማ አባላት እና መገናኛ ብዙሃን በውጪ ካለው የህወሃት ርዝራዥ ጋር በቀጥታ በመናበብ የሚያቀርቡት ውትወታ ህወሃት መልሶ ነፍስ እንዲዘራ የሚያቀርቡት አሳሳች መረጃ ለማንም የሚጠቅም ባለመሆኑ ትክክለኛ አለመሆኑን ለማስረዳት በውጪ ያለው ኢትዮጵያዊ እና ትውልደ ኢትዮጵያዊ ተቀናጅቶ የመስራቱ ሚና ወሳኝ ነው ብለዋል ፡፡

ባለፉት ሶስት አመታት የተካሄደው ሪፎርም በሰላም በሃሳብ በመወዳደር አሸናፊነትን በጸጋ የመቀበል ስርአትን የመገንባት ጥረቱ ተጠናክሮ በቀጠለበት ለማደናቀፍ በተመሳሳይ ተደጋጋሚ ጥረቶች ተደርገዋል ነገር ግን አልተሳኩም፡ኢትዮጵያን ውጤት በሚያመጣ ስራ ነው ማሻገር የሚቻለው ያሉት አምባሳደር ተፈሪ ግብጽና ሱዳን ከግድቡ ጋር በተያያዘ የያዝነውን መርህ የተከተለ አሰራር እጅ በመጠምዘዝ ለማደናቀፍ የሚያደርጉት ሴራ ተጠናክሮ በመቀጠሉ ኢትዮጵያዊያን እና ት/ኢትዮጵያዊያን ይበልጥ ተቀናጅተው ለሀገራቸው ብሄራዊ ጥቅም መቆም አለባቸው ብለዋል፡

ኢትዮጵያዊያኑና እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያኑ በበኩላቸው የዲጂታል ዲፕሎማሲና የሎቢ ዘመቻው ተጠናክሮ እንዲቀጥል የበኩላቸውን ሚና እንደሚጫወቱ ቃል ገብተው የዘመኑ መረጃ ፈጣን እና ጊዜን የማይጠይቅ በመሆኑ ሳያቋርጥ መረጃ ሊያቀብል የሚችል ማእከል እንዲፈጠር መጠየቃቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ፅህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ via (ኢ ፕ ድ)


Exit mobile version