Site icon ETHIO12.COM

በአጣዬና አካባቢው የተፈጸመውን የወንጀል ድርጊት የሚያጣራ የፌዴራልና የክልሉ የምርመራ ቡድን ሥራ ጀመረ

በአጣዬ እና አካባቢው የተፈጸመውን የወንጀል ድርጊት የሚያጣራ የምርመራ ቡድን ወደ ስፍራው መላኩን የአማራ ክልል ጠቅላይ ሕግ አቶ ገረመው ገብረጻዲቅ አስታወቁ። የተላከው ቡድን ከፌዴራል እና ክልል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ እና ፖሊስ የተውጣጡ አባላት የያዘ መሆኑ ተገልጿል።በአጣዬ እና አካባቢው በሰው ሕይወት መጥፋት፣ በአካል መጉደል፣ በንብረት መውደም እና በሰዎች መፈናቀል የደረሰው ጥፋት ተራ ግጭት ሳይሆን ለዘመናት የተገነባ ከተማን ያወደመ አስከፊ የወንጀል ድርጊት መሆኑንም አቶ ገረመው አመልክተዋል።

የወንጀል ድርጊቱን በልዩ ትኩረት ለማጣራት የፌዴራል እና የክልሉ ተቋማት የጋራ የምርመራ ቡድን በማቋቋም፣ ዕቅድ በማውጣት እና አቅጣጫ በማስቀመጥ ወደ ሥራ መገባቱን ተናግረዋል።በደረሰው ሰብአዊ እና ቁሳዊ ሀብት ውድመት ተሳታፊ የሆኑ አካላትን በቁጥጥር ስር በማዋል ለሕግ የማቅረብ ሥራ እንደሚከናወን ያመለከቱት ዐቃቤ ሕጉ፤ የምርመራ ቡድኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሥራውን ከማጠናቀቅ ባሻገር በማጣራት ሂደቱ የሚገኘውን ውጤት በተከታታይ ለሕዝቡ የሚገልጽ መሆኑን ጠቁመዋል።

የታክቲክ እና የቴክኒክ ስልቶችን ተጠቅሞ በሚከናወነው ምርመራ የአካባቢው ማኅበረሰብ ትክክለኛ መረጃ በመስጠት፣ ማስረጃ በማቅረብ እና ምሥክር በመሆን እንዲተባበር ጠይቀዋል።በተመሳሳይም በማዕከላዊ ጎንደር ጭልጋ አካባቢ ከቅማንት ማንነት ጋር በተያያዘ በተደጋጋሚ የሚፈጸመውን የወንጀል ድርጊት የሚያጣራ መርማሪ ቡድን ወደ ስፍራው መላኩንም አቶ ገረመው ገብረጻዲቅ ተናግረዋል።

በክልሉ በየትኛውም አካባቢ የሚፈጸሙ የወንጀል ድርጊቶችን ማስቆም የሚቻለው በየደረጃው የሕግ የበላይነትን ማረጋገጥ ሲቻል መሆኑን ኅብረተሰቡ በመገንዘብ ተባባሪ እንዲሆን ጠይቀዋል።የክልሉ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ የሕግ የበላይነትን በማረጋገጥ የሕዝቦችን ደህንነት ለመጠበቅ የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት በቁርጠኝነት እንደሚሠራ ማረጋገጣቸውን ኢዜአ ዘግቧል።


Exit mobile version