Site icon ETHIO12.COM

አብንና ባልደራስ ከተሸነፉ ” ውጤቱን አንቀበልም” ሊሉ የሚችሉ ፓርቲዎች እንደሚሆኑ ዲፕሎማቶች ገለጹ

በኢትዮጵያ ለስድሰተኛ ጊዜ የሚካሄደውን ምርጫ አስመልክቶ ባሰባሰቡት መረጃ ከተሸነፉ የምርጫውን ውጤት የማይቀበሉ የፖለቲካ ድርጅቶች መለየታቸውን ዲፕሎማቶች በውስጥ ውይይት ማስታወቃቸው ተሰማ። አብንና ባልደራስ ተጠቅሰዋል።

የኢትዮ 12 የአዲስ አበባ ተባባሪ በውይይቱ የተገኙ የውጭ አገር ሚዲያ ባለሙያዎችን ጠቅሶ እንዳለው ይህ ጉዳይ የተነሳው ሶስት የውጭ አገር ተቋማት ባዘጋጁት መረጃ የመቀያየሪያ መድረክ ላይ ነው። በዚሁ መድረክ ተናጋሪዎቹ የተቋማቱ ሃላፊዎች በቅድመ ምርጫ ትንተና የአማራ በሄራዊ ንቅናቄ / አብን/ እንዳ የአዲስ አበባ ባለ አደራ በሚል ስያሜ የሚጠራው ባልደራስ የሚፈልጉትን ውጤት ካላገኙ ውጤቱን አንቀበልም ከሚሉት ውስጥ ቀዳሚዎቹ መሆናቸውን አመልክተዋል።

ተቀማጭነቱ አዲስ አበባ የሆነው የአሜሪካ እርዳታ መስሪያ ቤት US AID፣ አሜሪካን ኤምባሲ፣አሊያንስ ፍራንስ በጣምራ ምርጫ ለመታዘብና ለመዘገብ አዲስ አበባ የገቡ የሚዲያና የታዛቢ ድርጅት መሪዎች በሰጡት የቅድመ ምርጫ መረጃ አሁን ስማቸው በጸጥታ ችግር በሚጠቀስባቸው አካባቢዎች ሰዎች ወደ ምርጫ ጣቢያ እንዳይሄዱ ክልከላ እንደሚኖር፣ ይህም ኦሮሚያ ላይ እንደሚታይ ገልጸዋል።

ወደ ምርጫ የሚሄዱ ነዋሪዎችን ማስፈራራት፣ ማሸማቀቅ የጸጥታ ችግር አለባቸው በሚባሉባቸው ጥቂት አካባቢዎች መኖሩን እንድ ቅድመ መረጃ አጋርተዋል። የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎችም በተወሰነ ደረጃ ራቅ ባሉ አካባቢዎች ሁከት ሊፈጥሩ እንደሚችሉም አብራርተዋል። ይሁን እንጂ ምርጫው ከተጠናቀቀ ሌላ አይነት ውዝግብ እንደማይኖር ምልክት እንዳለ ጠቅሰዋል።

አብንና ባልደራስ አስመልክቶ በድህረ ምርጫ ውጤት አንቀበልም እንደሚሉ ከመናገራቸው በተጨማሪ በብዛት ቪዛ በመጠየቅ፣ ገንዘብ እንዲሰጣቸው በማመልከት አብንን ስሙን አንስተዋል። አብን ገንዘብ ሲጠይቅ የበሰለ ፕሮፖዛል እንደማያቀርብ ከጉዳዩ ጋር ባይገናኝም እንደመረጃ ለሚዲያና ታዛቢ ቡድን መሪዎች ” እወቁት” በሚል ነው የተነገራቸው።

ባልደራስ በአዲስ አበባ መጠነኛ አቅም እንዳለው ጠቁመው በድህረ ምርጫ ” ውጤቱን አንቀበልም” ቢሉም ከመንግስት ቁጥጥር ውጭ የሚወጣ ረብሻ የማስነሳት አቅም ግን እንደሌላቸው ገልጸዋል። አብን በአማራ ክልል አሁን ሁከትና ችግር በተፈጠረባቸው አካባቢዎችና መነግደ ዳር ባሉ ከተሞች ደጋፊዎቹን ለማስተባበር እንደሚችል መረጃ እንዳላቸው ጠቁመዋል። ተባባሪያችን እንዳለው ይህን መረጃ የተሰጠው በመደበኛ ስብሰባ ደረጃ እንዳልሆነ አመልክቷል። ዋናው ዓላማ ወደተለያዩ አካባቢዎች ከመነቃነቃቸው በፊት አጠቃላይ መረጃ ለማስጨበጥ በሚል ነው።

ተባባሪያችን እንዳለው ሰዎቹ ስለ እያንዳንዱ ፓርቲ ያላቸው መረጃና ለፓርቲዎቹ ያወጡላቸው ደረጃ አስገራሚ ነው። በንግግራቸው መካከል በተደራቢ ስም ሁሉ ይጠሯቸዋል። አንዳንዶቹን ” የልጆች ስብስብ” ይሏቸዋል። ፖለቲካው ያልገባቸውን ” የአንድ ሰው ንብረት” ሲሉ የሚጠሯቸውና አግጣሚውን ለቪዛ ንግድ የሚሯሯጡ እንዳሉ የገለጹት እጅግ ክብር በሚነካ መንገድ ነው። ከምርጫው በፊት መጻፍ አስቸጋሪ በመሆኑ እንጂ ” እኛ መንግስት እንሆናለን” በሚል ቅድሚያ ድርድር ለመቅመጥ የሚፈልጉ መኖራቸውን ስም እየጠሩ ገልጸዋል።

በየተቋማቱ ተመድበው የሚሰሩ የውጭ ዜጎች በዚህ መልኩ ጠቅለል ያለ መረጃ ቢሰጡም በዝርዝር ጥልቅ ቅደም ምርጫ ትንተና ሰርተው ለአገራቸው ማስተላለፋቸውንና ምርጫው ሁከት ይገጥመዋል የሚል ድምዳሜ የለም። ከምርቻው በሁዋላ ግን ከላይ በተገለጸው መሰረት መጠነኛ ችግር ሊኖር እንደሚችል ግምት አለ። በተመሳሳይ ግን ሕዝቡ ሰላም እንደናፈቅውና ሁከት እንደማይፈልግ ደጋግመው ገልጸዋል።

ይህ መረጃ የተሰጠው እነዚህ ክፍሎችን የምርጫ ታዛቢዎችና ጋዜተኞች ሲያገኙዋቸው በስራቸው ጥንቃቄ እንዲወስዱ ለማስቻል ነው። ምርጫውን አስመክቶ እስካሁን በምርጫ ቦርድ ላይ ይህ ነው የሚባል ቅሬታ እንደሌለም በስፋት አውስተዋል።

Exit mobile version