Site icon ETHIO12.COM

የኬሚካል ጦር መሳሪያ ዜና- አዲሱ የጫና ማጥበቂያ አዲሱ መሳሪያ

የቴሌግራፍ ዘጋቢ ዊል ብራውን በትግራይ ክልል የተካሄደውን የህግ ማስከበር ዘመቻን ተከትሎ ባወጣው ዘገባ “መንግስት በትግራይ ክልል የኬሚካል ጦር መሳሪያ ተጠቅሟል” ሲል ላወጣው ዘገባ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባጭሩ “በአሁኑ ወቅት በአገሪቷ ላይ ጫና ለማሳደር ከሚደረገው ጥረት ተለይቶ ሊታይ አይችልም” ሲል ነው መረጃ ያሰራጨው።

ሁሉም ተብሎ ካለቀ በሁዋላ የተፈለገው ባለመሳካቱ አቡነ ማቲያስ በሃይማኖት አባትነት በሚመሩት ህዝብ ላይ ዓለም ክንዱን እንዲያነሳ ሲጠይቁ “ጂኖሳይድ ተፈጽሟል” በሚል ነበር። ጫናውን ለማጥበቅ ያለመ ነው በተባለው የአባ ማቲያስ ጥሪ ተከትሎ በኢትዮጵያ ስም የዓለምን የጤና ድርጅት የሚመሩት የትህነግ አመራር ዶክተር ቴዎድሮስ አድሃኖም አደባባይ ወጥተው እጅግ የተቀነባበረ መግለጫ ሰጡ። “ዘግናኝ” ሲሉ በጠሩት የትግራይ ግጭት የሆነውን ለመግለጽ ቃል እንደሚያጥራቸው አስታውቀው እሳቸውም እንደ አባ ማቲያስ ዓለም ኢትዮጵያ ላይ እጁን እንዲያነሳ ጠይቀዋል።

ይህ ከሆነ በሁዋላ ነው ቴሌግራፍ “የጦር ወንጀል መፈጸሙን የሚያሳይ መረጃ አገኘሁ” ሲል ኢትዮጵያ የተከለከለ መሳሪያ መጠቀሟን የዘገበው። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይን የጦር ወንጀለኛ አድርጎ ለማቅረብ የትህነግ ደጋፊዎች በተደጋጋሚ መዛት የጀመሩት ገና ትግራይን ሳይለቁ እንደነበር የሚያስታውሱ እንዳሉት ውጥኑ ቀደም ሲል ጀምሮ የተቀነባበረ ስለመሆኑ ማስረጃ ነው ይላሉ።

ኢትዮጵያ ተገዳና ሰአራዊቷ ታርዶባት የገባችበትን ጦርነት መልክ ለማስቀየር በየዕለቱ መልካቸውን እየቀያየሩ የሚወጡ መረጃዎች ሄደው ሄደው የኬሚካል ጦር መሳሪያ ተጠቅመዋል የሚል ድምዳሜ ላይ መደረሱ የውጭ ጉዳይ እንዳለው ጫና ማጥበቂያ መሳሪያ፣ የተለመደ የሃሰት ዘገባ ነው። ዘገባው ቅሳነት ገብረሚካኤል የተባለች የ13 ዓመት ታዳጊ አንዷ በኬሚካል መሳሪያ ጉዳት የደረሰባት እንደሆነች አመልክቷል።

መግለጫው እንደሚከተለው ቀርቧል።

“ኢትዮጵያ የኬሚካል ጦር መሳሪያ መጠቀም የሚከለክለውን ሕግ በማስፈጸም ድርጊቱንም በግንባር ቀደምነት ከሚያወግዙ አገራት አንዷ ናት”-የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርግንቦት 16 ቀን 2013

ኢትዮጵያ የኬሚካል ጦር መሳሪያን መጠቀም የሚከለክለውን ሕግ በማስፈጸምና ድርጊቱንም በግንባር ቀደምነት ከሚያወግዙ አገራት አንዷ መሆኗን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ የቴሌግራፍ ዘጋቢ ዊል ብራውን በትግራይ ክልል የተካሄደውን የህግ ማስከበር ዘመቻን ተከትሎ ባወጣው ዘገባ “መንግስት በትግራይ ክልል የኬሚካል ጦር መሳሪያ ተጠቅሟል” በሚል ላሰራጨው የተሳሳተ ጽሁፍ የመረጃውን ሐሰተኛነትና ሃላፊነት የጎደለው መሆኑን ገልጿል።

በመግለጫውም “ኢትዮጵያ እንዲህ አይነት ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርሱ የጦር መሳሪያዎችንና በአለም አቀፍ ደረጃ በስምምነት የተቀመጡ ጸረ ኬሚካል መሳሪያ ድንጋጌዎችን በግንባር ቀደምነት ከሚተገብሩ አገራት አንዷ ነች” ብሏል።

የኬሚካል የጦር መሳሪያዎች ሰለባ የሆነችው ኢትዮጵያ የትኛውም አካል በየትኛውም ቦታ የኬሚካል የጦር መሳሪያዎችን ጥቅም ላይ ማዋል በጽኑ እንደምታወግዝ መግለጫው አመላክቷል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዚህ አስቀድሞ ለአለም አቀፉ ማኅበረሰብ ይህን የመሰለ ሆን ተብሎ የተሳሳተና ኃላፊነት የጎደላቸው ሪፖርቶችን በተመለከተ ተጨማሪ ውጥረትን ከማባባስ ሌላ ዓላማ እንደሌላቸው ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ማስታወቁን ገልጿል።

አሁን የተሰራጨው ሐሰተኛና ሃላፊነት የጎደለው ዘገባም በአሁኑ ወቅት በአገሪቷ ላይ ጫና ለማሳደር ከሚደረገው ጥረት ተለይቶ ሊታይ አይችልም ብሏል።የኬሚካል የጦር መሳሪያዎችን ማምረት፣ ማከማቸትና ጥቅም ላይ ማዋል የሚከለከለው ስምምነት የተዘጋጀው እ.ኤ.አ በ1993 መቀመጫውን በኔዘርላድ ሄግ ባደረገው የኬሚካል የጦር መሳሪያ ክልከላ ድርጅት አማካኝነት ነው። በዚህም ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች 193 አገራት ስምምነቱን የፈረሙ ሲሆን ስምምነቱ ከእ.አ.አ 1997 ጀምሮ ተግባራዊ እየሆነ ይገኛል።


Exit mobile version