Site icon ETHIO12.COM

ቦርዱ በሰኔ 14 በተለያዩ ምክንያቶች ድምጽ የማይሰጥባቸውን አካባቢዎች ይፋ አደረገ

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ በሰኔ 14 በተለያዩ ምክንያቶች የድምጽ አሰጣጥ ሂደቱ የማይከናወንባቸውን የተወሰኑ አካባቢዎች ይፋ አደረገ ።

ቦርዱ በማህበራዊ የትስስር ገጹ እንዳስታወቀው ፣በሰኔ 14 በተለያዩ ምክንያቶች የድምጽ አሰጣጥ ሂደቱ የማይከናወንባቸውን የተወሰኑ አካባቢዎች ይፋ አድርገዋል። በዚህም መሰረት፡-

1. በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከዚህ በፊት የተጠቀሱት አራቱም (መተከል፣ ሺናሻ ልዩ፣ ካማሽ እና ዳለቲ) የምርጫ ክልሎች ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ድምጽ የመስጠት ተግባር አይከናወንባቸውም፣ ቦርዱ ተጨማሪ የአፈጻጸም ሁኔታዎችን ለወደፊት የሚያሳውቅ ይሆናል።

2. በሶማሌ ክልል 14 ምርጫ ክልሎች ላይ (11ዱ ምርጫ ክልሎች ምርመራ ላይ ያሉ) ሰኔ 14 ቀን 2013 ድምጽ የመስጠት ሂደት ለማካሄድ አስቸጋሪ ይሆናሉ የተባሉ ሲሆን ቦርዱ የመራጮች ምዝገባ ላይ የታየ መጠነ ሰፊ የአሰራር ችግር አለ በሚል የቀረበውን አቤቱታ ተከትሎ የአጣሪ ቡድን አሰማርቶ የማጣራት ተግባሩን አጠናቋል፣ በዚህም መሰረት የአጣሪ ቡድኑን ግኝት መሰረት አድርጎ ድምጽ መስጠት ሊከናወንባቸው የሚችል ምርጫ ክልሎች ካሉ ለይቶ የሚያሳውቅ ይሆናል።

3. በኦሮሚያ ክልል ከዚህ በፊት እንደተጠቀሰው ሰባት ምርጫ ክልሎች (ቤጊ፣ ሰኞ ገበያ፣ አያና፣ገሊላ፣አሊቦ፣ጊዳሚ፣ ኮምቦልቻ) ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ድምጽ የመስጠት ተግባር አይከናወንባቸውም።

4. አማራ ክልል ከዚህ በፊት ከተጠቀሱት ስምንት ምርጫ ክልሎች መካከል ድልይብዛ ምርጫ ክልል ላይ ቦርዱ ሰኔ 14 ቀን 2013 ድምጽ መስጠት ሂደት እንዲከናወን ወስኗል። ይህም ከክልሉ መንግሥት በተሰጠ ማረጋገጫ መሰረት የመራጮች ምዝገባ በተስተጓጎለባቸው አምስት ምርጫ ጣቢያዎች አካባቢ ያሉ ዜጎች ሌሎች ጣቢያዎች ላይ መመዝገባቸው በመረጋገጡ ነው።

በሌላ በኩል ግን በአማራ ክልል አንኮበር የምርጫ ክልል ድምጽ መስጠት ሰኔ 14 ቀን እንደማይካሄድም ቦርዱ ወስኗል፣ ቦርዱ ይህንን የወሰነው የአርጎባ ልዩ ምርጫ ክልል ላይ ድምጽ የሚሰጡ ዜጎች ለክልል ምክር ቤት በዚህ ምርጫ ክልል ድምጽ የሚሰጡ በመሆኑ እና በአካባቢው ባለ የጸጥታ ችግር ምክንያት ባለመመዝገባቸው ነው። በዚህም መሰረት በአማራ ክልል በስምንት ምርጫ ክልሎች ሰኔ 14 ቀን ድምጽ መስጠት ሂደቱ አይከናወንም።

5. በደ/ብ/ብ/ህ ክልል ከዚህ በፊት ከተጠቀሱት አራት የምርጫ ክልሎች በተጨማሪ ማጀት መደበኛ የምርጫ ክልል ሰኔ 14 ቀን ድምጽ አይሰጥበትም፤ ይህም የሆነበት ምክንያት በሱርማ፤ በዲዚ፣ በሜኢኔት ልዩ የሚኖሩ ከብሔሩ ውጪ ያሉ ዜጐች ለተወካዮች ም/ቤት በማጀት መደበኛ ላይ ድምፅ ስለሚሰጡ እና የተጠቀሱት ቦታዎች ምዝገባ ስላልተከናወነ ነው።

ከዚህም በተጨማሪ ጉራፈርዳ ላይ ባለው የጸጥታ ችግር የተነሳ የጸጥታ ችግር ሸኮ ልዩ የምርጫ ክልል እና ቴፒ ምርጫ ክልል ሰኔ 14 ቀን ድምጽ መስጠት አይከናወንም። በዚህም ምክንያት ደ/ብ/ብ/ህ ክልል ሰባት ምርጫ ክልሎች ላይ በእለቱ ድምጽ እንደማይሰጥ አስታውቋል።

አዲስ ዘመን ግንቦት 27 ቀን 2013 ዓ.ም


Exit mobile version