Site icon ETHIO12.COM

ኢትዮጵያ መበታተን አልተቻለም፤ አይቻልምም። ኢትዮጵያን የሚበታትኑትን በታትነናቸዋል፤ ወደፊትም እንበትናቸዋለን።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በደብሊው ኤ ኢንደስትሪያል የምግብ ዘይት ኮምፕሌክስ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ ከተናገሩት የተወሰዱ አንኳር ነጥቦች:-

• አንድነታችን እንደዘመኑ ጀግንነት በብልጽግና ላይ መደገም እንዲችል ምክንያት ፌስቡክ ነው፣ ዩቲዩብ ነው፣ እያልን በረባው ባልረባው እንዳንጋጭ አደራ ልላችሁ እፈልጋለሁ።

• የፋብሪካው ባለቤት ከሰራው ፋብሪካ በላይ ያለውን ለማካፈል ባለው ፍላጎት ምስጋና ይገበዋል፤ ይህ ልባም ባለጸጋ መስራት ብቻ ሳይሆን መካፈልን አስተምሯል።

• አትዮጵያ ሶስት ወሳኝ ምሰሶዎች አሏት፤የመጀመሪያው ምሶሶያችን ፈጣሪ ነው፣ ሁለተኛው ኢትዮጵያን ለማልማት ወደኋላ የማይለው የኢትዮጵያ ህዝብ ሲሆን ሶስተኛው በፈጣሪ የተሰጠን አንጡራ ሀብታችን ነው።

• እነዚህ ሀብቶች ማልማት የሚችል ህዝብ ልበ ብርሃን የሆነ ህዝብ እና ፈጣሪውን የሚፈራ ህዝብ ስንሆን ኢትዮጵያ የሚገዛትም የሚያስቆማትም ኃይል በምድር ላይ አይኖርም።

• የእኛ የኢትዮጵያዊያን ዋና አደጋ የፈጠረንን አምላክ አላማውን ስተን መጣላት ስንጀምር የኢትዮጵያ ህዝብ አንድነት ሲያጣ ፣ የኢትዮጵያ ሀብት እና ጸጋዎች ማልማት ሲሳነን የሌሎች መሳለቂያ እንሆናለን።

• ኢትዮጵያዊያን ፈጣሪ እንዳለን እና አንድ መሆን እንዳለብን እንዲሁም ተዝቆ የማያልቅ ሀብት እንዳለን ከተገነዘብን ግን ለዓለም ምሳሌ እንሆናለን እንጂ የማንም ሀገር መፈንጪያ አንሆንም።

• አንድነታችንን፣ ፈጣሪያችንን እንዲሁም ሀብታችን ደግሞ እንዲህ አድርጎ የሚያለማ ባለጸጎችን እንዲያበዛልን መትጋት ይኖርብናል።

• ሁለት ልበ ብርሃኖች በሁለት ወር አይተናል፤ ጎጃም ውስጥ ብዙ ሺህ ልበ ብርሃኖች እንዲፈጠሩ እንመኛለን።

• ስንፍናን በማይወዱ ተግተው በሚሰሩ ሀገራቸውን በሚወዱ አሁን አንበሳ መግደል ሳይሆን ኑሮን ማሸነፍ ነው ጀግና የሚያሰኘው ።

• ድሮ ብዙ ሰራዊት አስከትሎ መሸፈት ጀግንነት ነበር፤ አሁን ግን እንደልባሙ በለጸጋ ወርቁ አይተነው ብዙ ሰራተኞችን ቀጥሮ ስራ ማስፋፋት ነው ጀግንነት።

• አባቶቻችን ታሪክ ሰርተው አውርሰውናል፤ እኛም ብልጽግና በማውረስ የሚያኮራ ታሪክ ብቻ ሳይሆን ስንዴ የማይለምን ትውልድ፣ የማይፈራ ትውልድ እንዲሁም ያሰበውን ማድረግ የሚችል ትውልድ እንድንፈጥር የትብብር መንፈስ ያስፈልጋል ብለዋል።

• ኢትዮጵያ ለጎረቤት ሀገር የሚሸልሙ ባለሀብቶች መፍጠር ትችላለች፡፡

• ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ብሔሮች ቋንቋቸው ቢለያይ፣ ታሪካቸው የተለያየ ቢመስል፣ ኢትዮጵያ በምትሰኝ ብልቃጥ ውስጥ አብረን እስካለን ድረስ አንዳችን ለሌላችን መከታ እና ጋሻ እንጂ አንዳችን ለሌላችን ጠላት መሆን አንችልም።

• ከውጭ ኢትዮጵያን እየነቀነቁ ጠላት የመጣ እያስመሰሉ ጎጃም ከኢትዮጵያ ለመለየት የሚጥሩ ኃይሎችን አውቀንባችኋል ብለን በጋራ መቆም እንጂ ጠላት መጣ ብለን መባላት አስፈላጊ አይደለም።

• ኢትዮጵያ መበታተን አልተቻለም፤ አይቻልምም። ኢትዮጵያን የሚበታትኑትን በታትነናቸዋል፤ ወደፊትም እንበትናቸዋለን።

• በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ሌሎች ነጋሪ መስካሪ መሆን አይችሉም፡፡

Exit mobile version