Site icon ETHIO12.COM

መንግስት ዕርዳታን አስመልክቶ ከደረግ እንዲማር ሕዝብ እየጠየቀ ነው

የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ዕርዳታን ለጦርነት እንዴት እንደተጠቀመበት የሚያውቁ ዜጎች ዛሬም መንግስት ከደረግ ስህተት በመማር ለአፍታም ቸል እንዳይል ጥሪ እያሰሙ ነው። በእርዳታ ስም የገቡ ድርጅቶቻቸው አቋማቸውና አካሄዳቸው የማይምር መሆኑንን የሚያሳዩ ምልክት በመታየታቸው አንዳንዶች ስጋት እንዳላቸውም እየጠቀሱ ነው።

በማህበራዊ ሚዲያ፣ በተለያዩ አውዶችና በጎንዮሽ ሕዝብ ” የእርዳታ ቁሳቁስ ሊፈተሽ ይገባል። መፈተሽ ከደህንነታችን አንጻር ለነገ የሚባል አይደለም። ለጋሾችም ቢሆኑ ፍተሻን የሚቃወሙበት አንዳች ህጋዊ መሰረት የላቸውም” ብለዋል። ኢዜአ ያነፋገራቸው ባለሙያ የሚከተለውን ብለዋል።

የተራድኦ ድርጅቶች ከተፈቀደላቸው ተግባር ውጭ እንዳይንቀሳቀሱ መንግስት ጥብቅ ቁጥጥር ማድረግ እንዳለበት የህግና የታሪክ ምሁር ዶክተር አልማው ክፍሌ ተናገሩ።የተራድኦ ድርጅቶች ከአድሎ በጸዳ መልኩ ሰብዓዊነት፣ ገለልተኝነትና ነጻነታቸውን ጠብቀው በችግር ውስጥ ያሉ ሰዎችን ለመርዳት የተቋቋሙ ናቸው።

ዓለም አቀፋዊ የሰብዓዊ ድርጅቶች ደግሞ በየትኛውም የዓለም ጥግ ያሉ አገሮች ተፈጥሯዊም ሆነ ሰው ሰራሽ ችግሮች ወይም ግጭት ሲገጥማቸው ድጋፍ ለማድረግ ይገባሉ።በኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርስቲ የህግና የታሪክ ምሁር ዶክተር አልማው ክፍሌ፤ አገሮች ቀውስ በሚገጥማቸው ጊዜ የተራድኦ ድርጅቶች የሚያደርጓቸው ሰብዓዊ ድጋፎች ትልቅ ፋይዳ እንዳላቸው ያስረዳሉ።ነገር ግን እነዚህ ድርጅቶች በአንድ አገር ውስጥ ለሰብዓዊ ድጋፍ ሲንቀሳቀሱ መከተል የሚጠበቅባቸው መብቶችና ግዴታዎች መኖራቸውን ተናግረዋል።

የተራድኦ ድርጅቶቹ ሥራቸውን ሲያከናውኑ የአገር ሉዓላዊነትን ባከበረ መልኩ መሆን እንዳለበት አመልክተው፤ በውስጣዊ ፖለቲካ እንዲሁም ህዝብንና አገርን ከሚጎዱ እንቅስቃሴዎች መታቀብ እንዳለባቸውም አንስተዋል።መንግስት በትግራይ የወሰደውን የህግ ማስከበር እርምጃ ተከትሎ ዓለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅቶች ወደ አካባቢው መግባታቸውን ጠቅሰው፤ የድርጅቶቹ ሰራተኞች ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ተገቢ ባለሆነ እንቅስቃሴዎች ውስጥ እየታዩ መሆኑን ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት አንዳንድ የተራድኦ ድርጅት አባላቶች ተገቢ ባልሆነ መልኩ በህዝብና መንግስት ላይ የሽብር እንቅስቃሴን አንግበው ለሚንቀሳቀሱ ሃይሎች የመወገን አዝማሚያ እንደሚታይም ጠቅሰዋል።በአሸባሪነት የተፈረጀው ድርጅት አባላት በተራድኦ ድርጅቶች ቅጥር ግቢ ውስጥ ሲንቀሳቀሱ በማህበራዊ ሚዲያዎች መሰራጨቱንም ለአብነት አንስተዋል።

አሸባሪው “ህወሃት ደርግን ለመጣል ባደረገው የትጥቅ ትግል የተራድኦ ድርጅቶች የጦር መሳሪያ በማቀበል ሲያግዙ ነበር” ያሉት የህግና ታሪክ ምሁሩ፤ መንግስት ከደርግ ዘመን ሂደቶች ትምህርት በመውሰድ የተራድኦ ድርጅቶች የሚያደርጉትን ያልተገባ እንቅስቃሴ መከታተል እንዳለበት ገልጸዋል።በእርዳታ ስም ሌሎች የአገሪቱን ህግ የሚጥሱ ተግባራት እንዳይከናወኑ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ ገልጸው፤መንግስት አስፈላጊውን ፍተሻ የማድረግና እርዳታው ለተገቢው አካል መድረሱን ማረጋጋጥ እንዳለበትም ተናግረዋል።መንግስት ግብረ ሃይል በማቋቋም የቁጥጥር ስራውን ማከናወን እንደሚችልም ዶክተር አልማው ተናግረዋል።


Exit mobile version