Site icon ETHIO12.COM

አማራ ክልል ክተት አወጀ፣ ልዩነት ወደጎን ሲል የቀደሞ ጦር ኣባላትን ጠራ

Members of Amhara Special Forces stand guard along a street in Humera town, Ethiopia July 1, 2021. Photo: Reuters.

አንድነታችንን ጠብቀን ያጋጠመንን የህልውና አደጋ በትግላችን እንቀለብሰዋለን፡፡

የኢትዮጵያና የአማራ ህዝብ ጠላት የሆነው ትህነግ ወያኔ እንደአገር ባደረሰብን ህልቆ መሳፍርት የሌለው ግፍና በደል እንዲሁም ለፈጸመብን ሀገራዊና ህዝባዊ ክህደት የአገራችንን የግዛት አንድነት በመሸርሸር ሉአላዊነቷ የማይከበር፣ ራሷን ችላ መቆም የማትችልና በሁሉም መስክ ተንበርካኪ ሀገር ባለቤቶች እንድንሆን በርካታ ደባ ፈጽሞብናል፡፡ በአለም አደባባይ የምንኮራበት ሀገራዊና ህዝባዊ የጋራ ታሪክ ባህልና እሴት እንዳይኖረን አንድነታችንንና አብሮነታችንን በፈጠራ ታሪክ እየቦረቦረ እርቃናችንን እንድንቀር፣ አንዳችን ለሌላችን ጋሻና መከታ መሆን ሲገባን እርስ በእርስ በመጠራጠር አውሎ ነፋስ ወዲያና ወዲህ እንድንላጋና በጠላትነት እንድንፈራረጅ ከሰማይ በታች ያልፈጸመብን ግፍ የለም፡፡

ከሁሉም የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች ጋር ተባብረንና ተፈቃቅደን የጸረ ጭቆና ትግሉን አንድ ብለን ስንጀምር በጋራ ያነሳነው የፍትህና የእኩል ተጠቃሚነት ጥያቄ በትህነግ መንደር የቱን ያህል መራር የሆነ የመደፈር ስሜት እንደፈጠረ የቅርብ ጊዜ ክስተት ነው፡፡ አሸባሪው ትህነግ ከመንበረ ስልጣኑ ተምዘግዝጎ ሲወድቅና መቀሌ ሲከትም የነበረው ብቸኛ ምክንያት አይናችሁን ጨፍኑና ላሞኛችሁ የሚል ፖለቲካዊ ቁማር እንደነበር የሚዘነጋ አይደለም፡፡በውሁድ ፓርቲ ደረጃ የተፈጠረውን አዲስ የፖለቲካ ፓርቲ አደረጃጀት የአህዳውያን ውጤት አድርጎ ያበሻቀጠው ፍላጎቱ በለመደው የአድራጊ ፈጣሪና የአዛዥነት ሚና ያልተሳተፈበትን መዋቅር ለማጣጣል ከማለም ባሻገር ለኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች እኩል ተጠቃሚነት ባለው ከፍ ያለ ንቀትና ጥላቻ ምክንያት መሆኑ ለሁሉም ግልጽ ነው፡፡

ይህንን ተከትሎ በትግራይ ክልል የሰሜን ዕዝ እንዳይነቀሳቀስ በተደጋጋሚ ያደረገው ሙከራ የልብ ልብ ሰጥቶት ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም.የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች ውድ ልጆችን በግፍ ያለርህራሄ አሰቃቂ ግድያ ከፈጸመባቸው በኋላ የዕዙን ጠቅላላ ንብረት በመውረስ በመላው ኢትዮጵያውያን ላይ ጦርነት ማወጁ ይታወቃል፡፡ የአማራ ክልልን ወሰን ጥሶ በማለፍ ጥቃት ለመፈጸም ያደረገው ጥረት ባይሳካለትም በማይካድራ ንጹሀን ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ላይ የፈጸመው አረመኔያዊ የጅምላ ጭፍጨፋ የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ይህንን ተከትሎም መንግስት በየደረጃው የህግ የበላይነት ለማስከበር ዘርፈ ብዙ ስራዎችን አከናውኗል፡፡በሂደቱም በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸው የሚዘነጋ አይደለም፡፡ይሁን እንጂ ይህ አረመኔና አሸባሪ ቡድን አይኑን በጨው አጥቦ ጥቃት የተፈጸመበት በማስመሰል አለምአቀፉን ማህበረሰብ በተደጋጋሚ በማጭበርበር ላይ ይገኛል፡፡

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐፕሊክ መንግስት በአንድ ወገን የወሰደውን የተኩስ አቁም ውሳኔ እንደመልካም አጋጣሚ በመጠቀም በኢትዮጵያና በአማራ ክልል ህዝብ ላይ መሰረተ ሰፊ የሆነ ወረራና ጥቃት ማድረግ ጀምሯል፡፡ ይህ አሸባሪ ቡድን የጀመረብንን ግልጽ ወረራ ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ እንደሚያወግዘውና የምንጊዜም አጋራነቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ፍጹም ጥርጣሬ የለንም፡፡ በዚህ አጋጣሚ የኢትዮጵያ መንግስትና ህዝብ በግልጽ እንደሚያውቀው የአማራ ክልልና ሕዝብ የዚህ አሸባሪ ቡድን ቀጥተኛና የቅርብ ተጠቂ መሆኑን ነው፡፡ ስለሆነም ትግላችን ለህዝባችን ህልውናና ለሀገር ሉአላዊነት መሆኑ ግንዛቤ ውስጥ ገብቶ የጋራ ጠላታችንን በጋራ እንድንፋለመው የአጋርነት ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

አሸባሪው የትህነግ ቡድን ከአማራ ክልል ጋር በሚያዋስኑት ሁሉም አቅጣጫዎች መጠነ ሰፊ ወረራና ጥቃት እየፈጸመ የሚገኝ አረመኔና ጨካኝ ቡድን መሆኑ እንዲታወቅና ሁሉም የአማራ ክልል ህዝብ ጉዳዩን ከህልውናው ጋር በማስተሳሰር እንዲመለከተውና ከዚህ ጨካኝና አረመኔ ቡድን ጋር ቀጣይ የምናደርገው ሁሉ አቀፍ ትግል የህልውና ትግል መሆኑን አውቆ በገንዘብ፣ በጉልበትና በህይወት መስዋዕትነት አስፈላጊውን አበርክቶ ለማድረግ ራሱን እንዲያዘጋጅና የመንግስትን ጥሪ እዲጠባበቅ የክልሉ መንግስት ጥሪውን ያቀርባል፡፡

አሸባሪው ትህነግ የትግራይን ህዝብ ከህጻን እስከአዋቂ በማንቀሳቀስ አለም አቀፍ የጦርነት ህግጋትን በመቃረን ህጻናትንና ሴቶችን በጅምላ ጦርነት እየማገደና ያለ የሌለውን አቅሙን ተጠቅሞ ክልላችን ላይ ወረራ የፈጸመ ሲሆን በተለይም ለዘመናት የአማራ ህዝብ የማንነትና የወሰን ጥያቄ እያነሳ ሲታገልባቸው የቆዩ የራያ አላማጣና ኮረም አካባቢዎችን ዳግም በመውረር እንዲሁም ወልቃይት ጠገዴ ሴቲት ሁመራ በኃል ለመያዝ በተለይም ጠለምትና አካባቢውን ለመያዝ አሁናዊ ሙከራ የጀመረ መሆኑ በአካባቢው የሚኖሩ አማራዎችንና የአማራ ክልል ተወላጆችን ፈጽሞ የማጥፋት ህልሙን እውን ለማድረግ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ ስለሆነም ይህንን አረመኔያዊ ድርጊትና ዳግም ወረራ የክልሉ መንግስት በፍጹም የማይቀበለውና በጀመርነው የህልውና ትግል ተፈጥሯዊና ታሪካዊ መብታችንን የምናረጋግጥ መሆኑን አበክረን እንገልጻለን፡፡
ስለሆነም፡-

1ኛ. በየግንባሩ የምትገኙ የሀገር መከላከያ ሰራዊት አባላት፣ የክልላችን ልዩ ኃይልና የሚሊሻ አባላት፣ ህዝባዊ ፖሊስና ሰላም አስከባሪ አባላት እንዲሁም አገርና ህዝብን ለማዳን የተግባር እንቅስቃሴ እያደረጋችሁ ያምትገኙ የየክልሉ የጸጥታ አካላት በዚህ ታሪካዊ መድረክ ከጠላት ጋር ፊት ለፊት በመግጠም ለአገራችሁ ሉአላዊነትና ለህዝባችሁ ህልውና የምትከፍሉትን ክቡር መስዋዕትነት ታሪክ ምንጊዜም ሲያስታውሰው ይኖራል፡፡ በቀጣይም የተሰጣችሁን ህዝባዊና አገራዊ ተልዕኮ በጽናትና በቁርጠኝነት እንደምትወጡ እምነታችን የጸና ነው፡፡ስለሆነም መላው የኢትዮጵያና የአማራ ህዝብ ከጎናችሁ መሆኑን አውቃችሁ በጀግንነት ታሪካዊ ጠላታችንን በመደምሰስ ለአገራችሁ ዳግም የኩራት ምንጭ እንድትሆኑ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

2ኛ. መላው የኢትዮጵያ ህዝብ በትህነግ ወያኔ ላይ የተጀመረው ህግን የማስከበር ትግል ተጠነናክሮ እንዲቀጥል አስፈላጊውን እርብርብ ሁሉ ማድረግ አለበት ብለን እናምናለን፡፡ አሸባሪው ትህነግ አገር ከማፍረስ እኩይ ተልዕኮው ሊታቀብ የሚችለው የአገራችንን ሉአላዊነትና የግዛት አንድነት በጽናትና በአላማ ቁርጠኝነት
በጋራ መጠበቅ ስንችል ስለሆነ በዚህ ታሪካዊ መድረክ ላይ በጋራ እንድንቆም የአክብሮት ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

3ኛ. በየትኛውም ዘመን ሰልጥናችሁ፣ የአገርና የህዝብ ሉአላዊነት ለማስከበር በማንኛውም የመንግስት ጸጥታ መዋቅር ውስጥ ተሰልፋችሁ ስታገለግሉ የቆያችሁና በታሪክ አጋጣሚ የሙያ ዘርፍ የቀየራችሁ የክልላችን ነዋሪዎች ለህልውናችን የምናደርገውን የትግል ጥሪ ተቀብላችሁ በክልሉ ጸጥታ መዋቅር ውስጥ እንድትቀላቀሉ ጥሪያችንን እያቀረብን ከዛሬ ጀምሮ በየአካባያችሁ ሰላምና ደህንነት ጽ/ቤት በአካል ተገኝታችሁ በፈቃደኝት እንድትመዘገቡ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡

4ኛ. መላው የክልላችን ወጣቶች ከፊት ለፊታችን የተደቀነብንን የህልውና አደጋ ያለበቂ ዝግጅትና ደረጃውን ከጠበቀ ስልጠና ውጭ የምንጋፈጠው አይደለም፡፡ ስለሆነም ከማንኛውም ግብታዊ እንቅስቃሴ ታቅባችሁ በየደረጃው ለሚኖረው ምልመላና ስልጠና በመሳተፍ በቂ ዝግጅት አድርጋችሁ የመንግስትን ጥሪ እንድትጠባበቁ እናሳስባለን፡፡

5ኛ. መላው የክልላችን ተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሲቪክና የሙያ ማህበራት፣ ማህበራዊ አንቂዎችና የሚዲያ ባለሙያዎች የጀመርነው የህልውና ትግል የሁላችንንም አንድነት፣ ህብረትና ተቀራርቦ መስራት የሚጠይቅ ነው፡፡ በሩቅ ሆኖ ስህተት በመፈለግና እርስ በእርስ በመነቋቆር ከጠላት መንጋጋ ፈልቅቀን የምንታደገው አንዳችም ህልውና የለንም፡፡ በቂ መረጃ ባገኘንበትም ባላገኘንበትም ጉዳይ ላይ ተሳፍረን በተለያዩ አቅጣጫዎች መክነፍ ለጠላቶቻችን ተጨማሪ ጉልበት ከመሆን ባለፈ ለህዝባችን የሚሰጠው ጥቅም የለም፡፡ ስለሆነም የጋራ ዕጣ ፋንታችንን በጋራ ጥረት የምናስከብርበትና አደጋ የተጋረጠበትን የህዝባችንን ህልውና ከጠላት ጥቃት የምንታደግበት የታሪክ መድረክ ላይ ስለምንገኝ ከመቸውም ጊዜ በላይ ልዩነታችንን ወደጎን በመተው የህዝባችንን አንድነት ጠብቀን በጋራ እንድንረባረብ የክልሉ መንግስት ጥሪውን ያቀርባል፡፡

6ኛ. መላው የክልላችን ህዝብ፣ በከተማና በገጠር የምትኖሩ የክልላችን ነዋሪዎች፣ በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጭ የምትገኙ ምሁራንና የክልላችን ተወላጆች፣ በተለያየ ሙያ ተሰማርታችሁ አገርና ህዝብ በማገልገል ላይ የምትገኙ የክልላችን ነዋሪዎችና ባለሀብቶች የጀመርነውን የህልውና ትግል በማገዝ የትግል ሂደት አዎንታዊ ሚናችሁን እንድትወጡ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

በመጨረሻም የጀመርነው ትግል እልህ አስጨራሽ በጣም መራርና ረዥም ጊዜ የሚጠይቅ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡የፈጀውን ጊዜ ይፍጅ የእኛ አንድ መሆንና ለጋራ ግብ በጋራ መተባበር በመድረኩ አሸናፊ ሆነን እንደምንወጣ ያለምንም ጥርጥር ልናረጋግጥልችሁ እንወዳለን፡፡ሁልጊዜም ቢሆን የአማራ ክልል ህዝብ ትግል ከኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች የጋራ ተጠቃሚነት ውጭ እንደማይሳካ ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡ የምናደርገው ትግል
ለአገራችን ሉአላዊነት መከበርና የጭቁን ህዝባችን የህልውና ትግል እንጂ እላፊ ጥቅም ለማግኘት የምናደርው ትግል በፍጹም አይደለም፡፡

የአማራ ህዝብ ከፉክክር ይልቅ ትብብርን ከእብሪት ይልቅ ድርድርን የሚያስቀድም በፍትህ ከሄደች በቅሎየ ያለፍትህ ያጣኋት ጭብጦየ ትቆረቁረኛለች ብሎ የሚያምን ህዝብ ነው፡፡ ስለሆነም ዛሬ የምናደርገው ትግል ለልጅ ልጆቻችን የምናወርሰው የኩራትና የክብር ምንጭ እንደሚሆን አንጠራጠርም፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ሪፐፕሊክ መንግስት የወሰደው ተናጠላዊ የተኩስ አቁም ውሳኔን ተከትሎ የጠላት ኃይል አገርና ህዝብ ለማዋረድ የሚያደርገውን እብሪተኛ እንቅስቃሴ መሰረት በማድረግ በጠላት ላይ የማያዳግም እርምጃ እንዲወስድ በአጽንኦት እናሳስባለን፡፡

ትግላችን ለህልውናችን !

ሐምሌ 6 ቀን 2013 ዓ.ም
የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት

Exit mobile version