Site icon ETHIO12.COM

በመንግሥታቱ ጉባኤ ተቃውሞ የገጠመው ዘረኝነትና የጅምላ ጥረዛ

የቆዳ ቀለምን መነሻ አድርጎ የሚፈፀም ጥቃት፣ የጅምላ እስርና የስደተኞች ጥረዛ የሃብት ኦጦት ሳይሆን የዘረኝነት ውጤት ነው ሲሉ ኢትዮጵያን ጨምሮ በርካታ የአፍሪካ አገራት ተቃውሟቸውን አሰሙ።

በተባበሩት መንግሥታት 76ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ዘረኝነትን መፀየፍና የስደተኞች አያያዝን የተመለከተው የደርባን ቃል ኪዳንና የ20 ዓመታት ትግበራው ላይ ያተኮረ ውይይት ተደርጓል።

በ2 ዙር የተከፈለውን ውይይት በመጤ ጠል ተደጋጋሚ ግጭት የምትፈተነው ደቡብ አፍሪካ የዓለም ዐቀፍ ግንኙነትና ትብብር ሚኒስትሯ ናለዲ ፓንዶር (ዶ/ር) እና የጋቦን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፓኮሌት ሙቤለት ቦቢያ ሲመሩ አገራት ጥቁር የቆዳ ቀለም ባላቸው ላይ እየደረሰ ያለውን የዘረኝነት ጥቃት እያነሱ ተቃውመዋል።

የስደተኞች አያያዝና ከፅየፋ የሚነሳውን የማግለል እንዲሁም የጅምላ ጥረዛ በመጥቀስም ዘረኞች በገንዘብ እጥረት ሳይሆን ውስጣቸው ባለው አግላይ ስሜት ያልተገባ እርምጃ እየወሰዱ እንደሆነ ነው በርካታ የአፍሪካ አገራት መሪዎች የገለፁት።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ደመቀ መኮንን “በተወሰኑ ሃብታም አገሮች ስደተኞች ለብዝበዛ፣ ጅምላ ጥረዛ፣ እስርና ለምግብ ክልከላ ይዳረጋሉ” ብለዋል። አክለውም “ከእነዚህ እሳቤዎች ጀርባ ያሉት ፖሊሲዎች የሃብት እጥረት ሳይሆን የመጤ ጠልነት ውጤት ናቸው” ሲሉ ኮንነዋል።

በተባበሩት መንግሥታት የኤርትራ ቋሚ ተወካይ አምባሳደር ሶፊያ ተስፋማሪያም “ካሳ ማለት ከገንዘብ የሚሻገር ማካካሻ ነው፤ ስደተኞችን አለመቀበልና እሴታቸውን አለመጠበቅ የበላይ ሆኖ የመታየት ሃሳብ ነው፤ እውነተኛውን የታሪክ እድገት ሳናስተምር መገለልን ልንዋጋው አንችልም” ሲሉ ተናግረዋል።

የዛምቢያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይና ትብብር ሚኒስትሯ ኔቲምቦ ናንዲ ዳትዋህ “የመገለል፣ ጥላቻ ንግግሮች፣ ስርዓታዊ ዘረኝነት፣ ደም አፋሳሽ የዘረኝነት ግጭቶች እና መጤ ጠልነት መጨመር ሥራችንን ያለመከወናችን ግልፅ ማሳያ ናቸው” ብለዋል።

የአንጎላ ውጭ ግንኙነት ሚኒስትሯ እስመራልዳ ሜንዶንካ በበኩላቸው ዘረኝነትና ማግለልን አጥብቀን እናወግዛለን በማለት የደርባን ቃል ኪዳን ምክረ ሃሳቦችን ለመተግበር ጥረታችንን ማስፋት አለብን ሲሉ ተደምጠዋል።

የአልጀሪያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስተሩ ላማምራ ዲዝ ዓለም ዐቀፉ ማኅበረሰብ ጨዋዎቹን አፍሪካዊያን በእያንዳንዱ ድርጊቱ የማክበር ግዴታ አለበት በማለት ማኅበረሰብና ሃይማኖትን የጥቃት ሰለባ ለማድረግ የሚሰሩ የመገናኛ ብዙኃን ዘገባዎችንም አገራቸው እንደምታወግዝ አስታውቀዋል።

“የአፍሪካ ኅብረት ለደርባኑ ስምምነት መርሆዎች ስለመገዛት ደጋግሞ አሳስቧል” ያሉት የሞሪሺየስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አለን ጋኖ “ዘርን መነሻ አድርጎ የሚፈፀም ቸል ማለትና መብትን መግፈፍ የተባበሩት መንግሥታት ምስረታ የቆመበትን መሰረት የሚጣረስ” ስለመሆኑም አስምረውበታል።

የዩጋንዳ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ሙሊምባ በበኩላቸው “ዘረኝነትን፣ በዘር መገለልና መጤ ጠልነትን የመከላከል የጋራ ጥረታችንን ወደላቀ ምዕራፍ ማሻገር ከፈለግን ተጨባጭ ተግባር መውሰድ አለብን፤ ትርጉም ያለውና አዎንታዊ ውጤት ለማምጣት ከሻትንም ጊዜው የተግባር ነው” ብለዋል።

ከምትገኝበት አፍሪካ ይልቅ የነጮች ነው የምትለውን የምዕራብና አረቡን ዓለም ናፋቂ ነች በሚል የምትተቸው ግብፅ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሚህ ሽኩሪ “መሻሻሎች እንዳሉ ሆኖ ፈተናዎች በተለያዩ መልኩ እንደቀጠሉ ነው፤ ዘረኝነትን ለመቀነስ እጅ ለጅ ተያይዘን መስራት አለብን” ማለታቸውን በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኅብረት ተልዕኮ በቲውተር ገፁ ጽፏል።

የተባበሩት መንግሥታት የሰብኣዊ መብቶች ኃላፊ ሚሼል ባችሌት በበኩላቸው “በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በዘረኝነትና መገለል ውስጥ መኖራቸውን ቀጥለዋል” ብለዋል። የዘረኝነት ሰለባ ለሆኑ አፍሪካዊያንና ዘረኝነት በወለደው ጥላቻ ተገልለው ለሚኖሩ ሁሉ ፍትሕን ለማሰጠት ጠንካራ ጥረትና ንቅናቄ ያስፈልገናል ሲሉም ጨምረዋል።

Via – walta information

Exit mobile version