Site icon ETHIO12.COM

አማራ ክልል አዲስ ርዕሰ መስተዳድር ሾመ

የአማራ ክልል ምክር ቤት 6ኛ መሥራች ጉባኤ እየተካሄደ ነው፡፡ የአማራ ብልጽግና ፓርቲ ዶክተር ይልቃል ከፋለ ለክልሉ ርእሰ መሥተዳድርነት በእጩነት አቅርቧል፡፡ጉባኤውም ዶክተር ይልቃል ከፋለ የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አድርጎ መርጧቸዋል። ፕሬዚዳንቱ ቃለ መሃላ ፈጽመዋል።

“አማራ መንግስት ማቋቋም አይችልም” በሚል ፕሮፓጋንዳ ሲነዛ ቢቆየም የክልሉ ሚዲያ እንዳለው አዲስ መንግስት ምስረታው በተያዘለት እቅድ መሰረት እየሄደ ነው። ዶክተር ይልቃል የትምህርት ቢሮ ሃላፊ እንደነበሩ ታውቋል።

ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋየ የአማራ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ሆነው ተመርጠዋል፡፡በጉባኤው አቶ አማረ ሰጤ ምክትል አፈ ጉባዔ ሆነው ተመርጠዋል፡፡የቀድሞው የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ ወይዘሮ ወርቀሰሙ ማሞ አዲስ ለተመረጡት አፈጉባኤ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋየ የስልጣን ርክክብ አድርገዋል፡፡

አዲሱ መሪ በወራሪው የህወሓት የሽብር ቡድን የተያዙ የአማራ ክልል አካባዎችን በህልውና ዘመቻው በአጠረ ጊዜ ነፃ ለማውጣት በትኩረት እንደሚሰሩ አስታውቀዋል።

በህልውና ዘመቻው ወራሪውን ቡድን አቁስሎ መተው ብቻ ሳይሆን ስጋት እንዳይሆን አድርጎ መተው ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራም ርዕሰ መስተዳደሩ ለአማራ ክልል ምክር ቤት ባደረጉት ንግግር አመልክተዋል፡፡

የወራሪው ቡድን በሰሜን ወሎ፣ዋግ ኸምራ እና ሰሜን ጎንደር ወረራውን በመፈፀም የአማራን ህዝብ ቅስም ለመስበር ያደረገውን ጥረት መላ የክልሉ ህዝብ በአንድነት በመቆም ህልውናውን ለማስከበር አኩሪ ጀብዱ በመፈፀም አንድነቱን አሳይተዋል ብለዋል፡፡

ወራሪው የሽብር ቡድን እየፈፀመ ያለው ጭፍጨፋ፣ ማፈናቀል እና ንብረት ማውደም የአማራ ክልል ህዝብ አንድነት እንዲቆም ከማድረጉ ባሻገር፣ የኢትዮጰያን አንድነት ለማስከበር የቆመ መሆኑን በዘመቻ ህልውናው በግልፅ ማሳቱንም ርዕሰ መስተዳደር ይልቃል ከፍአለ /ዶ/ር/ ተናግረዋል፡፡የአማራ ህዝብ ህልውና እና ክብር የሚረጋገጠው ከሌሎች ወንድም ኢትዮጵያዊያን ጋር በመሆኑ ለዚህ ትኩረት ሰጥቶ ክልሉ እንደሚሰራም ተናግረዋል፡፡የዘመቻ ህልውናውን በአጭር ጊዜ ለማጠናቀቅ ክልሉ ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ተፈናቃዮችን ለማቋቋምም እና ድጋፍ ለማድረግ አዲሱ የክልሉ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራም አስታውቀዋል፡፡

Exit mobile version