Site icon ETHIO12.COM

የቀድሞው የፌስቡክ ሠራተኛ የፌስቡክን ሚስጥር አጋለጡ

ፌስቡክ ኢትዮጵያን ጨምሮ በሌሎችም አገራት ሐሰተኛ መረጃና ግጭት ቀስቃሽ መልዕክቶችን እንዳላስቆመ በይፋ ተናግረዋል።

የአሜሪካ ኮንግረስ ፊት ቀርበው ቃላቸውን የሰጡት ፍራንሲስ ሐውገን ፌስቡክ በኢትዮጵያና በምያንማር ግጭት ቀስቃሽ እና ሐሰተኛ መረጃዎችን ሳያስቆም ቀርቷል ብለዋል።

“እርምጃ የማይወሰድ ከሆነ አሁን ላይ የምናያቸው ጽንፈኛ ድርጊቶች እየተባባሱ ይሄዳሉ ብዬ እፈራለሁ። በኢትዮጵያና በምያንማር ያየናቸው ነገሮች ወደባሰ ደረጃ የሚደርሱ፣ የአስፈሪ ታሪክ የመጀመሪያ ምዕራፍ ናቸው” ብለዋል።

ፌስቡክ ሐሰተኛ መረጃዎችን፣ ግጭት ቀስቃሽ መልዕክቶችን እንዲሁም የጥላቻ ንግግሮችን ከመሰራጨት ማስቆም እንዳልቻለ ተናግረዋል።

የ37 ዓመቷ የቀድሞው የፌስቡክ ፕሮዳክት ማናጀር በአሜሪካ ምክር ቤት ተገኝተው ቃላቸውን ሲሰጡ ድርጅቱን በጽኑ ወቅሰዋል።

ፌስቡክ ለሚለጠፉት መልዕክቶች ኃላፊነት እንዲወስድ መደረግ እንዳለበት ለኮሚቴው ባደረጉት ንግግር ጠቁመዋል።

ፌስቡክን ተጠያቂ ማድረግ የሐሰተኛ መረጃ ስርጨትን እንደሚገታ አልፎም ግጭት እንዳይነሳ እንደሚከላከል ተናግረዋል።

ፌስቡክ በአምባገነን እና የሽብር ድርጅት መሪዎች ጥቅም ላይ እየዋለ እንደሆነ በንግግራቸው አጋልጠዋል። እነዚህ አካሎች እየተጠቀሙበት እንደሆነ ፌስቡክ መረጃው እንዳለውም አክለዋል።

የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ላይክና ሼር እንዲያደርጉ እንዲሁም አስተያየት እንዲሰጡ የሚያነሳሱ ጽሑፎች በገጹ ወደላይ እንደሚገፉ ተናግረዋል።

“እነዚህ መልዕክቶች እንደ ኢትዮጵያ ባሉ በብሔር ክፍፍል የሚናጡ አገሮች ውስጥ ግጭት እያስነሱ ነው” ሲሉ አብራርተዋል። ፌስቡክ ክሱን ውድቅ አድርጓል።. Via – @tikvahethiopi

Exit mobile version