Site icon ETHIO12.COM

አውሮፓ ሕብረት – ማዕቀብ ለመጣል ተሰብስቦ ሳይስማማ ተበተነ፤ የሚዛናዊነት ጥያቄ ተነስቷል

በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ ለመጣል የተሰበሰበው የአውሮፓ ህብረት ሰብሰባውን ያለ ስምምነት ማጠናቀቁ ታውቋል። ከስብሰባው በሁዋላ ጆሴፕ ቦሬል ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ በኢትዮጵያ ላይ ህብረቱ ሊጥል የነበረውን ማእቀብ በህብረቱ ሀገራት መካከል ስምምነት መድረስ ባለመቻሉ ስብሰባው ያለውሳኔ እንደተጠናቀቀ ይፋ አድርገዋል።

የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በኢትዮጵያ ላይ የማዕቀብ ውሳኔ ለመወሰን ስብሰባ ከማድረጋቸው በፊት ውሳኔው በማዕቀብ እንዲቋጭ ጫና የሚያደርጉ እንቅስቃሴዎች በተደራጀ መልኩ ሲደረጉ ነበር።

የኢትዮጵያ መንግስት በሁሉም ግንባር በአየር ድሮንና ጀት፣ በከባድ መሳሪያና በመላው እግረኛ ሰራዊቱን ማሰማራቱን የትህነግ አመራሮች ታላላቅ ለሚባሉት ሚዲያዎች እንዲያስታውቁ ተደርጓል። የድረሱልን ጥሪ ቀርቧል።

የዓለም የጤና ድርጅት ዳይሬክተር ቴዎድሮስ አደሃኖም በትግራይ የኢትዮጵያ መንግስት እርዳታ እንዳይደርስ ማድረጉን በስፋት በማስተጋባት፣ ህዝብ እያለቀ ስለሆነ ድረሱልን በማለት ሃላፊነታቸውን ተገን በማድረግ ውተውተዋል። ሚዲያም ይህን ሲያሰራጭ ቆይቷል።

እሳቸው ይህ ካሉ በሁዋላ በመቀሌ የህክምና ሙያተኞችና ሰራተኞች ሰልፍ አድርገው የትግራይ ህዝብ በመድሃኒና በምግብ እጥረት አደጋ ላይ መውደቁን በመጥቀስ ድምጻቸውን እንዲያሰሙ ተደርጓል። ዛሬ ስብሰባው ከመጀመሩ ቀደም ብሎ “በአውሮኘላን ተደበደብን” በሚል የተሳሳተ ፎቶና የቆየ ማስረጃ በማውጣት ሰላማዊ ዜጎች ኢላማ መደረጋቸውን አስትውቀዋል። በተመሳሳይ ሚዲያዎች ይህንኑ ዜና ተቀባብለው አየር ላይ አውለዋል። ይሁን እንጂ መንግስት አስተባብሏል።

አቶ ጌታቸው ረዳ በቲውተር ገጻቸው የአየር ድብደባ መፈጸሙን በምሬትና መንግስት የተስፋ መቁረጥ ውስጥ እንዳለ በማመላከት እያስፈራሩ ጥቃት ያሉትን ገልጸዋል። በተመሳሳይ ትህነግ በውጫሌ ብቻ ከባድ መሳሪያ በመተኮስ ጨፈጨፈ ስለተባለው የንጹሃን ሞት ያሉት ነገር የለም። ጭፍራ ላይም ተመሳሳይ ግድያ መፈጸማቸውን የአፋር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ቢያስታውቅም ትህነግ ያለው ነገር የለም።

በአቶ ጌታቸው ቲዊት ስር “ጦርነት ውስጥ ገብቶ ሲገል ጀግና፣ ሲነካ ድረሱልኝ ማለት አስገራሚ ትወና ነው” ሲሉ በርካቶች በስድብና በቁጣ ምላሽ ሰጥተዋል። አያይዘውም በምስል የተደገፈ ” የድል ዜና” አኑረዋል። ቪኦኤ የአየር ጥቃት መካሄዱን አመልክቶ ጉዳት እንደደረሰ ቀድሞ ዘግቧል። ይሁን እንጂ በደቡብ ወሎ ሰሞኑንን እያለቀ ስላለው ሕዝብ በሚገባው ደረጃ አልዘገበም።

ሁሉም ሆኖ የአውሮፓ ህብረት ኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ ለመጣልና የአሜሪካ ሎሌነቱን ለማጽናት ባካሄደው ስብሰባ የሚዛናዊነት ጥያቄ መነሳቱ ታውቋል። ህወሃት በአማራና በአፋር ክልል መጠነ ሰፊ ኢሰብአዊ ድርጊት እየፈፀመ ባለበት ወቅትን አንድን ወገን መደገፋ ተገቢ አለመሆኑና ማዕቀብ ማድረጉ ደግሞ የባሰ ችግር እንጅ መፍትሔ አያመጣም በሚሎ ወቅታዊውን ሁኔታና የትህነግ አቋም ከግምት በማስገባት ውሳኔው ሳይወሰን ቀርቷል።

በሉክዘመበርግ በተካሄደው ስብሰባ ተቀነባብሮ እየቀረበ ያለው ድራማ ያላሳመናቸው አገራት ብዙ ስለነበሩ ያለውሳኔ ስብሰባቸውን አጠናቀዋል። ጆሴፕ ቦሬል ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ በኢትዮጵያ ላይ ህብረቱ ሊጥል የነበረውን ማእቀብ በህብረቱ ሀገራት መካከል ስምምነት መድረስ ባለመቻሉ ስብሰባው ያለውሳኔ መጠናቀቁን ገልፀዋል።

Exit mobile version