Site icon ETHIO12.COM

ህወሓት እና የእኔ ትውልድ

የእኔ ትውልድ (በደርግ ዘመን ተወልዶ በኢህአዴግ ዘመን የጎለመሰ) በብዙ መልኩ እድለኛ አይደለም እላለሁ። ህወሓት የተባለ ጊንጥ ሀገራችንን ገና ከማለዳው ሰቅዞ ይዟት ስለነበር በልጅነታችን የሕጻናትን ሳይሆን የአብዮት መፈክር እና የዘመቻ መዝሙር እየሰማን ነው ያደግነው።

የልጅነት እድሜያችን ተጠንፍፎ ወጣትነታችን ሲያቆጠቁጥ ጊንጦቹ መንግሥት ጥለው “መንግሥት” ሆኑ። በመንበሩ እንደተሰየሙም ግራ እና ቀኛችንን በውል ሳንለይ አፈር ፈጭተን ውኃ ተራጭተን አብረን ያደግን እህት ወንድሞቻችን ጋር በዘር የተተበተበ የእሾኽ አጥር አጥረው ለያዩን። በህወሓት መርዝ ለተነደፈው የእኔ ትውልድ ቋንቋችን መግባቢያ ጌጣችን መሆኑ ቀርቶ እንደ ሰናኦር ሰዎች የጠብ እና የመለያየት ምክንያት ሆኗል።

የዩኒቨርሲቲ ቆይታችንም የተረጋጋ እና እንደቀደምቶቻችን የዕውቀት ማዕድ አልነበረም። ዲግሪያችንን ያገኘነው ግማሽ ትምህርት ግማሽ ዱላ ችለን ነበር። (በአንድ ወቅት ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ብጥብጥ ተነስቶ ለውይይት የመጣችው የትምህርት ሚንስትር የነበረችውን ገነት ዘውዴን አንድ ተማሪ “ክብርት ምኒስትር በየዓመቱ ፖሊስ ካምፓሳችን ድረስ እየገባ ይቀጠቅጠናል። ወይ አንደኛችንን በኮርስ መልክ እንውሰደውና ግሬድም ይለጠፍልን” ብሎ በስላቅ ጠይቋት ነበር) የእኔ ትውልድ ትምህርት ቀልሎት ዱላ ከብዶት ነው የተመረቀው።

ትኩሶቹ ተመራቂዎች ሀገር እና ወገን በምናገለግልበት አፍላ ዘመናችን እንደቀደምቶቻችን በገዛ ሀገራችን ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ፤ ከሰሜን እስከ ደቡብ ተንቀሳቅሰን በመረጥነው ቦታ ለመሥራት፣ ሀብት ለማፍራት እና ለመኖር የተፈቀደልን አልነበርንም። በገዛ ሀገራችን ባይተዋር ሆነን የምንኖር መጻተኞች እንጂ።

በጉልምስናችን ወራት በዕድሜያችንም እኩሌታ እነሆ የተስፋ ጭላንጭል ለማየት ዕድል ገጥሞን ነበር። በይሁዳ ፈርስ ላይ የበቀለው ህወሓት የተባለ ነቀርሳ ከኢትዮጵያችን ጫንቃ ላይ ተነቀለ። የጨነገፈ የመሰለን የልጅነት ህልማችን ሊለመልም ሆነ! በገዛ ሀገራችን መጻተኞች ሳንሆን ባለሀገር እና ባለወገን መሆናችንን ዐየን። በአባቶቻችን ታሪክ በወላጆቻችን ትረካ ወደምናውቃት ሁሉን በእኩል ወደምታቅፍ ኢትዮጵያ ጎጆአችን መሰባሰብ ጀመርን። ግና የሀገራችን የተስፋ ወጋገን ጎሁ ገና ከመቅደዱ ወደቀ የተባለው ህወሓት የተባለ መርዛም እሾኽ ጉቶው ማቆጥቆጥ ጀምሮ ነበር። ልትነጋ የነበረችውን የሀገሬ የንጋት ጀምበር ጥቁር ደመና ጋረዳት።

ዛሬ የእኔ ትውልድ ትንቅንቅ ላይ ነው። የልጅነት ሕልማችችን፣ የወጣትነት ተስፋችን፣ የጉልምስና ወዛችንን የቀማን ጨካኝ ሥርዓት የሽምግልና ትዝታችንን ሊነጥቀን ጦር ሰብቆ ዘገር ነቅንቆ እንደገና አፈር ልሶ ተነስቷል። በጸሎትም በትግልም የተገላገልነው የመሰለን ጠላታችን እንደ አጥፍቶ ጠፊ የመጨረሻ ሙከራውን ለማድረግ ያለየሌለ ኃይሉን አሰባስቦ ኢትዮጵያን ጉሮሮ ለማነቅ እየተንደረደረ ነው።

ሕወሓት እንደ ድሮው ሀገር ለማስተዳደር እንደማይጓጓ ግልጽ አድርጎልናል። ነገር ግን የተፈጥሮ ሞቱን ከመሞቱ በፊት የተፈጠረበትን ዓላማ ለማሳካት ለመጨረሻ ጊዜ እየሞከረ ነው። “ጥንተ ጠላቴ ነው” የሚለውን የአማራ ህዝብን አዋርዶ ማጥፋት እና ኢትዮጵያን በትኖ ከዓለም ካርታ ላይ መደምሰስ።

ስለዚህ ለኢትዮጵያውያን የቀረበልን ጥያቄ ብዙ እና ውስብስብ አይደለም። የኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምን ንግግር ልዋስ እና “ምርጫችን አንድ ነው! ይጥፉ ወይንስ እንጥፋ !”

ምርጫው የራሳችን ነው።

Yohannes Mekonnen – ዮሐንስ መኮንን

Exit mobile version