Site icon ETHIO12.COM

የተፈናቃዮች እጣ ፋንታና ስር የሰደደው ዘረኝነት

« ኦነግ ሸኔ ንጹሃንን በዘር ማንነታቸው እየለየ ሲገድልና ሲያፈናቅል ሰዎቹን ለማዳን የሞከሩ ኦሮሞዎችም ከግድያው አላመለጡም፡፡ በሩዋንዳ .. 1994 በነበረው የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ አንተባበርም ያሉ ወይም ቱትሲዎች በቤታቸው ሸሽ ገው የተገኙ ሁቱዎች አሁን በወለጋ እንደተደረገው ይገደሉ ነበር »

ፍቱን ታደሰ

አቶ ፍቱን ታደሰ

የትግራይ ወራሪ ኃይል ኢትዮጵያን ማፍረስ ግቡ ያደረገ ጦርነት ከከፈተበት ከጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ዜጎቻችን ከመኖሪያ አካባቢያቸው ተፈናቅለዋል፡፡ በተለይ ወያኔ በአማራና በአፋር ክልሎች ባካሄደው ወረራ ከመኖሪያቸው የተፈናቀሉ ዜጎች ቁጥር ከ3 ሚሊዮን በላይ መድረሱን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

የሰሜኑ ጦርነት ከመጀመሩ አስቀድሞም ከወለጋና ከቤንሻንጉል ክልሎች በጽንፈኛ ኃይሎች በማንነታቸው ምክንያት ከመኖሪያ ቀዬአቸው የተፈናቀሉት ኢትዮጵያውያን ቁጥር ከአንድ ሚሊያን መብለጡን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

በተለይ ወለጋ ውስጥ የአማራ ብሔር ተወላጆችን መግደሉና ማፈናቀሉ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ በህዳር ወር አጋማሽ አካባቢ በምስራቅ ወለጋ አኖ እና ስሬ በሚባሉ ቀበሌዎች ውስጥ የሚኖሩ አማራዎች ላይ የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት በመቶዎች የሚቆጠሩ ንጹሃን ሲገደሉ በወቅቱ ሸሽተው ህይወታቸውን ለማትረፍ የቻሉትም 52 ሰዎች እንደምንም አዲስ አበባ ደርሰው አስኮ አካባቢ በጊዜያዊ መጠለያ ውስጥ ይገኛሉ፡፡

ኦነግ ሸኔ ንጹሃንን በዘር ማንነታቸው እየለየ ሲገድልና ሲያፈናቅል ሰዎቹን ለማዳን የሞከሩ ኦሮሞዎችም ከግድያው አላመለጡም፡፡ በሩዋንዳ እ.ኤ.አ በ1994 በነበረው የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ አንተባበርም ያሉ ወይም ቱትሲዎች በቤታቸው ሸሽ ገው የተገኙ ሁቱዎች አሁን በወለጋ እንደተደረገው ይገደሉ ነበር፡፡

ከወለጋም ሆነ ከቤንሻንጉል የሚፈናቀሉት ዜጎች እንዲፈናቀሉ የተደረጉት ተወልደው ካደጉበት ቦታ ነው፡፡ ወላጆቻቸው በአንድ ወቅት በሰፈራም ይሁን የተሻለ ሥራና ኑሮ ፍለጋ ወደ ወለጋ ወይም ቤንሻንጉል ሄደው ያፈሩት ቤተሰብ ውጤት ናቸው፡፡ ያ አካባቢ ለእነሱ የትውልድ ቦታቸው ነው፡፡ ሌላ የሚያውቁት አካባቢም ሆነ ማህበረሰብ የለም፡፡ በተለይ ወለጋ ውስጥ ተወልደው ያደጉት በቋንቋም ሆነ በባህል ከማህበረሰቡ ጋር ተዋህደዋል፡፡

ዛሬ ግን ጸጉረ ልውጥ ተብለው ተገድለዋል፤ የተረፉትም ቤት ንብረታቸውን ትተው እንዲፈናቀሉ ተደርገዋል፡፡ ይህ ላለፉት ሰላሳ አመታት በሃገራችን ስር እንዲሰድ የተደረገው የዘረኝነት ፖለቲካ ውጤት ነው፡፡

ወያኔ በአማራና በአፋር ክልሎች ላይ በፈጸመው ወረራ ምክንያት ወደ አጎራባች ወረዳዎችም ይሁን ወደ መሃል ሃገር የተፈናቀሉ ዜጎች ወረራው ተቀልብሶ አካባቢው ሙሉ በሙሉ ነጻ ሲሆን ወደ ቀዬአቸው ይመለሳሉ፡፡

በርግጥ ልክ ባጣ ዘረኝነት የታወሩት የትግራይ ወራሪዎች በቁጥጥራቸው ስር የቆዩትን አካባቢዎች መሠረተ ልማት በማውደምና በመዝረፍ እንዲሁም የግለሰቦችን ቤት ሳይቀር ንብረታቸውን በመዝረፍና ለመውሰድ ያልቻሉትን ደግሞ በማፈራረስና በማቃጠል ከፍተኛ ውድመት አድርሰዋል፡፡ ከብቶችን ሳይቀር በጥይት ጨፍጭፈዋል፡፡

ይህ ሁሉ ጥፋትና ውድመት ቢደርስም የተፈናቀሉትን ዜጎች ወደ ቀዬአቸው እንዳይመለሱ የሚያደርግ ሁኔታ የለም፡፡ በህዝብና በመንግስት ድጋፍ ተፈናቃዩቹ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ንብረታቸው እንዲተካላቸው ከተደረገ በተለይ አርሶ አደሩ የእርሻ በሬዎች እና የግብርና ግብአት ካገኘ ወደ ቀደመው ህይወቱ ለመመለስ ጊዜ አይወስድበትም፡፡ በአማራና በአፋር ክልል ተፈናቃዮችን ወደ ቀዬአቸው መልሶ ማቋቋሙ በወለጋና በቤንሻንጉል እንዳለው ሁኔታ አስቸጋሪ አይደለም፡፡

ከወለጋና ከቤንሻንጉል የተፈናቀሉት ዜጎች ግን ተመለሱ ቢባሉ እንኳን ለህይወታቸው ዋስትና ይፈልጋሉ፡፡ ምክንያቱም ገዳዮቻቸው በማንኛውም ሰአት ተመልሰው ለማጥቃት መንቀሳቀሳቸው አይቀርም፡፡ ይህንን ሁኔታ ሊያስቀር የሚችል ማህበረሰብ አቀፍ ውይይትና መግባባት እንዲሁም ጠንካራ የህግ ማዕቀፍ ያስፈልጋል

በወለጋ ዜጎች በማንነታቸው ምክንያት እንዲፈናቀሉ የተደረገው በጽንፈኛ ቡድኖች ታቅዶ በሚፈጸም “ዘር ማፅዳት“ በተሰኘ የናዚ አይነት ተልዕኮ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ህወሓት ስልጣን ከያዘበት ጌዜ ጀምሮ አላማና ግብ አሰቀምጦለት ሲያስፈጽመው የነበረ እኩይ ድርጊት ነው፡፡ የአማራንና የኦሮሞን ብሔረሰቦች ለማጋጨት ከተጠቀመባቸው ሰይጣናዊ መንገዶች አንዱ የሃሰት ታሪክ መፍጠር ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ኦሮሞ ክልል ውስጥ የሞኖሩ የአማራ ብሔር ተወላጆችን እራሱ በሚመራቸው የኦሮሞ ታጣቂዎች የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ (Genocide) እንዲፈጸምባቸው አድርጓል፡፡ ከ1984 ዓ.ም በምስራቅ ሐረርጌ በበደኖ፣ በወተር፣ በአርባጉጉ የተጀመረው የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ ዛሬ ድረስ በወለጋና በቤንሻንጉል ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

እንዲህ ስር የሰደደው ዘረኝነት የሚለወጥበት የተጠና የፖለቲካ ሥራ እስካልተሰራ የወለጋና የቤንሻንጉል ተፈናቃዮችን ወደ ቀዬአቸው ለመመለስ መሞከር ህዝቡን ለእልቂት መዳረግ ይሆናል፡፡ ሰሞኑን በመንግስት የታቀደው ብሔራዊ መግባባት ተግባራዊነቱ ከእነዚህ አካባቢዎች ቢጀምር በአስከፊ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙት የወለጋና የቤንሻንጉል ተፈናቃዮች በቅድሚያ መፍትሄ ሊያገኙ ይችላሉ፡፡

shorturl.at/fnvC9

Exit mobile version