ETHIO12.COM

የ.ተ.መ.ድ የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት የጠራው ልዩ ስብሰባ እንዲመክን ኢትዮጵያ ተጣራች፤ “ስብሰባው ዓላማው ሌላ ነው”

“ሁልጊዜ የግንባሩ ዜናና የሃይል ሚዛን ሲቀየር ለኢትዮጵያ ይደገስላታል” በሚለው ሃሳብ ጉዳዩን የሚከታተሉ ሁሉ ይስማማሉ። ከፈጠራ ዜና ጀምሮ እውነታውን አጣሞ በማቅረብ የተካኑት የውጭ ሚዲያዎች ይህንኑ ድግስ በብረሃን ፍጥነት ያራቡታል። የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት በኢትዮጵያ ጉዳይ የተራው ስብሰባ የዚሁ የድግሱ አካል እንደሆነ ኢትዮጵያ ወዲያው አስታውቃለች። “አምክኑልኝ” ስትል ፍትህ ወዳድ ወዳጆቿንና አገራትን ጠይቃለች።

የአውሮጳ ህብረት ለምክር ቤቱ ፕሬዝዳንት ላከ በተባለ ደብዳቤ መነሻ የመንግስታቱ ድርጅት የሰብአዊ መብት ጉባኤ መጠራቱ ይፋ ሆኗል። ይፋ በሆነው ዜና እንደተመለከተው አውሮፓ ሕብረት፣ የችግሩን አካል ሳይጠቅስ የአገሪቱ ፓርላማ ” አሸባሪ” ያለውን ትህነግን ሳይከስ ጦርነቱ አስከፊ የሰብአዊ ቀውስ እያስከተለ፣ በሺህ እያፈናቀለ፣ የበርካቶችን ህይወት እየቀጠፈ በመሆኑ በፍጥነት እንዲፈታ አሳስቧል።

በአማራና በአፋር የደረሰውን የመሰረተ ልማቶች ውድመት፣ የጅምላ ጭፍጨፋ፣ አስገድዶ መድፈርና ዘርፊያ በገሃድ እያዩ ምንም ያልተነፈሱት የአውሮፓ ሕብረትና የተመድ የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ይህንን ስብሰባው እንዲካሄድ የወጠኑት ሴራ ፖለቲካዊ ስለመሆኑ አመላካች እንደሆነ በግልጽ የሚያሳብቅ እንደሆነ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አመልክቷል።

“አዲስ አበባ ልትያዝ ተከባለች” በሚል በሰላሟ ከተማ ላይ “የገሃነብ አዋጅ” የተባለውን ” የጥላችሁ ውጡ” ጥሪ በገሃድም በድብቅም እያሰራጨች ያለችው አሜሪካ “ያልተረጋገጠ” ስትል በንጹሃን ደምና ህይወት፣ በወደመው ንብረትና በጭፍጨፋው አማካይነት ወላጅ አልባ በሆኑ ከ50 ሺህ በላይ ህጻናት ላይ የተሳለቀ መግለጫ በሰጠችበት ቅጽበት ስብሰባው እንደሚካሄድ መሰማቱ ሴራውን ይበልጥ ግልጽ የሚያደርገው እንደሆነ እየተነገረ ነው።

አውሮፓ ህብረት “ባስቸኳይ እንዲቆም” ሲል ባቀረበው ጥሪ መነሻ የሚካሄደውን ስብሰባ ቀድማ “በአማራና አፋር ክልሎች በትግራይ ሃይሎች ተፈፅመዋል የተባሉ የሰብዓዊ መብትጭፍለቃ፣ የመሠረተ ልማት ማውደም፣ አሳስቦኛል” ስትል ነጻ የወጡ አካባቢዎች የሆነው ሁሉ ይፋ መሆን ከጀመረ ከሁለት ሳምንት በላይ ቆይታ አስታውቃለች።

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ቃል አቀባይ ኔድ ኘራይስ እሁድ ባሰራጩት መግለጫ “በአማራና በአፋር ክልሎች በትግራይ ኀይሎች ተፈፅመዋል የተባሉ የሰብአዊ መብት ረገጣ ግፍና የንፁሐን መሠረተ ልማቶች መውደምን የሚገልጹ ያልተረጋገጡ ሪፖርቶች ዩናይትድስቴትስን በእጅጉ አሳስቧታል” ሲሉ ዓለም በገሃድ ወደ ዓመድነት የተቀየረ ከተማ፣ የተዘረፈና የወደመ መሰረተ ልማት፣ ትምህርት ቤቶችና የጤና ተቋማት፣ የተደፈሩ እናቶችና ህጻናት፣ የጅምላ መቃብር፣ የጅምላ ጭፍጨፋ እየቀረበለት፣ ተበዳዮች በአካል እየመሰከሩ፣ የሰው ልጅ ሲቃጠል የሚያሳይ የቪዲዮና የሰው ማስረጃ እየቀረበ፣ አሜሪካ ” ያልተረጋገጠ” ስትል ስጋቷን የገለጸችው በስብሰባው ላይ ” ዝም አላልኩም” በሚል የንግግር ማድመቂያ ለማመቻቸት እንደሆነ ከወዲሁ ተመልክቷል።

– የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ቃል አቀባይ ኔድ ኘራይስ በተለዩ ወቅቶች ያሰራጩትን ቲውተር በማጣቀስ ትችት እየተሰነዘረ ነው። “ይህ ሁሉ ጉድ ተፈጽሞ “ያልተረጋገጠ” መባሉ አካሄዱን ከወዲሁ አመላክቷል

ከክልሉ በመውጣት አማራና አፋር ክልል ገብቶ አገር ያወደመ የትግሬ ወራሪ ሃይል፣ የሰራውን ሁሉ እንደ ጽድቅ በመቁጠር ኢትዮጵያን አስመልክቶ የተጠራው ስብሰባ ለዚህ ይመስላል ኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ይዘት እንዳለው ያስታወቀችው።

በኢትዮጵያ አስተባባሪነት የተጀመረው የፓን አፍሪካኒዝም ንቅናቄና ” የበቃ” ማዕበል ያላስደሰታቸው፣ ቀደም ሲል በቀይ ባህር ፖለቲካ ኢትዮጵያ ዳግም መመለሷ ያበሳጫቸው ምዕራባዊያንና አሜሪካ ኢትዮጵያን ለማክሰም በገሃድ ዘመቻ ላይ መሆናቸው፣ ለዚህም ዘመቻቸው ቅርብ ሆኖ የተገኘው አለንጋ ትህነግ መሆኑንን በመግለጽ ቀደመው አስተያት የሰጡ ” አገራቱ የትህነግ ወይም የትግሬ ፍቅርና ክብር ይዟቸው ሳይሆን፣ ኢትዮጵያን ለመበተንና አቅም አልባ ለማድረግ መጋለቢያ ሲፈልጉ ያገኙት ፈረስ ትህነግ ስለሆነ ነው። ትህነግ ኢትዮጵያ ቢል ኖሮ እስከ አሁን ልሳኑንን ዘገተው ታሪክ ያደርጉት ነበር። አሁን በተቃራኒው ትህነግ ላይ ሲከርበትና ህልውናው አደጋ ላይ ሲወድቅ የሚሯሯጡት ለዚህ ነው” ማለታቸውን የተለያዩ መረጃዎች ይመስከራሉ።

የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር፣ ትህነግ በወታደራዊ ስሌት አቋሙ ወደ መጨረሻው መሆኑ ይፋ እየሆነ ባለበት ቅጽበት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ  መብቶች ምክር ቤት በኢትዮጵያ  ጉዳይ ላይ የጠራው ልዩ ስብሰባ ፖለቲካዊ ፍላጎት ያለው ነው ሲል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በገሃድ የተቃወመበትና “የምክር ቤቱ አባላት የተጠራውን ስብሰባ ውድቅ እንዲያደርጉ” ሲል የጠየቀውም በዚሁ መነሻ እንደሚሆን በርካቶች ያምናሉ። ሰላም እንዲወርድ ቢፈግሉም አካሄዱን አይቀበሉትም።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት በኢትዮጵያ ጉዳይ የጠራው ስብሰባ ድርጅቱና የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ያደረጉት የጣምራ ምርምራና መንግስት የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩ እያደረገ ያለውን ጥረት የገፋ መሆኑን እንደሆነ ተመልክቷል። በጥምር ሪፖርቱ የቀረቡ ምክር ሀሳቦችን መንግስት ተቀብሎ የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑንም መግለጫው አስታውሷል።

ይህ ባለበት ሁኔታ በምክር ቤቱ የተጠራው ልዩ ስብሰባ ፍላጎት ፖለቲካዊ ዓላማ ለማሳካት እንደሆነ በግልጽ መረዳት እንደሚቻል መግለጫው አስገንዝቧል። አንዳንድ አገራት ምክር ቤቱን ለራሳቸው የፖለቲካ አጀንዳ ማስፈጸሚያ አድርገው መጠቀማቸው ኢትዮጵያን እንዳሳዘናት ሚኒስቴሩ ገልጿል።

ምክር ቤቱን አሸባሪው የሕወሓት ቡድን በአማራ እና አፋር ክልሎች የፈፀማቸውን አስከፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ላይ ምርምራ ማድረግ ሲጠበቅበት በተወሰኑ አገራት የፖለቲካ ፍላጎት ምክንያት ያን አለማድረጉን አስታውቋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት ይህን ያልተገባ አካሄዱን በአስቸኳይ ማቆም እንዳለበት አመልክቷል።

የምክር ቤቱ አባል አገራትም ይህንን የተወሰኑ አገራትን የፖለቲካ አላማ ለማስፈጸም የተጠራውን ልዩ ስብሰባና ውጤቱን በመቃወም ውድቅ እንዲያደርጉት የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥሪ አቅርቧል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ሕግን ባከበረ መልኩ አሁንም የዜጎች ሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩና እንዲጠበቁ በቁርጠኝነት እንደምትሰራ የምክር ቤቱ አባላት ልታረጋግጥ ትወዳለች ብሏል ሚኒስቴሩ በመግለጫው።

ኢትዮጵያ በግልጽ በአማራና በአፋር ክልል የደረሰውን ቀውስ የውጭ መገናኛዎች ግብተው እንዲዘግቡ፣ እንዲመረምሩ በግልጽ ጥያቄና ግብዣ ብታቀርብም ተመድ እስካሁን ያለው ነገር የለም። አንዳንድ ሚዲያዎችም ቢሆኑ ሲዘግቡት ከማይገናኝ ጉዳይ ጋር እያላተሙ ሲሆን ሂውማን ራይትስ ዎች በውስን ቦታም ቢሆን የተሻለ ሪፖርት ይፋ አድርጓል። እንግዲህ አሜሪካ ይህን ወንጀል ነው ” ያልተረጋጠ ” ስትል የገለጸችው።

Exit mobile version