Site icon ETHIO12.COM

የዋሽንግተንና አካበቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የጆ ባይደን አስተዳደርን በመቃወም ለሴናተር ክሪስ ኩንስ ደብዳቤ ልከዋል

የዋሽንግተን እና አካበቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የፕሬዝዳንት ጆ ባይደን አስተዳደር በኢትዮጵያ ላይ እየተከተለ ያለውን ፓሊሲና አካሄድ በመቃወም ለአሜሪካው ሴናተር ክሪስ ኩንስ ደብዳቤ ልከዋል

👉 ሴናተሩ የኢትዮጵያን እውነት እንዲረዱ፤ የህወሓትን የቀደመ ታሪክና የአሁኑን የውሸት ትርክቱን እንዲያጤኑና ከኢትዮጵያ ጎን እንዲቆሙ በሀገር ሥብከቱ ስም ጠይቀዋል‼️

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክረስቲያን የዋሽንግተን እና አካበቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብጹእ አቡነ ፋኑኤል የፕሬዝዳንት ጆ ባይደን አስተዳደር በኢትዮጵያ ላይ እየተከተለ ያለውን ፓሊሲና አካሄድ በመቃወም ለአሜሪካው ሴናተር ክሪስ ኩንስ ደብዳቤ ጽፈዋል።

ሊቀ ጳጳሱ በዚሁ ደብዳቤያቸው የፕሬዝዳንት ባይደን አስተዳደር እየተከተለ ያለው ፓሊሲ፤ ፍጹም በተሳሳተ መረጃ ላይ የተመሰረተ እና የአሜሪካን እና የአፍሪካ ቀንድ አገራትን ግንኙነት የሚጎዳ፤ የአሜሪካን ጥቅምም የማያስጠብቅ ነው ብለዋል።

ኢትዮጵያዊያን ላለፉት 27 አመታት በላያቸው ላይ ተጭኖ የኖረውንና የህወሓት የበላይነት የነበረበትን አገዛዝ በህዝባዊ ተቃውሞ በማስገደድ መለወጣቸውን እና አገራዊ ለውጥ መጀመሩን ያብራሩት ብጹእ አቡነ ፋኑኤል፤ ለውጡ ለትግራይ ህዝብ እንዳይደርስ፤ ወደኋላም እንዲቀለበስ ህወሓት ወደመቀሌ በመግባት ያካሄዳቸውን ሴራዎች ዘርዝረው አስረድተዋል።

የፌዴራል መንግስት ይህንን ችግር ሠላማዊ በሆነ መንገድ ለመፍታት የተለያዩ በርካታ ጥረቶችን ማደረጉን አስታውሰው፤ በዋናነትም የሀይማኖት አባቶች፣ ታዋቂ ግለሰቦች እና እናቶችን ሳይቀር ወደመቀሌ በመላክ የተደረጉ የሰላም መንገዶችን በአብነት በማንሳት ሁሉም በህወሓት እንቢተኝነት ሳይሳካ መቅረቱን አብራርተዋል።

በአንጻሩ ህወሓት ወታደራዊ ስልጠናዎችን በስፋት ሲያካሂድ መቆየቱን፣ ለጦርነት ሰፊ ዝግጅት ማድረግ መቀጠሉን አስታውሰው፤ በኮሮና ምክንያት ምርጫ ሲራዘም ህወሓት በእንቢተኝነት ከፌዴራል መንግስት እውቅና ውጭ ምርጫ አካሂዶ ሲያበቃ በግልጽ የፌዴራል መንግስትን አላውቅም ብሎ ማወጁን አስረድተዋል።

በዚህ አይነቱ ህገ ወጥ መንገድ የተጓዘው ህወሓት ጥቅምት 24/2013 የሠሜን ዕዝ ላይ ጥቃት በመፈጸም ከትግራይ ተወላጆች ውጭ ያሉ የሠራዊቱን አባላት ያለምንም ምህረት ጨፍጭፎ ጦርነቱን ጅምሯል ያሉት አቡነ ፋኑኤል፤ ህወሓት በዚህ ሳያበቃ በአማራ እና በአፋር ክልል ወረራ በመፈጸም ንጹሀንን መጨፍጨፉን የማይካድራውን፣ የጋሊኮማውን እና የጭናውን ጭፍጨፋ በአብነት በማንሳት የቡድኑን ወንጀል አብራርተዋል።

ይህንን ሁሉ ወንጀል የፈጸመው ህወሓት ላይ አንድም እርምጃ ያልወሰደው የባይደን አስተዳደር በተቃራኒው ኢትዮጵያን ከአግዋ ለማስወጣት በመወሰን ደሃዎች ላይ የቅጣት በትሩን አሳርፏል ያሉት አቡነ ፋኑኤል፤ በውጭ አገራት ከፍተኛ ሀብት ያላቸውን እና ጦርነቱን በገንዘብ እየደገፉ ያሉትን የቡድኑን ሰዎች በዝምታ ማለፉን ተገቢነት የጎደለው መሆኑን በመጥቀስ አብራርተዋል።

አቡነ ፋኑኤል በዚሁ ዳቤያቸው ሴናተሩ የኢትዮጵያን እውነት እንዲረዱ፤ የህወሓትን የቀደመ ታሪክና የአሁኑን የውሸት ትርክቱን እንዲያጤኑና ከኢትዮጵያ ጎን እንዲቆሙ በሀገር ሥብከቱ ስም ጠይቀዋል። Via (ኢ.ፕ.ድ)

Exit mobile version