Site icon ETHIO12.COM

መንግስት ትግራይን ሊቆጣጠር እንደሚችል ህግን ተንተርሶ ይፋ አደረገ፤ አሜሪካ የተድበሰበሰ መግለጫ ሰጠች

“አሸባሪው ሃይል” አሉ ሬድዋን ሁሴን፣ ” አሸባሪው ሃይል በሚሸሽባቸው እያንዳንዱ የትግራይ መንደሮች እግር በእግር በመከተታል የመግባት ፍላጎት የለንም” ሲሉ በተዘዋዋሪ የቀድሞው የየዋህነት ስህተት እንደማይደግም አመላከቱ። ቀጠሉና “የኢትዮጵያን የግዛት አንድነትን ማስጠበቅ የመንግስት ኃላፊነት እንደመሆኑ መጠን፣ ትግራይን ጨምሮ በማንኛውም ሀገሪቱ አካባቢዎች ሰራዊቱን የማስፈር መብት አለን” ሲሉ በስልጣን ህግ ጠቅሰው አስረዱ። ይህን ያሉት ተቀማጭነታቸው አዲስ አበባ የሆኑ ዲፕሎማቶችና አምባሳደሮችን ሰብስበው ነው።

የአሜሪካንን የሽብር አዋጅ ሰምተው አገር ለቀው የወጡ ዲፕሎአማቶችና አምባሳደሮችን “ስትወጡ መግለጫ አውጥታችሁ በአዋጅ እንደወታችሁ፣ በአዋጅ በገሃድ መመለሳችሁን እያስታወቃችሁ ግቡ” ሲል ቆፍጣና የአጻፋ መመሪያ የሰጠው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ የአውሮፓ፣ አሜሪካ፣ ኤስያ እና መካከለኛው ምስራቅ ሀገራት አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶችን ሰብስቦ በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ማብራሪያ ሲሰጥ ሚኒስትር ዳኤታው አቶ ሬድዋን መነሳት ያለባቸውን ጉዳዮች አንስተዋል።

“የዓለም ዋናዎቹ” የሚባሉት አገራት፣ እነሱው “የሚነዱት” የሚባለው የተባበሩት መንግስታትና የነሱ “ድምጽና ፍላጎት አስፈጻሚ” የሚባሉት መገናኛዎች በመናበብ ትህነግ ጻፈው የሚባለውን ደብዳቤ እያጎሉ ባለበት፣ ትህነግ “ተገብቶላታል” የተባለውን ቃል እንዲከበርለት ጣላቅ ገብነትን በሚጠይቅበት በአሁኑ ሰዓት መንግስት ትግራይ ወታደር ማስፈር የመንግስትነት አንዱ ስራው መሆኑንን ለተሰብሳቢዎቹ አስረድቷል። የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ውሳኔም ፖለቲካዊ አጀንዳ ማራመጃ በመሆኑ ኢትዮጵያ ምድር ላይ ሊተገበር እንደማይችል በግልጽ ቋንቋ አስታውቋል።

“የፖለቲካ ፍላጎት ባላቸው አካላት ገፊነትና አስተባባሪነት የተላለፈው የተመድ የሰብአዊ መብት ምክር ቤት ውሳኔ በኢትዮጵያ ምድር ተፈፃሚ አይሆንም” ሲሉ እንቅጩን የተናገሩት አቶ ሬዲዋን ከህግና ደንብ ውጪ የሚደረጉ አካሄዶችን በሙሉ ኢትዮጵያ እንደማትቀበል አመልክተዋል።

አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን የፖለቲካ ፍላጎትን መሠረት አድርጎ በቅርቡ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብት ምክር ቤት ያሳለፈውን ውሳኔ ኢትዮጵያ እንደማትቀበል ተናግረዋል። ኢትዮጵያን አግባብነት ካላቸው ተቋማት ጋር ትብብር ስታደርግ መቆየቷን አንስተዋል።የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በመመርመር ተግባራዊ ማስተካከያዎችን ለመውሰድ የሚያስችል ተቋማዊ አቅም እንዳላትም ጠቅሰዋል። ቀደም ሲል የተመድ የሰብዓዊ መብት ተቋም እና የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ባደረጉት የጋራ ምርመራ የተሰጡትን ምክረ ሀሳቦችን ለመተግበር ኢትየጵያ ተግባራዊ አንቅስቃሴ በማድረግ ላይ በምትገኝበት ጊዜ የተላለፈ ውሳኔ መሆኑንም ገልጸዋል።

ም/ቤቱ የሽብር ቡድኑ በወረራ በቆየባቸው የአማራ እና አፋር አካባቢዎች የፈጸማቸውን መጠነ ሰፊ ሰብአዊ እና ቁሳዊ ጥፋት በማውገዝ ምርመራ እንዲካሄድ ውሳኔ ቢያሰተላልፍ ኖሮ ተገቢና የሚያስመሰግነው እንደነበርም ገልጸዋል።

የህወሃት ቡድን የእርዳታ አቅርቦት ለማስተጓጎል የሚወስደው የእብሪት ተግባርን የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በቸልታ መመልከቱን ጠቅሰው፤ በመንግስት በኩል ግን የሰብዓዊ እርዳታ ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የሚቻለውን ሁሉ ማድረጉን አመልክተዋል።

መንግስት ለሰላም ሲባል የተናጠል የተኩስ አቁም ውሳኔ ያስተላለፈ ቢሆንም የሽብር ቡድኑ ግን ተመሳሳይ እርምጃ ለመወሰድ ፈቃደኛ ያልነበረ መሆኑን አስታውሰው፣ የአለም አቀፉ ማህበረሰብም የመንግስትን ውሳኔ በአዎንታዊነት በመመልከት በአንጻሩ ደግሞ በህወሃት የእብሪተዠት ተግባር እንዲገታ ጫና ባለማሳደሩ ችግሩን እንዳወሳሰበው ገልጸዋል።

የህወሃት በመንግስት የተወሰደውን የተናጠል የተኩስ አቁም ውሳኔ እንደመልካም አጋጣሚ በመውሰድ በአማራና አፋር የተለያዩ አካባቢዎች ላይ ወረራ በመፈፀም በንጹሃን ላይ ጭፍጨፋ መፈጸሙን፣ የመሰረተ ልማትና ሃይማኖታዊ ተቋማትን ማዉደሙን፣ ህፃናትንና ሴቶችን መድፈሩ ገልጸዋል። ይህም የህዝብ ቁጣን ቀስቅሶ በሰብዓዊ እርዳታ መስመሩን ለመዝጋት ያነሳሳበት ጊዜው እነደነበርም አስረድተዋል።

አምባሳደር ሬድዋን በማብራሪያቸው የህወሓት አሸባሪ ሀይል በደረሰበት ምት ይዟቸው የነበሩ አብዛኛው የአፋር እና የአማራ አካባቢዎችን በማስለቀቅ በመንግሥት የፀጥታ ሀይሎች ቁጥጥር ስር እንደሚገኙ ገልፀዋል። ይህም ቡድኑ ለሰላም ሲል በወረራ ከያዝኳቸው አካባቢዎች ለቅቂያለሁ ማለቱ ከተጨባጩ እውነታ ጋር የሚቃረን ስለመሆኑም አንስተዋል።

ክቡር አምባሳደር ሬድዋን መንግስት ቡድኑ በሚሸሽባቸው እያንዳንዱ የትግራይ መንደሮች እግር በእግር በመከተታል የመግባት ፍላጎት የሌለው መሆኑን ጠቁመው፣ ነገር ግን ቡድኑ መቸውም ቢሆን መልሶ ጥቃት የማድረስ አቅሙ የተዳከመ መሆኑ ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

አክለውም የኢትዮጵያን የግዛት አንድነትን ማስጠበቅ የመንግስት ኃላፊነት እንደመሆኑ መጠን፣ ትግራይን ጨምሮ በማንኛውም ሀገሪቱ አካባቢዎች ሰራዊቱን የማስፈር መብት እንዳለው አመላክተዋል።

በቀጣይም በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም ለማስፈን ያለመ ሁሉን አካታች ዉይይት እንዲኖር ማንኛዉም በአገሪቱ ጉዳይ ይመለከተኛል የሚል አካል የሚሳተፍበ የህገ መንግስት ማሻሻያን ጨምሮ በሀገሪቱ ስምምነት ያልተደረሰባቸው ጉዳዮችን የተመለከቱ ጉዳዮች ለውይይት ክፍት እንደሚደረጉ መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

በተያያዘ ዜና ዩናይትድ ስቴትስ በኢትዮጵያ የሚካሄደውን ጦርነት ለማስቆም እንዲቻል ዲኘሎማሲያዊ ድጋፏን አጠናክራ እንደምትቀጥል በውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ቃል አቀባይዋ ኔድ ኘራይስ በኩል አስታውቃለች። ትህንግን እንደምትረዳ አቶ ጌታቸው ረዳ በግልጽ ምስክረነት የሰጡባትና ወደ አዲስ አበባ እንዲያቀኑ ያዘዘቻቸው እሷው እንደሆነች ማረገገጫ ያቀረቡባት አሜሪካ ” አዲስ አበባ ለተነድ ነው” በሚል በሽብር ተጋባር ተጠምዳ መቆየቷ አይዘነጋም።

ይሁን እንጂ የትህነግ ሃይል ተመቶና ከፍተኛ ሰብአዊ ቀውስ ደርሶበት በሃይል ከወረራቸው የአማራና የአፋር አካባቢዎች እንዲወጣ መደረጉን መንግስት ማስታወቁን ተከትሎ፣ ትህነግ ለሰላም ሲባል ሆን ብሎ ወደ ትግራይ ማፈግፈጉን ሲያስታውቅ “የኢትዮጵያ መንግሥት ተዓማኒነት ያለውና ሁሉንም ያሳተፈ ብሄራዊ ውይይት እንዲጀምር ጥሪ እናቀርባለን” ሲሉ ኔድ ፕራይስ ተናግረዋል። አስከትለውም ዩናይትድ ስቴትስ ጦርነቱ በአስቸኳይ እንዲቆም መጠየቋን እንደምትቀጥል አመልክተዋል። አገራቸው ሁሉን አቀፍ ብሔራዊ ውይይት ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲደረግ የተለመደውን ጥያቄ እንዳቅረበችም ገልጸዋል። ” ሁሉን አቀፍ” ሲሉ ግን ትህነግና ኦነግ ሸኔን ጨምሮ ስለመሆኑ በግልጽ አላስታወቁም።

መንግስት አመኤሪካ ስላለች ሳይሆን በኢትዮጵያ አተቃላይ መግባባትን የሚያሰፍን ሁሉንም ወገኖች ያካተተ ንግግር ለማድረግ ኮሚሽን አቋቁሞ እየሰራ መሆኑንን፣የማቋቋሚያ ረቂቅ ህጉን በይፋ ምክር እንዲደረግበት በበተኑ፣ ንግግሩ በሽብርተኛነት የተመደቡትን ሁለቱን ድርጅቶች እንደማይመለከት ምላሽ የተሰጠበት ሆኖ ሳለ አሜሪካ ምን አይነት ውይይት እንዲደረግ እንደምትሻ ግልጽ አላደረገችም። በአማራና በአፋር ክልል አገር ያወደሙና ዘር ያጠፉ፣ ከፈተኛ ወንጀል የፈጸሙ፣ በኦሮሚያ በተመሳሳይ በከፍተኛ ወንጀል የሚፍለጉና ንጽሃንን የጨፈጨፉ ናቸው የሚባሉት ሁሉ ይካተቱ ስለማለቷ በገሃድ አላስታወቀችም።


Exit mobile version