Site icon ETHIO12.COM

በሙስና ወንጀል የተከሰሱት ሁለቱ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኞች የክስ መቃወሚያቸውን አቀረቡ

ከዚህ በፊት በዐቃቤ ህግ ክስ ተመስርቶባቸው ክሱን ከደረሳቸው እና በችሎትም ከተነበበላቸው በኋላ ተከሳሾች በጠቦቆቻቸው አማካኝነት የጊዜ እጥረት ስለገጠመን የክስ መቃወሚያ አላቀረብንም በማለታቸው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የፀረ ሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎቱ ለታህሳስ 19/2014 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳለ።

በዚህ የክስ መዝገብ ዐቃቤ ህግ በከባድ የሙስና ወንጀል ክስ የመሰረተባቸው ተከሳሾች በቁጥር ሰባት ሲሆኑ 1ኛ ተከሳሽ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ዳኛ አዱኛ ነጋሳ 2ኛ ዳኛ አክሊሉ ዘሪሁን : 3ኛ ተከሳሽ ረቂቅ ዜናዊ፣ 4ኛ ረቡማ በለጠ፣ 5ኛ ቶፊቅ ሙላት 6ኛ ተከሳሽ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ሬጂስትራር ስሜነህ አለሙ እና 7ኛ የቦሌ ክ/ከ ወረዳ 06 ኗሪዎች መረጃና ማስረጃ አገልግሎት ባለሙያ ከድር ጁንዲ ናቸው።

ባለፈው ቀጠሮ የክስ መቃወሚያ እንዲያቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸው የነበሩት ሁለቱ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኞችና ሌሎች ሁለት ተከሳሾች ሲሆኑ በዛሬው ችሎት የክስ መቃወሚያ ማቅረብ የቻሉት ግን ሁለቱ የፍርድ ቤት ዳኞች ብቻ ናቸው፡፡ በዚህም መሰረት 1ኛ ተከሳሽ ባለ 2 ነጥብ፤ 2ኛ ተከሳሽ ደግሞ ባለ 5 ነጥብ ይዘት ያላቸውን የክስ መቃወሚያ ለፍርድ ቤቱ አቅርበዋል።

ሆኖም ፍርድ ቤቱ የክስ መቃወሚያ ያላቀረቡ ተከሳሾች እንዲያቀርቡና በዛሬው ችሎት መቃወሚያቸውን ያቀረቡት ሁለቱ ተከሳሾች ባቀረቡት የክስ መቃወሚያ ላይ ዐቃቤ ህግ መልስ እንዲሰጥበት ለታህሳስ 25/2014 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል።

5ኛ ተከሳሽ ቶፊቅ ሙላት ለግዳጅ ወደ ወልድያ አካባቢ መሄዳቸውንና 3ኛ ተከሳሽ ረቂቅ ዜናዊ ደግሞ ከአዲስ አበባ ወደ ዶሃ መሄዳቸውን ከኢምግሬሽን አገኘሁት ባለው መረጃ ፖሊስ ማስታወቁ የሚታወስ ሲሆን 7ኛ ተከሳሽ ደሞ የክስ መቃወሚያ የለኝም ስላሉ መከራከራቸውን እንዲቀጥሉ መወሰኑ ይታወቃል።

በዚሁ መዝገብ በባለፈው ቀጠሮ 1ኛ ተከሳሽ የሆኑት አዱኛ ነጋሳ የእኔና የባለቤቴ የባንክ አካውንት እንዳይንቀሳቀስ በመታገዱ ምክንያት ለልጆች የት/ቤት ክፍያ፣ የመብራትና የውሃ አንዲሁም የቤት ኪራይ ክፍያ ጭምር ለመክፈል ተቸግረናል ብለው አቤቱታቸውን ለችሎቱ ቢያቀርቡም ችግራቸው ስላልተፈታ በፍትህ ሚኒስትር የሃብት ማስመለስ ዳይሬክቶሬት በሁኔታው ላይ ቀርቦ እንዲያስረዳ ችሎቱ ትዕዛዝ በሰጠው መሰረት በፍትህ ሚኒስቴር የሃብት ማስመለስ ዳይሬክቶሬቱ ዛሬ በችሎት ቀርቦ በአመልካች ንብረት ላይ የዕግድ ትዕዛዝ የተላለፈው በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ ጊዜ ቀጠሮ ወንጀል ችሎት በፍ/መ.ቁ 008283 እንጂ አመልካች አሁን አቤቱታቸውን ባቀረቡበት መዝገብ ላይ በንብረታቸው ላይ ምንም አይነት ዕግድ ያልተላለፈ በመሆኑ ፍርድ ቤቱ ዕግድ እንዲነሳ ተለዋጭ ትዕዛዝ ለመስጠት የሚችልበት የህግ አግባብ ስለሌለ አመልካች እግድ ለሰጠው ፍርድ ቤት አቤቱታቸውን የማቅረብ መብት እንዳላቸው ሆኖ ፍርድ ቤቱ የአመልካችን አቤቱታ ውድቅ እንዲያደርገው ገልጾ በፅሁፍ መልስ ሰጥቷል ።

ተከሳሾቹ ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት በማሰብ የወንጀል ህግ አንቀጽ 32 1(ሀ) እና (ለ) እንዲሁም አንቀጽ 33 እና የሙስና ወንጀል አዋጅ ቁ 881/2007 አንቀጽ 9(ሀ) 2 በመተላለፍ እንዲሁም በወንጀል የተገኘ ገንዘብን ወይም ንብረትን ህጋዊ አስመስሎ ማቅረብ ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳትን ለመቆጣጠርና ለመከላከል የወጣውን አዋጅ ቁ 780/2005 በመተላለፍ እንደየተሳትፎ ደረጃቸው መከሰሳቸው ይታወቃል።

Exit mobile version