Site icon ETHIO12.COM

ለአገር መከላከያ ተጨማሪ 90 ቢሊዮን ብር በጀት ጸደቀለት፣

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበለትን የፌደራል መንግስት 122 ቢሊየን ብር ተጨማሪ በጀት አፀደቀ ። 90 ቢሊዮን ብር ለአገር መከላከያ ሚኒስቴር ስንቅና ትጥቅ ተጨማሪ በጀት እንዲሆን ተወሰኗል።

ተጨማሪ በጀቱ ለሀገር ደህንነት ማስጠበቂያ፣ ለሰብአዊ እርዳታ፣ በጦርነትና ግጭቶች ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች ማቋቋሚያ እንዲሁም ለሌሎች አስፈላጊ የመንግስት ስራዎች ማስፈጸሚያ የሚውል ነው ተብሏል፡፡

ተጨማሪ በጀቱን ማዘጋጀት ያስፈለገው በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በተካሄደው ጦርነት ምክንያት ተጨማሪ ወጪ በማስፈለጉ፣ መንግስት በሚሰበስበው ገቢ አሁን ያለውን የክፍያ ጥያቄ መመለስ አስቸጋሪ በመሆኑ እንዲሁም የተጨማሪ ወጪ ፍላጎትን በበጀት ሽግሽግ ማስተናገድ አዳጋች በመሆኑ ነው፡፡

በአጠቃላይ ለመከላከያ ሚኒስቴር ለትጥቅና ቀለብ 90 ቢሊየን ብር፣ ለእለት እርዳታ 8 ቢሊየን ብር፣ ለመጠባበቂያ 8 ቢሊየን ብር፣ ለካፒታል ፕሮጀክቶች ማስፈፀሚያ 7 ቢሊየን ብር እንዲሁም የታክስ ጉድለቱን ለማካካስ በበጀት ሽግሽግ ብቻ መሸፈን ባለመቻሉ ለወጪ አሸፋፈን ማስተካከያ 9 ቢሊየን ብር መመደቡ ነው የተመለከተው።

የ2014 በጀት አመት የፌደራል መንግስት የተጨማሪ በጀትና የወጪ አሸፋፈን ማስተካከያ ረቂቅ አዋጅን በ9 ተቃውሞ፣ በሰባት  ድምፀ ተአቅቦ እና በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል ።

ምክር ቤቱ በዛሬው ልዩ ስብሰባዉ የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን ረቂቅ አዋጅን መርምሮ በአብላጫ ድምፅ ለሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ መርቷል። ዘገባው የፋና ነው።

Exit mobile version